Monday, June 2, 2014

እስከዛሬ የጭቁኖች ድምፅ ነኝ ብዬ አስብ ነበር፡፡ ለካ የጭቁኖች ጦስ ነኝ፡፡

ወገን! ቀጥሎ የለጠፍኹትን ጽሑፍ እኔ እያነባኹ እንደሳቅኹበት እናንተም አንብባችኹና አንብታችኹ እንድትስቁልኝ ጀባ ብያችኃለኹ፡፡ ሙሉ ጽሑፉን አዲስ ጉዳይ መጽሔት ላይ ታገኙታላችኹ፡፡ ሀብቴና አዲስ ጉዳዮች ተባረኩ! (በቢላ አይደለም!) ዕድሜ ይስጣችኹ! (የሸቢ ሳይኾን የሥራ)




...

አጎቴ መቀጠል አልቻለም፡፡ ልማታዊ ንዴቱ ገታው፡፡ ሚስቴ ተራዋ ደረሰ፡፡
“ተው! ተው! የኔ ፍቅር፡፡”
“አንቺን ደግሞ ምን አደረግኹሽ?”
“ቤታችን በተንኳኳ ቁጥር ሊወስዱኽ መጡ እያልኹ በሥጋት ልሞት ነው፡፡ እንደምታየኝ ነፍሰጡር ነኝ፡፡ ዶክተሩ ከወራት በፊት መንታ ማርገዜን ነበር የነገረኝ፡፡ ትናንትና ስመረመር ግን “አንድ ብቻ ነው” አለኝ፡፡ እንዴት ብዬ ስጠይቀው “አንደኛው ወጥቼም ፍዳ ነው ብሎ ጠፍቷል” አለኝ፡፡ የኔ ቆንጆ፣ መንገድ ላይ ድሮ አስቁሜ እስማቸው የነበሩ ሕጻናት ሳይቀሩ ዛሬ ሲያዩኝ ከሩቁ ይሸሻሉ፡፡ አንዱን ባለፈው ጊዜ ይዤ ለምን ትሸሻለኽ ብለው “እና ከሰባ ዓመቴ ጀምሮ ቃሊቲ ልግባልሽ!” አለኝ፡፡ ተው፡፡ ተው፡፡ ሌላው ቢቀር ብዙ ምክሮችን ሰጥቼኽ አንዱን ምክር እንኳ ለመተግበር ፈቃደኛ አልኾንኽም፡፡”
“መጥተው የሚወስዱኽ ቀን አይታወቅምና ወፈር ያለ ቱታ ግዛ ብዬኽ ነበር እንቢ አልኸኝ፡፡ መቼም ካሰሯችኹ በኋላ ዱላ ስለማይቀርላችኹ እስከዚያው ሥጋ ለመደረብ ምግብ አብዝተኽ ብላ አልኹኽ፡፡ አልሰማኸኝም፡፡ አንጀት በልተኽ ታልፋቸው እንደኾነ አላውቅም፡፡ ይኼ አካልኽ እንኳን ዱላ ማሳጅ የሚችል አይመስለኝም፡፡ እሺ አልጋ ላይ መተኛቱን ትተኽ ወለል ላይ መተኛት ልመድ አላልኹም? አንተ ግን ቃሊቲ ሳይኾን ላንጋኖ እንደሚኼድ ሰው መዝናናት አብዝተኻል፡፡ ተው! ተው!...”
ለቅሶው ተጀመረ፡፡

እኔ ግን “ምክራችኹን ተቀብያለኹ የሚል ነገር ፊቴ ላይ አልተነበበም፡፡ እስከዛሬ የጭቁኖች ድምፅ ነኝ ብዬ አስብ ነበር፡፡ ለካ የጭቁኖች ጦስ ነኝ፡፡


ከረጅም ጸጥታ በኋላ እናቴ ለንግግር ቆረጠች፡፡
“የእኛ ቤት ሰው ሠላሳን አልፎ አያውቅም፡፡ ነፍሱን ይማረውና አባትኽ ደፋር ሰው ነበር፡፡ ክደቱ 45 በነበረበት ሰዓት ነው ለአየር ወለድነት የተመዘገበው፡፡ በአንድ የሥልጠና’ለት ከእሱ ክብደት በእጥፍ የሚልቅ ፓራሹት አዝሎ ከአውሮፕላን ዘለለ፡፡ ወደ ምድር አልተመለሰም፡፡ ከመዝለሉ በፊት አንዱ ጀነራል ላይ ምላሱን አውጥቶ ነበር አሉ፡፡ ዕድሜው ሠላሳ ነበር፡፡ ታላቅ ወንድምህም ደፋር ነው፡፡ ለመጨረሻ ጊዜ የታየው 97 ላይ የአንድ ተቃዋሚ ፓርቲ ቲሸርት ለብሶ ፓርላማ ምግብ ቤት ውስጥ ቦንቦሊኖ ሲበላ ነው፡፡ እሱም ሠላሳ ዓመቱ ነበረ፡፡ ይኸው አንተ ደግሞ መጣኽ፡፡ በጅብ ቅኝ ግዛጽ በተያዘች ሀገር ውስጥ አንበሳ ለመኾን ጣርኽ፡፡ የዛሬ ሳምንት ሠላሳ ዓመት ይሞላኻል፡፡ የፈራኹት ከመድረሱ በፊት ግን አባትኽና ወንድምኽ ያጡትን ነገር አንተ እንዳታጣ የነፍስ አባታችንን ጠርቻቸዋለኹ፡፡ ኹለቱም ከመጥፋታቸው በፊት ጸሎተ ፍትሐት አልተደረገላቸውም ነበር፡፡ እንግዲኽ አንተም የእርሱ ዕጣ እንዳይደርስብኽ አባ ቄሱ እባክዎ ኹላችንም ባለንበት የቁም ፍትሐት እንዲያደርሱልን ልለምነዎ!”
አጎቴም፣ ባለቤቴም፣ እናቴም የቁም ፍትሐቱን ሊቀበሉ ከተቀመጡበት ተነሡ፡፡ የነፍስ አባቴና እኔ ብቻ ተፋጥጠን ቆየን፡፡ የነፍስ አባቴ ከተቀመጡበት ተነሡ፡፡ ወደ በሩ አዘገሙ እያልጎመጎሙ፡፡

“ፍትሐቱንማ የጨረስኹት ጋዜጠኛ በጠፍ ጨረቃ በሚለቀምበት ዘመን ልጄ ጋዜጠኛ ነው ስትዪኝ ነው ወለተ ማርያም፡፡”  





ምንጭ፡- ሀብታሙ ሥዩም፡፡ "እሪ ብሎ መሳቅ፡፡" አዲስ ጉዳይ መጽሔት፡፡ ግንቦት 23፣ 2006 ፡፡

No comments:

Post a Comment