Wednesday, November 28, 2012

የውሎ ቅኝት ጸሎት


ባለፈው ጊዜ ቃል በገባኹት መሠረት እነሆ ቅዱስ አግናጥዮስ ካዳበራቸው የጸሎት ዓይነቶች አንዱን እንካፈል፡፡ ስያሜውን “የውሎ ቅኝት ጸሎት” ብንለው ያስማማል ብዬ አምናለኹ፡፡ ጸሎቱ አጭርና ቀላል ስለኾነ የትም ቦታ ኹነን የድርጊቶቻችንን መንፈሳዊነት ለመመርመርና በኃጢኣት ርቆ ከመጥፋት ለማምለጥ ጥሩ ራስን በእግዚአብሔር ዓይኖች የመፈተሻ (በዘመኑ ቋንቋ “የመገምገሚያ”) መሣሪያ ነው፡፡ 


“ለጸሎት ጊዜ ያጥረናል!” “ኑሮ እጅግ ቢዚ አድርጎኛል!” ለምንል ለብዙዎቻችን የገንዘብ ክፍለ ዘመን ሰዎች ከእግዚአብሔር ጋር ያለን ግንኙነት የምናጎለብትበት፣ እኛ ለእርሱ "ጊዜ ባይኖረን" እንኳ ፈጽሞ ለእኛ ጊዜ የማያጣው አባታችን እግዚአብሔር በዕለት ኑሯችንና በገጠመኞቻችን ውስጥ ወደ እኛ ለሚልካቸው ጥሪዎቹ በመንፈስ ንቁ መኾንን የምናዳብርበት ቀላል የጸሎት ዓይነት ነው፡፡ ምንም እንኳ ጸሎተኛው ጸሎቱን ማድረግ እንዳለበት በተሰማው ጊዜ ኹሉ ማድረግ ቢችልም መደበኛ ጊዜው ግን የቀኑ ፍጻሜ ነው፡፡ ይህንን ጸሎት የሚያዘወትር ሰው ራሱን በጸሎት መንፈስ በየጊዜው የመቃኘቱን ነገር ይበልጥ እየለመደውና የሕይወቱ አካል እየኾነለት ይኼዳል፡፡ በዚህም የተነሣ ጸሎቱ ቀስበቀስ የጸሎተኛው አስተሳሰብ መንገድ ይኾንለታል፤ ማለትም በዚህች ቀን የሚገጥሙትንና የሚያከናውናቸውን ነገሮች ኹሉ በእግዚአብሔር ሚዛን ይመዝናቸዋል፡፡ በዚህም ከእግዚአብሔር ጋር ያለው ፍቅር እየጨመረ ይኼዳል፡፡ እግዚአብሔር የሕይወቱ ማዕከል፣ የህልውናው ምክንያት ስለሚኾንለት ፍጹም የተረጋጋ የምሥጋና ሕይወት ይመራል፡፡ ለሚተማመኑበት ልጆቹ ነገሮችን ኹሉ ለበጎ እንዲኾኑ በሚያደርጋቸው በእግዚአብሔር ላይ ፍጹም እምነት ስለሚኖረውም ነገ ምን ይዞ እንደሚመጣ ባያውቅም ነገ የሚባለው ቀን ራሱ በአባቱ በእግዚአብሔር እጅ የተያዘ እንደኾነ ስለሚያውቅ (ሮሜ 8፣ 28) አይሠጋም፡፡ አይፈራም፡፡ አይጠራጠርም፡፡ ይልቁንም እምነቱ እንደ ዕንባቆም
“ምንም እንኳ የበለስ ዛፍ ባያፈራ፣
ከወይን ተክልም ፍሬ ባይገኝ፣
የወይራም ዛፍ ፍሬ ባይሰጥ፣
ዕርሻዎችም ሰብል ባይሰጡ፣
የበጎች ጉረኖ እንኳ ባዶውን ቢቀር፣
ላሞችም በበረት ባይገኙ፣
እኔ ግን በእግዚአብሔር ደስ ይለኛል፤
በአምላኬና በመድኃኒቴም ሐሤት አደርጋለኹ፡፡” (ዕን. 3፣ 17)
እያለ እንዲዘምር ይቀሰቅሰዋል፡፡