Monday, October 28, 2013

የእሑድ ብቻ ሃይማኖት


ሰሞኑን እግር ጥሏቸው እጄላይ ከወደቁ ጽሑፎች መካከል አንደኛው ዲትሪች ቦንሆፈር ስለተባለ፣ አይሁዳውያን በናዚ ጥቃት በሚደርስባቸውና የጀርመን ብሔራዊት ቤተክርስቲያንም ከሒትለር ጋር ባበረችበት ዘመን አካኼዷ ትክክል አለመኾኑን ወቅሶ አይሁዳውያንን ይረዳ ስለነበረ ሊቅ ነው፡፡ ስለዚህ ሰው የተጻፈው ይህ ጽሑፍ በውስጡ ከያዛቸው መልእክቶች ኹሉ ገንኖ የተሰማኝን እንዲህ እንካፈል፡-


እውነተኛ ክርስትና የእሑድ ብቻ ሃይማኖት አይደለም- የምንተነፍሰው አየር፣ የልባችን ምት፣ በሥሮቻችን ውስጥ ያለ ደም፣ የህልውናችንም መሠረት ነው እንጂ፡፡ ይኹን እንጂ እውነተኛ ክርስትና፣ እውነተኛ ደቀ መዝሙርነት፣ ክርስቶስን በእውነት መከተል ዋጋ ያስከፍላል፡፡ በ2000 ዓመታት ታሪኳ ቤተክርስቲያን ክርስቶስን የተከተለችባቸው ጊዜያት ነበሩ፡፡ ክርስቶስን የመከተል ቋንቋ እየተናገረች እውነታው ሲታይ ግን የዓለም ተከታይ ኾና የተገኘችባቸው በርካታ ጊዜያትም አሉ፡፡ አንድ ሰው ቤተክርስቲያን ውስጥ ኾኖ ቤተክርስቲያኗን ከጥፋት መንገዷ እንድትመለስ ቢጮኽ ያ ሰው የቤተክርስቲያን ጠላት ተደርጎ ይቆጠራል፡፡ ቤተክርስቲያኒቱ እጅግ የሚያስፈልጋት ሰው ግን እርሱ ነበር፡፡ ታሪክ እንደሚያስረዳው ቤተክርስቲያን የዓለምን ዕውቅና የፈለገችባቸው ጊዜያት ነበሩ፡፡ ዕውቅናውን ባገኘች ጊዜ ግን ወንጌልን አሳልፋ ሰጥታ፤ በዚህም ተስፋዋን ጥላ ነበር፡፡

ቤተክርስቲያን ወንጌልን ስትተው ማዕከሏና የወደፊት ህልውናዋ የኾነውን መልእክቷን ታጣለች፡፡ ቤተክርስቲያን በወንጌል ላይ እምነት ስታጣ ለባህል መልእክት ባርያ ትኾናለች፡፡ እነዚህ ችግሮችም ቀስ በቀስ የቤተክርስቲያኗን የወደፊት ህልውና መሠረት ይገድሉታል፡፡ እግዚአብሔር ግን በአንድ ቅርንጫፍ ብቻ የሚኖር አይደለም፡፡ ወንጌል እያስገመገመ እንደሚኼድ ግሩም ወንዝ ነው፡፡ ሊበራሊዝም አያግደውም፤ ጭቆና አያፍነውም፤ ቢሮክራሲ አያንቀውም፤ የአገልጋዮች ስንፍናም አይገድለውም፡፡ አንድ ቤተክርስቲያን እውነተኛውን ወንጌል መመልከትና እርሱንም ከመስበክ ፈቀቅ ስትል እግዚአብሔር ሌላ ቤተክርስቲያን፣ ሌላ ትውልድ፣ ሌላ ሕዝብ ያስነሣል፡፡ አንድ ታሪካዊ ቅርንጫፍ በባህል ሲዋጥ እግዚአብሔር ሌላውን ቅርንጫፍ ስለ እውነት ያስነሣል፡፡         


Source:- <http://www.cbcroseville.org/sermons/text/The_Cost_of_Discipleship-1.pdf>