Saturday, January 26, 2013

ምናባዊ ጥያቄና መልስ ከቅዱሳን ጋር


በአንድ ቤተክርስቲያን ውስጥ በተቀምጫለኹ፡፡ በግቢው አፀድ ውስጥ ኑሯቸውን ከመሠረቱት አዕዋፍና የመቁጠሪያ ጸሎት ከሚያደርሱ አንዲት እናት ዝግተኛ የመቁጠሪያ ድምፅ በስተቀር ፀጥታ ነግሦዋል፡፡ ነፍሴ በፀጥታው ውስጥ ሟሟች፡፡


የአሲዚው ቅዱስ ፍራንቸስኮስ፣ የሳሉ ቅዱስ ፍራንቸስኮስና የሎዮላው ቅዱስ አግናጥዮስን አየኹዋቸው፡፡ ከአሲዚው ቅዱስ ፍራንቸስኮስ አጠገብ በደስታ የሚዘልሉ በርካታ እንስሳት ይታዩኛል፡፡ የሎዮላው ቅዱስ አግናጥዮስ ደግሞ ዓይኖቹ በተመስጦ ውቅያኖስ ላይ በርጋታ ይቀዝፋሉ፡፡ የሳሉ ቅዱስ ፍራንቸስኮስ ደግሞ በእጁ መጽሐፍ ይዟል፡፡ 














ያው እንደምታውቁት የመጽሐፍ ነገር አይኾንልኝምና “አባቴ፣ የያዝከውን መጽሐፍ ልየው?” ስል ጠየቅኹት፡፡ “ለአንዲት መንፈሳዊት ልጄ የጻፍኹት ነው፡፡” አለና ሰጠኝ፡፡ ርእሱ “Introduction to the Devout Life” ይላል፡፡ ውስጡን ገለጥ አድርጌ ሳይ የሚከተለውን አገኘኹ፡-

Tuesday, January 22, 2013

ተመልሰኽ ና!



በዚህ ዓለም ስትኖር በልብኽ ውስጥ ያስቀመጥኹት የእኔነቴ ኮከብ አለ፡፡ ይህን ኮከብ ከሑከትና ሩጫ ጨለማ ዘወር ብለኽ፣ በፀጥታና በጸሎት ብርሃን ስትፈልገው ታገኘዋለኽ፡፡ የህልውናኽ አልፋና ዖሜጋ፣ የሕይወትኽ ትርጉም ወደ ኾንኹት ወደ እኔ፣ ወደ አባትኽ ይመራኻልና ተከተለው፡፡ ኮከቡን የመከተል ጉዞኽን ስትጀምር የዚህ ዓለም ገዢ “ማነኽ ወዴት ነኽ? ማን ስለኾንኽ ነው ይህን ጉዞ የጀመርኸው?” የሚሉ ጥያቄዎችን ያቀርብልኻል፡፡

መልስኽ እንዲህ ይኹን፡- “እኔ ዩኒቨርሱን በእጆቹ ያበጃጀው የፍቅር ባርያ ነኝ፡፡ እርሱ በልቡናዬ ያስቀመጠልኝን ኮከብ ተከትዬ እየኼድኹ ነው፡፡ ዓላማዬም ለንጉሤ እኔነቴን እጅ መንሻ ማቅረብ ነው፡፡ ጉዞው ረጅም፣ መንገዱም ውጣ ውረድ የበዛበት እንደኾነ፣ ከእኔ የተሻለ ዐቅም ያላቸውን እንኳን አዳክሞ መግደል የቻለ ከባድ መንገድ እንደኾነ ዐውቃለኹ፤ ግን የጠራኝ እርሱ ኃይሌ ስለኾነልኝ ጉዞዬን እንደምፈጽመው አምናለኹ፡፡ ስሙ መጠጊያዬ፣ ኃይሉ ድጋፌ፣ ፍቅሩ መጽናኛዬ፣ ብርታቱም ምርኩዜ ናቸው፡፡” 

ገዢው ሊያታልልኽ “ተመልሰኽ ና!” ይልኻል፡፡ አንተ ግን በአዲሱ መንገድኽ ኺድ፡፡ ዕለት ዕለት ኮከብኽን ተከተል፡፡ ዕለት ዕለት ንጉሥኽን አግኘው፡፡ ዕለት ዕለት አንተነትኽን ለንግሥናው፣ ለማይነገረው ታላቅና ጥልቅ ፍቅሩ አቅርብለት፡፡ በእውነት ይገባዋልና!

እኔን ኾነኽ





ጌታ ሆይ! ምንኛ ወደድኸኝ! ስለወደድኸኝስ ምንኛ ተዋረድኽልኝ! ይህን ፍቅር ምን አንደበት ሊገልጠው፣ የትኞቹስ ቃላት ሊሥሉት ይችሉ ይኾን! የአንተ ታደርገኝ ዘንድ እኔን ኾንኽልኝ፤ ትፈልገኝ ዘንድ ተገኘኽልኝ፤ በመንግሥትኽ ታሳርፈኝ ዘንድ በድንግል ማኅጸን ኾነኽ ማረፊያ ፍለጋ ከበረት ገባኽልኝ፤ ታነሣኝ ዘንድ ወደቅኽልኝ፡፡ ጌታ ሆይ! በእውነት ሥራኽ ከአእምሮ በላይ ነው! እንደ ቅድስት ድንግል በልብ ይዞ “ዕፁብ ያንተ ሥራ!” እያሉ በምሥጋና ነፍስን በፊትኽ ከማፍሰስ ውጪ ምን መግለጫ ይኖረዋል!

የጣልኹትን እኔነቴን እኔን ኾነኽ ቀደስኸው! ያልቀደስኸው የእኔነቴ ቅንጣት የለም፡፡ ኹለመናዬን ቀደስኸው! ሰው ኾነኽ ሰው መኾንን ቀደስኸው! አቤቱ ስምኽ ይባረክ! የድንግል ማርያም ልጅ ፍጹም አፍቃሪዬ፣ የእነቴ እውነተኛ ወዳጅ ሆይ! ስምኽ ከፍ ከፍ ይበል፡፡ ጌታ ሆይ! በየዕለቱ ይበልጥ አንተን ማወቅን፣ አንተን ማፍቀርንና አንተን መከተልን በልቤ ጨምርልኝና በልቤ በየቀኑ ተወለድ፤ ኑርልኝም፡፡ እንዳረፍኽባት ግርግም ነገሥታቱም፣ እረኞቹም፣ መላእክቱም ወደ እኔ ሲመጡ የሚያገኙት አንተን ብቻ፣ የሚሰሙትም ቃልኽን፣ የሚሰማቸውም ሰላምኽና ፍቅርኽ ብቻ ይኹን፡፡ አባቴ ሆይ! እኔን የሚያገኙኝ ኹሉ አንተን እንጂ እኔን አያግኙ፡፡ በእኔ ውስጥ አንተ ብቻ እንጂ እኔ አይኑር፡፡ መድኃኒት በኾነልኝ ስምኽ! አሜን፡፡