Wednesday, November 28, 2012

የውሎ ቅኝት ጸሎት


ባለፈው ጊዜ ቃል በገባኹት መሠረት እነሆ ቅዱስ አግናጥዮስ ካዳበራቸው የጸሎት ዓይነቶች አንዱን እንካፈል፡፡ ስያሜውን “የውሎ ቅኝት ጸሎት” ብንለው ያስማማል ብዬ አምናለኹ፡፡ ጸሎቱ አጭርና ቀላል ስለኾነ የትም ቦታ ኹነን የድርጊቶቻችንን መንፈሳዊነት ለመመርመርና በኃጢኣት ርቆ ከመጥፋት ለማምለጥ ጥሩ ራስን በእግዚአብሔር ዓይኖች የመፈተሻ (በዘመኑ ቋንቋ “የመገምገሚያ”) መሣሪያ ነው፡፡ 


“ለጸሎት ጊዜ ያጥረናል!” “ኑሮ እጅግ ቢዚ አድርጎኛል!” ለምንል ለብዙዎቻችን የገንዘብ ክፍለ ዘመን ሰዎች ከእግዚአብሔር ጋር ያለን ግንኙነት የምናጎለብትበት፣ እኛ ለእርሱ "ጊዜ ባይኖረን" እንኳ ፈጽሞ ለእኛ ጊዜ የማያጣው አባታችን እግዚአብሔር በዕለት ኑሯችንና በገጠመኞቻችን ውስጥ ወደ እኛ ለሚልካቸው ጥሪዎቹ በመንፈስ ንቁ መኾንን የምናዳብርበት ቀላል የጸሎት ዓይነት ነው፡፡ ምንም እንኳ ጸሎተኛው ጸሎቱን ማድረግ እንዳለበት በተሰማው ጊዜ ኹሉ ማድረግ ቢችልም መደበኛ ጊዜው ግን የቀኑ ፍጻሜ ነው፡፡ ይህንን ጸሎት የሚያዘወትር ሰው ራሱን በጸሎት መንፈስ በየጊዜው የመቃኘቱን ነገር ይበልጥ እየለመደውና የሕይወቱ አካል እየኾነለት ይኼዳል፡፡ በዚህም የተነሣ ጸሎቱ ቀስበቀስ የጸሎተኛው አስተሳሰብ መንገድ ይኾንለታል፤ ማለትም በዚህች ቀን የሚገጥሙትንና የሚያከናውናቸውን ነገሮች ኹሉ በእግዚአብሔር ሚዛን ይመዝናቸዋል፡፡ በዚህም ከእግዚአብሔር ጋር ያለው ፍቅር እየጨመረ ይኼዳል፡፡ እግዚአብሔር የሕይወቱ ማዕከል፣ የህልውናው ምክንያት ስለሚኾንለት ፍጹም የተረጋጋ የምሥጋና ሕይወት ይመራል፡፡ ለሚተማመኑበት ልጆቹ ነገሮችን ኹሉ ለበጎ እንዲኾኑ በሚያደርጋቸው በእግዚአብሔር ላይ ፍጹም እምነት ስለሚኖረውም ነገ ምን ይዞ እንደሚመጣ ባያውቅም ነገ የሚባለው ቀን ራሱ በአባቱ በእግዚአብሔር እጅ የተያዘ እንደኾነ ስለሚያውቅ (ሮሜ 8፣ 28) አይሠጋም፡፡ አይፈራም፡፡ አይጠራጠርም፡፡ ይልቁንም እምነቱ እንደ ዕንባቆም
“ምንም እንኳ የበለስ ዛፍ ባያፈራ፣
ከወይን ተክልም ፍሬ ባይገኝ፣
የወይራም ዛፍ ፍሬ ባይሰጥ፣
ዕርሻዎችም ሰብል ባይሰጡ፣
የበጎች ጉረኖ እንኳ ባዶውን ቢቀር፣
ላሞችም በበረት ባይገኙ፣
እኔ ግን በእግዚአብሔር ደስ ይለኛል፤
በአምላኬና በመድኃኒቴም ሐሤት አደርጋለኹ፡፡” (ዕን. 3፣ 17)
እያለ እንዲዘምር ይቀሰቅሰዋል፡፡ 

Wednesday, October 10, 2012

“እምቢ!”


ራሳችንን ኹሉን ማድረግ እንደሚችሉና ሞት ፈጽሞ እንደማያውቃቸው ነገሮች ቆጥረን በምንኖርበት በዚህ ዓለም የኑሯችን ፍልስፍናው “ላብዛ! ልግዛ! ልብለጥ! ልሻል!” የሚል የሐሰት ጌትነትና በሃይማኖተኛነታችን ውስጥ ሳይቀር በተሸሸገ ፈጣሪን መካድ ስለኾነ፣ እነሆ የፍቅር-የለሽ እንቅስቃሴዎቻችን ውጤቶች አስከፊ መኾናቸውን ብናውቅም እንኳ “በአምልኮ-ርእስ” (ራስን በማምለክ) ተጠምደን “እኔ ብቻ!” በሚል የኑሮ ዘይቤ አእምሮ እንደሌላቸው ሰዎች ከሐዘን ወደ ሐዘን እንጓዛለን፡፡

በባሕርዩ አምላክ የኾነውን እግዚአብሔርን በፍጹም ልባችን፣ በፍጹም ነፍሳችን፣ በፍጹም ኃይላችንና በፍጹም ዐሳባችን አምላክ እንዳይኾን “እምቢ!” አልን፤ በቃላችን ብንመሰክርም በግብራችን በምንገልጠው ሐሰታችን አምላክ እንዳይኾነን ከለከልነው፤ በደጅ ቆሞ ለሚያንኳኳው ፍቅሩ የልባችንን በር ጥርቅም አድርገን ዘጋንበት፡፡ ፍቅሩን እምቢ ባለችው በሐሰተኛና ጨካኝ ልባችን የተነሣ መዋደድን፣ መተዛዘንን ከእኛ አራቅን፡፡ ከዕርፍ ይልቅ ሰይፍ፣ ከመደጋገፍ ይልቅ መጠላለፍ፣ ከመሳሳም ይልቅ መነካከስ ቀለለን፡፡ ታክሲዎቻችን የመሰዳደቢያ መድረኮች፣ ድንበሮቻችን የመዋጊያ ዐውድማዎች፣ ኃላፊነቶቻችን የመጠላለፊያ ገመዶች፣ መገናኛ ዘዴዎቻችን የሐሰቶቻችን መስበኪያዎች ኾኑ፡፡

በየቀኑ ሐዘንን በጽዋ እየሞላን እንጋታለን፡፡ እንባንም በስፍር እንጠጣለን፡፡ የእንባችን ምሬቱ ሲበዛብን አንዳችን የሌላችንን ደም በየጽዋችን እንቀላቅላለን- ምሬቱን ይቀንስልን እየመሰለን፡፡ ነገር ግን ምሬቱ በዕጥፍ ይጨምራል፡፡ ኃጢኣትን በኃጢኣት ለማስተካከል እንሮጣለን፡፡ የልባችንን እውነተኛውን ማረፊያ እግዚአብሔርን ስለተውነው ያለን ፈጽሞ አይበቃንም፡፡ በምኞት እንቃጠላለን፡፡ ምኞታችንን በማመንዘርና በመስረቅ፣ ማመንዘራችንንና መስረቃችንን በመግደል፣ መግደላችንን በመዋሸት ለመጋረድ እንሮጣለን፡፡ ኹሉን የሚያይ እግዚአብሔር ግን ይህን ኹሉ ጠማማነታችንን እያየ እንኳን የፍቅሩን መግቦት አያቋርጥብንም፡፡  አንድ ቀን ይመለሳል ብላ ልጇን እንደምትጠብቅ እናት የልባችንን ደጅ ደጅ ይመለከታል፡፡ ልጁን እንደናፈቀ አባት እጆቹን ዘርግቶ ይጠብቃል፡፡ ይህች የተዘረጋች ክንዱ ለማን ተገለጠች?

Saturday, October 6, 2012

ዕረፉ፡፡ እኔም አምላክ እንደኾንሁ ዕወቁ፡፡ (መዝ. 46፡ 10)


ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ጳጳስ በሚቀድሱበት ቤተክርስቲያን ውስጥ አንዲት ድብርት ፊታቸው ላይ ጎጆዋን የሠራችባቸው የሚመስሉ ክርስቲያን እናት ከፊት ለፊታቸው ተመለከቱ፡፡ በቅዳሴ ላይ እያሉ ድብርት የተከናነበውን የሴትየዋን ፊት ያስተዋሉት ጳጳስ በቅዳሴው ፍጻሜ ሴትየዋን ወደኋላ ቀረት ብለው እንዲያናግሯቸው መልእክት ላኩባቸው፡፡ ሴትየዋ እንደተባሉት ጳጳሱን ለማነጋገር ወደኋላ ቀረት አሉ፡፡ “እንደምን አሉ እናቴ? ምነው የከፋዎት ይመስላሉ፡፡” ሴትየዋ ደንገጥ ብለው “አይ እንደው ነው… እንደው ዝም ብዬ ነው፡፡ ድካሙ እርጅናው ይኾናል፡፡” ሲሉ መለሱ፡፡ ጳጳሱ ግን በዚህ መልስ አልረኩም፡፡ ይልቁንም ፊታቸው ውስጣቸውን የሚያስጨንቃቸውና የሚያበሳጫቸው ነገር እንዳለ እንደሚያሳብቅ በመጠቆም ችግሩን እንዲያካፍሏቸው አበረታቷቸው፡፡ በዚህ ጊዜ ሴትየዋ ወደ ጳጳሱ ዘንድ ይቀርቡና “አባቴ፣ ጸሎት ሰለቸኝ፡፡ ታከተኝ፡፡ እንደዛሬ ሳይታክተኝ የማልደግመው የጸሎት መጽሐፍ የለም፡፡ ከጥቂት ዓመታት በፊት ጀምሮ ግን የጸሎት መጽሐፌን ስከፍትና ስዘጋው ካልኾነ በስተቀር መኻል ላይ ስለምን እንደጸለይሁ እንኳ አላውቀውም፡፡ ይህም እጅግ ሲበዛ አታክቶኛል፡፡ እርግፍ አድርጌ ልተወው ነው፡፡” ሲሉ ራሳቸውን ይገልጣሉ፡፡ ጳጳሱም ሴትየዋን በጥሞና ካዳመጡ በኋላ “እናቴ፣እስኪ ጠዋት ከዕንቅልፍዎ ሲነቁ እዚያው መኝታዎ ላይ አንድ አስራ አምስት ደቂቃ ያህል ይቆዩና አካልዎን ዘና አድርገው የትንፋሽዎን ምልልስ፣ የልብዎን ምት፣ የደም ሥርዎችዎን ንዝረት፣ በዙሪያዎ ያለውን አየር በጸጥታ ያዳምጡ፡፡” የሚል መልስ ሰጧቸው፡፡ ሴትየዋ ምንም እንኳ የጳጳሱ መልስ ግራ ቢያጋባቸውም “የካህን ቃል እንዴት እምቢኝ ይባላል!” በሚል ሐሳብ ትእዛዝ እሺታቸውን ገልጸው ኼዱ፡፡

Wednesday, September 19, 2012

እንደሞተ ሰው


እጅግ ርኅሩኅና መልካም ኢየሱስ ሆይ! እስከ መጨረሻው ሕይወቴ ድረስ ከእኔ ጋር የሚኖረውን፣ በእኔ ውስጥ የሚሠራውንና፣ ከእኔ ጋር የሚቀረውን ጸጋህን ስጠኝ፡፡ እኔ፣ አንተ ዘወትር የምትወደውንና የሚያስደስትህን ነገር ብቻ እንድወድ አድርገኝ፡፡ ያንተ ፈቃድ የእኔ ፈቃድ ይኹን፡፡ የእኔም ፈቃድ ዘወትር የአንተን ፈቃድ ይከተል፤ ፈጽሞም ከእርሱ ጋር ይስማማ፡፡

አንተ ከምትወድደው ነገር በቀር ሌላ እንዳልወድ፤ አንተ ምትጠላው ነገር በቀር ሌላ እንዳልጠላ፤ መውደዴና መጥላቴ ከአንተ ሐሳብ ጋር አንድ እንዲሆን አድርግልኝ፡፡ በዚህ ዓለም ላይ ካሉት ነገሮች ኹሉ እንደሞተ ሰው ተለይቼ እንድኖር አድርገኝ፡፡ ላንተ ፍቅር ስል ራሴን እንድንቅና በዚህ ዓለም መታወቅን እንዳልወድ አድርገኝ፡፡

እኔ ከምመኛቸውና ከምፈልጋቸው ኹሉ በላይ በአንተ ዕረፍት ማግኘትን ስጠኝ፤ ልቡናዬም በአንተ ሰላምን እንዲገኝ አድርግልኝ፡፡ የልቤ እውነተኛ ሰላምና ዕረፍት አንተ ብቻ ነህ፤ ከአንተ ከተለየሁ ግን ኹሉ ነገር ጭንቀትና ሁከት የተሞላበት ይኾናል፡፡

እግዚአብሔር ሆይ! በሰላም እንድኖር የምታደርገኝ አንተ ብቻ ስለኾንህ በምተኛበት ጊዜ በሰላም አንቀላፋለሁ፡፡ (መዝ 4፡ 8)

ምንጭ፡- ክርስቶስን መምሰል

Monday, September 10, 2012

God loves me. Therefore, I am.


There is a certain similarity between how I am in myself and how I perceive God in my life and my prayer. Take, for example, a person preoccupied by law, rules and right behaviour. He or she is focussed on observances and performance, and that can be good, but it is not a place at which to remain, for there is more. Such a person will tend to see God as Lawgiver, Judge, Accountant, someone who is watching with a critical eye.
But the Lord is requesting of me not only a life lived by commandments, even if they be divine. My Creator is making an offer to me, inviting me into a personal, conscious relationship of love with Godself. I am invited to awaken to the deep truth of what it means to be a creature, namely, that my Creator is loving me into existence and is doing this continuously. I exist because God wants me to exist; he loves me, and so I exist. I am attractive and important in God’s eyes; I am ‘precious’ to him (Is 43:4). To accept this truth is a big shift in my perception of who I am, and in my image of who God is. A new level of relationship with God comes into view. But there is yet more.
This God wants my heart. As my Creator, God is giving me his heart already by loving me without reserve. Over the long history of salvation God has revealed more of his desire towards me by arriving at the extraordinary point of giving me his Son, so that I can be not only a loved creature but an adopted son or daughter, who shares in the Sonship of Jesus and in the inner life of the Three Persons. It takes time and God’s grace to become able to hear this in such a way that it is real for me and comes into play in my prayer and my life. God can only love me: I am his heart’s delight. He wants me to hear this in my heart, to hear it in an operative way. Personal prayer is a privileged place in which to hear it and to develop it over a lifetime. (Adapted from Finbarr Lynch: When You Pray. Dublin: Messenger Publications, 2012).
Source:- Sacred Space <http://www.sacredspace.ie/>

Thursday, August 2, 2012

ዐለምን መውደድ እንዴት ከእግዚአብሔር ጋር ሊያጣላ ይችላል?



ታላቁ መጽሐፍ “ገንዘብን መውደድ የክፋት ኹሉ ሥር ነው፡፡” (1ኛ ጢሞ. 6፡ 10) ሲል ወይም “ዐለምን መውደድ ለእግዚአብሔር ጥል እንደኾነ አታውቁምን?” (ያዕ. 4፣ 4) ብሎ ሲናገር ምን ማለቱ ነው? እግዚአብሔር ራሱ የፈጠረውን ዓለም መውደድ እንዴት ከእግዚአብሔር ጋር ሊያጣላ ይችላል? ደግሞስ ኦሪት ዘፍጥረት እግዚአብሔር ፈጥሮ ሲጨርስ “ኹሉም መልካም እንደኾነ ዐየ” ይል የለምን? ታዲያ እንዴት መልካም ነገርን መውደድ መጥፎ ሊኾን ይችላል? ይህ “ዐለምን መውደድ” የሚባለው መጥፎ ነገር ምን ማለት ነው?

Thursday, July 5, 2012

ላም እሳት ወለደች


የገዛ ልጇ እከክ ኾኖ ጎን ጎኗን ሲያቃጥላት፣
መጥባቱን ሳትከለክለው እየነከሰ ሲያቆስላት፣
ወልዳ ያዘለችውን ተስገብግቦ ሲቦጭቃት::
 እዩ...

"እሳት ወለደች!" በሉላት፤ 
በእንባ ሟሙ፤ አልቅሱላት፡፡

"ያድግልኛል፡፡" ብላ ቻለች፤
የልጅ ክፉ አደገባት፡፡

ደግሞ መጥምጦ መጥምጦ…
ወፍሮ፣ ቦካክቶ ቢያድግም፤
አልጠረቃም፡፡

ሆዱ ግን ገዝፎ ተሾልሹሎ፣
ውስጥ ኅሊናው ሰውነቱ በከርሥ ሰደድ ተቃጥሎ፣
በቃኝን ላያውቅ በቦርጩ ምሎ፡፡

እርሷ አቂማ፣ ውስጧ ቆስሎ፣ "እርሜ ነህ አንተ!" ብላ፣
የነፍሷን ጠላት ግና በኵሯን በአዲስ ልትተካው ፍሬ አዝላ-      
 በሆዷ፡፡
ወሯን ስትጠብቅ በተስፋ እየጠዘጠዛት ቁስሉ፣
የሚያጽናናት ማንም ሳይኖር የእርሷኑ እርም ሥጋ ከበኩሯ ጋራ እየበሉ...
ቀኗ ደርሶ ምጥ ስትጀምር ልትገላገል ከመከራ፣
ያው ጠላቷ፣ ደግሞም በኵሯ፣ የምጥ ሐሤቷን ሰምቶ እጅግ ፎከረ አቅራራ፡፡

“እኛ ያደግንበትን ሌላ ሊጠባው ከቶ?!
አሮጊቷም ልታገግም በሚያድግ ልጅ ገና ፋፍቶ!?
ሃሃሃሃሃሃሃሃሃሃ...!"

ቁጣው ተቀጣጠለ፤
ተወራጨ፤
ተበሳጨ፤
ሰማይ ቧጥጦ መሬት ነጨ፡፡
አላበቃም…

የጨቅላውን አናት ለመፈጥፈጥ የእናቱን ሆድ ረገጠ፤
የእምዬን ልጅ ወንድሙን ከሽርት ውኃው አፈረጠ፤
እናትየውም ደም መታት ጨቅላውም ልጅ ጨነገፈ፡፡

ሸሽታ ስትሰደድ...
በየጎዳናው፣
በየጥጉ፣ 
በየውቅያኖስ፣
በየደኑ፣
በየሻርኩ ሆድ፣ 
በየአሞራው ከርሥ፣ 
የበረኀው፣
በየጓዳው፣
በየገንዳው... 
የተረጨ፣ 
የፈሰሰ፣ 
የተቀዳ፣ 
የተጠጣ፣ 
የተደፋ
ደሟን ዐይተው ጎረቤቶቿ ተሳቀቁ፤
አንዳንዶቹም ተሳለቁ፡፡

እንዲህም ብለው በጋራ ሕመምተኛይቱን አሟት፡- 
“ሴሎቿ እርስ በርሳቸው የሚባሉባት ይህቺ ሴት፣
ምንም ጥርጥር የለውም የልጅ ሾተላይ አለባት፡፡” 


                                                                       (መቼ ትድን ይኾን? )

Tuesday, June 19, 2012

“መምሬ”[1] ኢየሱስ



ክርስቲያን ማለት “ተላውያኒሁ ለክርስቶስ” (“የክርስቶስ ተከታዮች”) ማለት እንደኾነ አበው ያስተምራሉ፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚነግረን እነዚህ ተከታዮች ከክርስቶስ ሊያገኟቸው ይፈልጓቸው ከነበሩ ነገሮች አንዱ ትምህርት ነው፡፡ በመኾኑም የክርስቶስ ተማሪዎች ነበሩ፡፡  ለዚህም ነው “ጸሎት አስተምረን፡፡” ብለው መምህራቸውን ሲጠይቁት የምናየው፡፡ ይህም እኔ “ክርስቲያን” ከኾንኹ የእነዚህ ተማሪዎች ወገን ነኝ ወደሚል ድምዳሜ ያደርሰናል፡፡ በዚህም መሠረት እርስዎ ክርስቲያን በመኾንዎ ብቻ መምህር ኢየሱስን በተመለከተ አንድ ሥልጣን ተሰጥቶዎታል ማለት ነው- ለመማር የሚፈልጉትን እንዲያስተምርዎ የመጠየቅ ሥልጣን፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ትናንትም፣ ዛሬም ለዘለዓለምም የማይለወጥ ስለኾነ የሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስ ብቻ ሳይኾን የእርስዎም መምህር ለመኾን አይደክመውም፡፡ ይልቁንም ደስ ይበልዎት! አዎን ኢየሱስ የእርስዎ መምህር ነው፡፡ ደስ ይበልዎት!

እሺ! ለአፍታ መምህር ኢየሱስ እግር ሥር ከሐዋርያቱ ጋር እንዳሉ ያስቡና ዛሬ እንዲያስተምርዎት የሚፈልጉትን ርእስ ያቅርቡለት፡፡ ዛሬ ኢየሱስ ምን እንዲያስተምርዎ ይወድዳሉ?  

ያገራችን ሰዎች ሲተርቱ “ፈረስ ያደርሳል እንጂ አይዋጋም፡፡” እንዲሉ እርስዎን ከመምህሩ ጋር እንዲኾኑ ካደረስኹዎት በኋላ እኔ እርሱ መማር የፈለገውን ልሰማ የ16ኛውን ክፍለ ዘመን የቤተክርስቲያን ጀግና የሎዮላው ቅዱስ አግናጥዮስን መስማት ከጅያለኹ፡፡[2] እርሱ ቀጥሎ ያለውን የትምህርት ጥያቄ አቅርቦ ነበር፤
እጅግ ተወዳጁ ጌታዬ ሆይ!
ለጋስ መኾንን አስተምረኝ፡፡
አንተን እንደሚገባህ ማገልገልን አስተምረኝ፡፡
ዋጋን ሳይቆጥሩ መስጠትን
መቁሰልን ሳይሠጉ መዋጋትን
ዕረፍትን ሳይሹ መልፋትን
ፈቃድኽን እያደረግሁ እንደኾነ ከማወቅ በስተቀር
አንዳችም ሽልማትን ሳይጠይቁ መድከምን አስተምረኝ፡፡

መምህሩም ኹሉ በእጁ ኹሉ በደጁ ነውና ይህን ተማሪውን በጥያቄው መሠረት ጥሩ አድርጎ እንዳስተማረው የሕይወት ታሪኩን የከተቡት ወዳጆቹ መስክረውልኛል፡፡



[1]መምሬ” ኢትዮጵያውያን ካህናትን ለመጥራት ከሚጠቀሙባቸው ቃላት አንዱ ነው፡፡ የቃሉ ምንጭ “መምህር” የሚለው የግእዝ ቃል ሲኾን ትርጉሙም አስተማሪ፣ የሚያስተምር ማለት ነው፡፡ “መምህርየ” ሲኾን ደግሞ የእኔ አስተማሪ የሚል ፍቺ ይይዛል፡፡ በአማርኛም “መምህሬ” ይባላል፡፡ እንግዲህ በእንግሊዘኛ contraction ብለን የምንጠራው ዓይነት የቋንቋ ኺደትን አልፎ ነው “መምሬ” ወደሚል ቃል የተለወጠው ብንል ብዙም የምንሳሳት አይመስለኝም- ቢያንስ ለዛሬ፡፡
[2] ምክንያቱም አንዳንድ ጎበዝ ተማሪዎቹ እንደነገሩኝ መምህር ኢየሱስ ጎበዝ መኾን የሚሹ ሰነፍ ተማሪዎች ከጎበዝ ተማሪዎቹ እንዲኮርጁ ይፈቅድላቸዋል፡፡ መኮረጅ የሚፈቀድባት ትምህርት ቤት እንዴት ትመቻለች ጃል!


Sunday, May 27, 2012

ከቅዱስ አውጉስጢኖስ ኑዛዜዎች

አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ ሆይ!


ሰማይና ምድርን ትመላለህና እነርሱ ሊይዙህ ይችሉ ይሆን? ወይስ ሊይዙህ ስለማይቻላቸው ሞልተህ ትፈስ ይሆን? ሰማይና ምድርን መልተህ ተትረፍርፈህ ስትፈስስ ወዴት ትፈስ ይሆን? ወይስ ሁሉን የምትይዝ አንተ በርግጥ በምልዐትህ ሁሉን ትይዛለህና በምንም ልትያዝ አትችልም? በምልዐትህ የምትገኝባቸው ሸክላዎች አንተን አይዙህም- ቢሰበሩም እንኳ አንተ አትፈስምና፡፡ በእኛ ላይ ስትፈስም አንተ የምትወርድ አይደለህም- እኛ ወደላይ ከፍከፍ እንላለን እንጂ፡፡ አንተ የምትበተን አይደለህም- እኛን ትሰበስበናለህ እንጂ፡፡ 

Thursday, May 24, 2012

Anima Christi


ይህንን ጸሎት በማስተዋል ያንብቡልኝ፡፡


የክርስቶስ ነፍስ ሆይ! ቀድሰኝ፡፡
የክርስቶስ ሥጋ ሆይ! አድነኝ፡፡
የክርስቶ ደም ሆይ! በሐሴት ሙላኝ፡፡
ከክርስቶስ ጎን የተገኘህ ውኃ ሆይ! እጠበኝ፡፡
ሕማማተ ክርስቶስ ሆይ! አበርታኝ፡፡
መልካሙ ኢየሱስ ሆይ! ስማኝ፡፡
በቁስሎችህም ሸሽገኝ፡፡
ከአንተ ለመለየት ሥቃይ አሳልፈህ አትስጠኝ፡፡
ከክፉው ጠላቴ መከታ ሁነኝ፡፡
በሞቴ ሰዐት ጥራኝ፡፡
ወዳንተ እንድመጣ ጥራኝ፡፡
ከቅዱሳንህ ጋር አንተን ለዘለዓለም እንዳመሰግን፡፡
አሜን፡፡

(ምንጭ፡- Draw me to Your Friendship: The Spiritual Exercises. A Literal Translation and A Contemporary Reading. )

Saturday, May 12, 2012

"God of Surprises" ውብ መጽሐፍ


ሰሞኑን እመለካከታቸው ከነበሩ መጻሕፍት መካከል በአባ ዤራርድ ሒዩስ የተጻፉ ሁለት መጻሕፍት ነበሩ፡፡ አንደኛው “God, where are you?” የሚል ርእስ ያለው ሲሆን ሁለተኛው “God of Surprises” ይሰኛል፡፡ በመጀመሪያው እንደቅዱስ አውጉስጢኖስ ኑዛዜዎች (Confessions) የተባለው መጽሐፍ አባ ዤራርድ ከሦስተ ዓመታቸው ጀምሮ መጽሐፉን እስከጻፉበት ጊዜ ድረስ እግዚአብሔርን ፍለጋ ያደረጉትን ጉዞ ለዛ ባለው ውብ ፍልስፍናዊ ትረካ ያስቃኙናል፡፡ “God of Surprises” የተሰኘው ሁለተኛው መጽሐፍ የተጻፈበት ዓላማ የመጽሐፉ ጀርባ ላይ እንዲህ ተብሎ ሰፍሯል፡-

Jesus said: ‘The Kingdom of Heaven is like a treasure hidden in a field. This book has only one purpose: to suggest ways of finding the treasure in what we may consider a most unlikely filed- ourselves. It is a guide book to the inner journey which we are all engaged and has much to say to those who have a love/hate relationship with the Church to which they belong or once belonged.  (አጽንዖት የኔ)       

ዐቢይ ጉዳዩ እግዚአብሔር በሕይወታችን የሚሠራባቸውን እኛ ግን የማናስተውላቸውን አስደናቂ መንገዶች በማየትና በዚህም እግዚአብሔር ምን ያህል እንደሚወድደን በማሰብ በፍቅሩ መደነቅ፣ በአሠራሩ ግሩምነት መመሰጥ፣ በሕይወትነቱ መኖር ነው፡፡ ከዚህ መጽሐፍ ካገኘኋቸው ቁም ነገሮች ጥቂቶቹን ላካፍላችሁ፡፡
   
ከእኔ ይልቅ ለእኔ የሚቀርበው እግዚአብሔር

Tuesday, May 1, 2012

ችግር ፈጣሪው ኢየሱስ


በዚህ በሰሙነ ፋሲካ አንድ ጧት የሰውየው በር ተንኳኳኳ፡፡ ሰውየው በሩን ሲከፍት ያየውን ማመን አቃተው፡፡ ኢየሱስ! አዎን ኢየሱስ ከበሩ ላይ ቆሟል፡፡ በድንጋጤ ፈዝዞ ቀረ፡፡ ኢየሱስ ግን “አይዞህ፡፡ አትፍራ፡፡ እኔ ነኝ፡፡” ሲል አረጋጋውና ወደ ውስጥ መዝለቅ ይችል እንደሆነ ጠየቀው ሰውየውም “በደስታ ጌታዬ!” ሲል መለሰለት፡፡ ኢየሱስ ወደ ቤቱ ውስጥ ገባ፡፡ ገና ወንበር ላይ እንኳ አረፍ ሳይል ሰውየው ችግሩን ይዘረዝርለት ገባ- ያደረገውን፣ ማድረግ ያልቻላቸውን፣ ሰዎች ያደረጉበትን፣ በሰዎች የተነሣ በኑሮው ላይ እንዴት ችግር እንደተፈጠረበት፣ ወዘተ.፡፡  ኢየሱስም በፀጥታ ይመለከተው ነበር፡፡ አንዳችም አስተያየት አልሰጠም፡፡ ዝም፡፡
“ጌታዬ እኔ ካንተ ጋር መኖር እፈልጋለሁ፡፡ እባክህን ሁል ጊዜ ናልኝ፡፡ ከእኔ አትለይ፡፡ እኔ ኮ ብቸኛ ነኝ…”
ችግሩን ዘርዝሮ፣ ዘርዝሮ፣ አልቅሶ፣ አልቅሶ ሲጨርስ ኢየሱስ ከመንገድ እንደመጣ ትዝ አለው፡፡
“ጌታዬ ወንበር ላይ አረፍ በል እንጂ፡፡” ብሎ ወደ ወንበሩ አመለከተውና “ቆይ ሻይ ላፍላ፡፡” ብሎ ወደ ማድቤት ሮጠ፡፡ ሻዩን ይዞ ሲመለስ በር ተንኳኳ፡፡
ኢየሱስም “ኦ! ዘመዶቼ መጡ፡፡ ታስገባቸዋለህ?” ሲል ጠየቀው፡፡
“ጌታዬ ያንተ ዘመዶች መጥተውልኝ? እንዴታ!” የሰውየው መልስ ነበር፡፡ በሩ ላይ ደርሶ እስኪከፍት ድረስ በልቡ ሐዋርያት፣ ሰማዕታት፣ እመቤታችን፣ ቅዱሳን፣ እጣን፣ ደመና፣ መላእክት ወዘተ. እያለ ኼደ፡፡ በሩን ሲከፍት ያያቸው ሰዎች ግን  ቡጭቅጭቅ ያለ ልብስ የለበሱ ወጣቶች፣ ጉስቁል ሕጻናት የታቀፉ የቆሸሹ እናቶች፣ የወገቦቻቸው አለልክ መጉበጥ ደጋፊ ማጣታቸውን የሚመሰክርላቸው ሽማግሌ፣ ወዘተ. ሆኑበት፡፡ አገጩ በድንጋጤ ቁልቁል ወደቀ፡፡ አስገባቸው፡፡ እንዴት እንደሆነ ሊገባው ባይችልም የተፈላው ሻይ ለሁሉም በቃቸው፡፡ ከሻዩ ጋር አብሮ የቀረበው አንድ ሳህን ቆሎም አላለቀም፡፡

Tuesday, April 3, 2012

አንድምታ (The Ethiopian way of Interpreting the Holy Bible)

ከቀደሙ ኢትዮጵያውያን አበው መካከል ቅዱሳት መጻሕፍትን እጅግ ከማፍቀራቸው የተነሣ ንባቡ አላጠግብ ቢላቸው ወደ ትርጓሜ ዘልቀው፣ በዓለም የነበረውን የቅዱሳት መጻሕፍት ዕውቀት መሠረት አድርገው እነርሱ ራሳቸው በትርጓሜ እየተራቀቁ፣ እየመጠቁ የሚጓዙ አበው ነበሩ፡፡ ከእነዚህ አበው የትርጓሜ ሥራዎች መካከል አንድምታ በመባል የሚታወቀው የትርጓሜ አካሄድ አንዱ ነው፡፡

ምንም እንኳ አንድምታ ምንጩ በልዩ ልዩ ሀገራት የነበሩ የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ቢሆኑና ለኢትዮጵያዊው ትርጓሜ እነርሱን መሠረት ቢያደርጉም ኢትዮጵያውያኑ ሊቃውንት እንዲሁ በመዋስ ብቻ ግን አልተወሰኑም፡፡ ይልቁንም እነርሱም ዕውቀታቸው ያራቀቃቸውን፣ እምነታቸው ያመጠቃቸውን ያህል መሠረቱን አስፋፍተውታል፤ አሳድገውታል፤ አምጥቀውታልም፡፡ ሆኖም ይህ የምጥቀት ጉዞው በአንዳንድ ምክንያቶች የተደናቀፈባቸው፣ የጫጨባቸው እንዲሁም የተገደለባቸው አጋጣሚዎችም ነበሩ፡፡ ከእነዚህም መካከል አንዱ ትርጓሜ በየጊዜው እያደገና እየሰፋ የሚሄድ ነገር ሳይሆን እንደጸሎት የሚደገም የማይሻሻልና የማይታረም እንደዶግማ ፍጹም ተደርጎ መቆጠሩ ነው፡፡ ለምሳሌ፡- እርሳቸው ራሳቸው የትርጓሜ መምህር የነበሩትና ዘመኑን የቀደመ ኢኩሜኒካል አስተሳሰብ የነበራቸው መጋቤ ብሉይ ሰይፈ ሥላሴ የሚከተለውን ጽፈው ነበር፡-

Thursday, March 29, 2012

ትምህርት ምን ያደርግልናል?


ቀጥሎ የቀረበላችሁ ጨዋታ ከባለ ቅኔው መንግሥቱ ለማ አባት ከአለቃ ለማ ኃይሉ የተገኘ ነው፡፡ ሙሉ ጨዋታቸውን “ትዝታ ዘአለቃ ለማ” ከተሰኘው መጽሐፍ ታገኙታላችሁ፡፡ የዚህ ጡመራ መታሰቢያነቱ እነርሱ ከሚያውቁት ውጪ ሌላ ዕውቀት ያለ ለማይመስላቸው፣ “መመራመር ብርቁ” ለሆኑ የዐውደ ምሕረትም ሆነ የዐውደ ዕውቀት “አስተማሪዎች” ይሁንልኝ፡፡  



ደጃች ኃይሉ የሸደሆ ገዥ፣ ደጃች ወንዴ ደግሞ የመቄት ገዥ ነበሩ፡፡ ደጃች ኃይሉ የተማሩ ሲሆኑ፣ ደጃች ወንዴ ግን አልተማሩም      ነበር፡፡ ደጃች ከጣቢሽ የተባሉት ደግሞ ሁለቱንም ግዛቶች በአንድነት ይገዙ ስለነበር የሁለቱም ደጃቾች የበላይ ነበሩ፡፡

ሁለቱ ደጃቾች ወደ ደጃች ከጣቢሽ ይሄዳሉ፡፡ ቤተክርስቲያኑ ጊዮርጊስ ነው፡፡ ሁለቱም በቤተክርስቲያን ተገኝተው ይጸልያሉ፡፡ ደጃች ኃይሉ ዳዊት አውጥተው ዳዊታቸውን ይደግማሉ፡፡ መልኩንና ይህን የመሰለውን ሁሉ በመጽሐፍ ይደግማሉ፡፡ ደጃች ወንዴ ደግሞ ትምህርት የሌላቸው ናቸውና “ቅዱስ ጊዮርጊስ የአባቴ አምላክ! ፈጥረህ የት ትጥለኛለህ?” እያሉ ያለ መጽሐፍ በቃል ይጸልያሉ፡፡ በኋላ ሁለቱም ተያይዘው ደጃች ከጣቢሽ ወዳሉበት ይወጣሉ፡፡ ከዚያ ደጃች ወንዴ “ደጃች ኃይሉ፣ መማር ለምን ይበጃል?” አሉ፡፡ ተንኮለኛ ነህ ለማለት ነው፡፡

ደጃች ኃይሉም “ቅዱስ ጊዮርጊስ ፈጣሪዬ! ከማለት ያድናል፡፡” ሲሉ መለሱላቸው ይባላል፡፡

Wednesday, March 21, 2012

አባቴን ሺኖዳን መሸኛዬ

መዝሙረ ፍጥረታት
ቀጥሎ የቀረበላችሁን መዝሙር የደረሰው አባት ለፍጥረታት በነበረው ልዩ ፍቅር የሚታወቀው ቅዱስ ፍራንቸስኮስ ይባላል፡፡ የተወለደው በአሥራ ሁለተኛው ክፍለ ዘመን መጨረሻ ሲሆን በአሥራ ሦስተኛው ክፍለ ዘመን በነበረው የቤተክርስቲያን እንቅስቃሴ ታላቅ ሚናን ከተጫወቱ ሰዎች አንዱ ነው፡፡

የዚህ የፍራንቸስኮስ ብሔረ ሙላዱ ጥንተ ነገዱ እንደምን ነው? ቢሉ እነሆ እጅግ በጣም በአጭሩ ይህን ይመስላል፡-
በ1182 ዓ.ም. (አንዳንዶች 1183ም ይላሉ) አሲሲ በምትባለው ዛሬ ጣልያን ውስጥ በምትገኘው ቦታ አንድ ፒየትሮ በርናርዶን የሚባል ሀብታም የጨርቅ ነጋዴ ወንድ ልጅ ተወለደለት፡፡ ይህ ልጅም ክርስትና ሲነሣ ጆቫኒ (ዮሐንስ) የሚል ስም ተሰጠው፡፡ አባቱ ግን ፍራንቸስኮስ ብሎ ሰየመው፤ የዚህም ምክንያቱ አባትየው ፈረንሳይን እጅግ አጥብቆ የመውደዱ ነገር እንደነበር ይነገራል፡፡

ቅዱስ ፍራንቸስኮስ የባዕለ ጸጋ ልጅ ሊያገኘው የሚችለው እንክብካቤና ምቾት ሁሉ ሳይጎድልበት ስላደገ ገንዘብ እንደውኃ መርጨት፣ መዝናናትንና መሽቀርቀርን ማዘውተር ተለይቶ የሚታወቅባቸው የወጣትነት ጠባዮቹ ነበሩ፡፡ ታሪኩን የጻፉልን አበው እንደሚናገሩት የወጣትነት ዘመኑን የመጀመሪያ ዓመታት ያየ ማንም ሰው “ፍራንቸስኮስ ቅዱስ ይሆናል፡፡” ብሎ አይጠብቅም ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ያኔም ቢሆን ለድኾች እጅግ የምታዝን ርኅርኅት ልብ ባለቤት እንደነበረው ሳይጠቅሱ አያልፉም፡፡

Tuesday, March 13, 2012

ጾም ምንድናት?



ዛሬ የማካፍላችሁን ትምህርት ያገኘሁት “ማር ይስሐቅ” ከተሰኘው ባለፈው ጊዜ ስለ ንስሐ፣ ፍቅርና ፈሪሃ እግዚአብሔር ከተማርንበት መጽሐፍ ነው፡፡ ጊዜው የጾም ወቅት ስለሆነ በእኛ በምሥራቃውያን ክርስቲያኖች ዘንድ ደግሞ የጾም ትውፊት እጅግ ይከበራል፡፡ ይህም ጥሩ ልምምድ ነው፡፡ ነገር ግን ጾምን የምንጾመው አባቶቻችን ሥርዓቱን ስለሠሩት ብቻ የምንፈጽመው ግዴታ አድርገን መሆን የለበትም፡፡ አንዳንዶቻችን “ጾም ሳይገባ እንብላ! እንጠጣ!” ብለን የምናካሒደው የቀበላ ሰሞን የግጦሽ ዘመቻ፣ አንዳንዶቻችን ደግሞ ጾም ላለመጾም የምናካሒደው የምክንያት ድርደራና የቅድስተ ቤተክርስቲያንን ትእዛዝ ያለመፈጸም ሽሽት ጾምን ጥቅሟን እንደማናውቅ ይመሰክርብናል፡፡ አንዳንዶቻችን ደግሞ አንደበቶቻችንን ለመቆጣጠር አንዳችም ጥረት ሳናደርግ፣ በምላሳችን የሰዎች ቁስል ላይ ጥዝጣዜን እየጨመርን፣ ፍርድ እያጓደልን፣ ሠራተኞቻችንን እየበደልን፣ ጉቦ እየበላን፣ ሚዛን እያጭበረበርን፣ “በርበሬ ነው፡፡” ብለን ሸክላ እያቀረብን፣ “ቅቤ ነው፡፡” ብለን ሙዝ እየሸጥን፣ በንግድ ስም በአልጠግብ ባይነት ከሚገባን በላይ ትርፍን በመፈለግ ድኃውን እየመዘበርንና እያስጨነቅን ለተወሰኑ ሰዐታት ከምግብ በመከልከላችን ብቻ ጾምን በጥሩ ሁኔታ እየጾምን እንደሆነ እናስባለን፡፡[i] ባጠቃላይ ስናየው ይህ ሁሉ የሚያመለክተው ወደአንድ አቅጣጫ ነው- የጾምን ምንነትና ጥቅም አለማወቃችንን፡፡ 

ስለሆነም ጥቅሙን ዐውቀን ስለምን እንደሆነ እንድንረዳ ስለጾም ምንነት ከአበው ትምህርቶች ጥቂት ፍርፋሪ ብንቀማምስ ለነፍሳችን ጥሩ ስንቅ ይሆነናል፡፡ ቀጥሎ የምናነበውን ትምህርት የምናገኘው “ማር ይስሐቅ” ላይ ነው፡፡ እርግጥ ነው “ማር ይስሐቅ” የተጻፈው በዐቢይነት የመነኮሳትን ሕይወት ለመምራትና ለማረቅ መኾኑ አይካድም፤ ይህ በራሱ ግን ያልመነኮሱና የማይመነኩሱ ሰዎች ሊያገኙበት የሚችሉትና ሊያገኙትም የሚገባቸው ትምህርት የለም አያሰኝም፡፡ በተለይም ደግሞ ክርስትና ራስን የመግዛት ሕይወት ስለሆነ ከመነኮሳት ኑሮ በርግጥ ብዙ የምንማረው ይኖረናል፡፡ ልንማርም ይገባናል፡፡ መጽሐፍ “ተሰአሎ ለአቡከ፤ ወይነግረከ፡፡” (ዘዳግ. 32፣7) (አባትህን ጠይቅ ይነግርህማል፡፡) ይል የለምን?

እነሆ! የአንድ ሺህ ስድስት መቶ ዓመቱ አረጋዊ መጽሐፍ ማር ይስሐቅ አንቀጽ 4 ምዕራፍ 6 ላይ እንዲህ ይላል[ii]፡-

ጥያቄ፡- በክርስትና ሕይወት ተጋድሎ ለመጀመር የሚፈልግ ሰው ሥራውን በምን ይጀምራል?
መልስ፡- ይህማ በሁሉ ዘንድ የታወቀ ነው፡፡ ሰው በሥጋው በኩል የምትዋጋውን የኃጢኣትን ጦር ድል ለመንሣት፣  ፍትወትንም ከእርሱ ለማራቅ በሚያደርገው ተጋድሎ በቅድሚያ የምትመጣው የመታገያ መንገድ በጾም ሥጋን ማድከም ናት፡፡ ዕንቅልፍን ቀንሶ በሌሊት ለጸሎት መትጋትም እንዲሁ ጾምን የምታግዝ መሣሪያ ናት፡፡ በዘመኑ ሁሉ እነዚህን የሚጠብቅ ሰው ንጽሕናን ገንዘቡ ማድረጉ አይቀርም፡፡ ጥጋብ የክፉ ሥራ መጀመሪያ እንደሆነች ሁሉ የዕንቅልፍ ብዛትም ሥጋዊ ፍላጎትን ያበረታዋል፡፡ ስለዚህም ከዕንቅልፍ ቀንሶ ጸሎት ማድረግና ቅዱሳት መጻሕፍትን ማንበብ ደግሞ በምግባር በትሩፋት ለማደግ ጥሩ መሠረት ይሆናሉ፡፡

ጾም የምግባር የትሩፋትን ሥራ ሁሉ ለመሥራት ታነቃቃለች፡፡ እርሷ እንደ ትጉኅ ገበሬ ራሳቸውን ለክርስቶስ ጠምደው ለሚኖሩ አክሊላቸው ናት፡፡ ዳግመኛም በክርስትና ሕይወት ለሚደረግ ተጋድሎ መጀመሪያ፣ ስለኃጢኣታችንና ስለወገኖቻችን ልናወርደው የሚገባንን እንባ የምናገኝባት የጸሎት ምንጭ፣ የድንግልናና የንጽሕና ጌጣቸው፣ የንጽሕና መገለጫ፣ የወንጌል ሥራ መጀመሪያ፣ አርምሞን የምታስተምር ናት፡፡

ጤነኛ ዓይኖችን ዘወትር ብርሃን ማግኘት እንደሚስማማቸው ሁሉ ትክክለኛ ጾምም ጸሎትን ማዘውተር ይስማማታል፡፡ ሰው ጾም በጀመረ ጊዜ ኅሊናው በጸሎት ከእግዚአብሔር ጋር መነጋገር ይጀምራል፡፡ ከዕንቅልፉ ቀንሶም ይጸልያል፡፡ ሰው አብዝቶ አፉን በጾም ከምግብ የከለከለውን ያህል በዚያው መጠን በትሕትና ሁኖ እያለቀሰ መጸለይን ገንዘቡ ያደርጋል፡፡[iii]  ጸሎታትም ከልቡናው ይታሰባሉ፡፡ ልቡ ጸሎታትን በማሰላሰል ይጠመዳል፡፡ በፊቱ ላይም ትዕግስት ትነበባለች፡፡ ስለኃጢኣቱ ያዝናል፡፡ ክፉ ሐሳቦችም ይርቁለታል፡፡ ከንቱ ንግግርም ትሸሸዋለች፡ 

ጾም የበጎ ምግባራት ግምጃ ቤት ስለሆነች ሰይጣን ከበጎ ምግባራት እንድንርቅ ሊያደርገን ሲሻ በቅድሚያ የሚያደርገው እርሷን እንድንንቅና እንድናቃልል መጋበዝ ነው- ምክንያቱም የጾምን ምንነቷን ዐውቆ ጥቅሟን ተረድቶ የሚጾማት ሰው የበጎ ነገሮች መከማቻ በሆነች ቤት ውስጥ ይኖራልና ከሥጋ፣ ከዓለምም ሆነ ከሰይጣን ለሚመጡለት የክፉ ፈቃድ ጥሪዎች አይገዛም፡፡ በዚህም የተነሣ ጾምን የሚያቃልል ሰው በፈቃዱ በጎውን ነገር ሁሉ ከራሱ አራቀ፡፡ አዳምን “ከእርሷ እንዳትበላ!” ብሎ በማዘዝ እርሷ እኛን ለክፉ ፈቃድ ከመገዛት እንድትጠብቀን እኛም እርሷን በመታዘዝ እንድንጠብቃት ከጥንት ጀምሮ ከፈጣሬ ዓለማት ተሰጥታናለችና፡፡

የሁላችን አባት አዳም እርሷን ባለመጠበቁ በሰይጣን ድል ተነሣ፡፡ እርሱ በመብላቱ ስለተሸነፈም ቅዱሳን ነቢያት ሁሉ ከሥጋ፣ ከዓለምና ከሰይጣን ክፉ ፈቃዳት ጋር በመጣላት ሕጉን ለመጠበቅ ያደረጉትን መጋደል በጾም ጀምረው ፍጹም ወደሆነው ፈሪሃ እግዚአብሔር ደረሱ፡፡ ክብር ይግባውና ጌታችን በዚህ ዓለም በተገለጠ ጊዜም ሥራውን በጾም ጀመረ፡፡ እርሱን ለመምሰል የፈቀዱ ቅዱሳንም ሁሉ ጾምን የገድላቸው መጀመሪያ አደረጓት፡፡ እርሷ ከልዑል እግዚአብሔር የተሰጠች ጋሻ ናትና ጾምን የሚንቅና የሚያቃልል ሰው ተግሣፅ ይገባዋል፡፡

ትእዛዝን የሰጠ፣ ሕግን የሠራ እግዚአብሔር ወልድ ኢየሱስ ክርስቶስ ከጾመ ሕግን ለመጠበቅ ከሚፈቅዱ ሰዎች መካከል ጾምን ሊወድዳት የማይገባው ማን ነው? በዘመነ ብሉይ ጌታ ስላልጾማት የሰው ልጆች ጾም በሰይጣን ላይ ፍጹማዊ የበላይነትን አልተቀዳጀችም ነበር፡፡ በዘመነ ሐዲስ ግን ክብር ይግባውና ለአዳም ካሣ ሊሆነው የመጣለት ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ አዳም ያልተጠቀመባትን ይህችን ሰማያዊ የጦር ዕቃ ጾምን አንሥቶ ሰይጣንን ተበቅሎልናል፡፡ በዚህም እርሱ ኢየሱስ ክርስቶስ የሐዲስ ኪዳን ገዳማዊ ሥርዓትን ለመጀመር በኵር ሆነ፡፡ ሰይጣንንና ክፉ ፈቃዳትን ለመዋጋትና ድል ለማድረግም በኵር ሆነልን፡፡ እነሆም በሰይጣን ተሸንፎ ወድቆ፣ ተጥሎ ለነበረ እኛነታችን የማሸነፍን አክሊል አቀዳጀ፡፡

ስለዚህም ዛሬ ሰይጣን ከሰው ልጆች መካከል አንዱን እንኳ ለጾም ሲጠመድ ሲመለከተው እጅግ ይፈራል- ጌታ በጾም እንዴት ድል እንደነሣው ያስታውሰዋልና፡፡ ከሊቀ ካህናታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ በተሰጠችን በጾም የሰይጣንና የመሣሪያዎቹ የክፉ ፈቃዳት ኃይላቸው ይደክማል፡፡ አቤት! ጌታ እንዴት ያለ ድንቅ ምክር ሰጠን! ከአጋንንት ጋር ለመዋጋት ለልቡና ጽንዓትን የሚሰጥ እንደዚህ የጦር ዕቃ (እንደ ጾም) የሚበረታ ሌላ የጦር ዕቃስ ወዴት ይገኛል? የሰው ልጅ ክብር ይግባውና ክርስቶን ለማገልገል በመራብ ሥጋው በጾም በደከመ መጠን የዚያኑ ያህል አጋንንትን ጸንቶ ይዋጋል፡፡ ድል ያደርጉኛል ብሎም አይፈራም- የሚዋጋው ድል ከተነሣ ጠላት ጋር ነውና፡፡

ጾምን ፈጽመህ ውደደው!                                   
ጾምን የናቀና ያቃለለ ሰው ሌላውን ትሩፋት ከመሥራት ቸል ይላል፤ ይደክማል፡፡ በስንፍና ምልክትነቷም ኃጢኣትን ወደ ሰውነቱ መርታ ታደርሳታለች፡፡ ኃጢኣትም ነፍሱን በመውጊያዋ ታቆሳስላታለች- የጦር ዕቃ ሳይይዝ ወደ ጦር ሜዳ ሔዷልና፡፡ ዳግመኛም፣ ፈተና በሚመጣበት ጊዜ የሚጸናበትን፣ ከፈተና ጦር የሚጠበቅበትን ከእግዚአብሔር ለሰው ልጆች የተሰጠችንን ጋሻ ጾምን አልያዘምና ከሚነሣበት ፈተና የተነሣ የጀመረውን ክርስቶስን የመምሰል ገድል አቋርጦ ይሸሻል፡፡

አንተ ግን ሰማዕታትን ምሰላቸው፡፡ እነርሱ የምስክርነት አክሊል የሚቀበሉበትን (ማለትም ስለክርስቶስ ሲሉ የሚገደሉበትን) ቀን ካወቁ በዚያች ሰማዕትነትን በሚቀበሉባት ቀን አንዳች ምግብ ሳይቀምሱ ሰማዕትነታቸውን በጾም ይቀበሏት፣ ይጠባበቋት ነበር ይባላል፡፡ ከጾሙ ጋርም ጸሎትን አብዝተው ያደርሱ፤ ወደ ሠርግ እንደሚሔድ ሰውም በምሥጋና፣ በደስታና በሐሴት ወደ ሰማዕትነታቸው ይጓዙ ነበር፡፡

ክርስቲያን በመሆን “እናንተ የአባቴ ቡሩካን በወደ እኔ ኑ!” የሚለውን ቃል ለመስማት የታጨን እኛም እንግዲህ ይህንን የሕይወት ቃል ለመስማት ንቁዎች ሁነን ልንኖር፣ ለጠላቶቻችን ለአጋንንትም በሕይታችን ላይ መንገድ እንዳንሰጥ ልንጠነቀቅ፣ ከአካል ክፍሎቻችን አንዱም ቢሆን ክፉ ሥራ የሚያስብበትን ምልክት እንዳንሰጠው ልንጠበቅ ይገባናል፡፡


“ንዑ ኀቤየ ቡሩካኑ ለአቡየ!” የሚለውን የሚያረጋጋ ድምጹን ለመስማት
የበቃን፣ የነቃን፣ የተጋን ያደርገን ዘንድ ልዑል እግዚአብሔርን
በአንድ ልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ
እንለምነዋለን፡፡
    አሜን፡፡


[i] እንደእኔ አመለካከት ከእንደዚህ ዓይነቱ “ጾም” መሰል ረኃብ ይልቅ አንዳንድ ፖለቲከኞችና የሰብአዊ መብት ታጋዮች የሚያካሒዱት የረኃብ አድማ ሳይሻል የሚቀር አይመስለኝም- የእነርሱ ቢያንስ አንድን ምድራዊ ዓላማ ለማሳካት ሲሉ የሚያደርጉት ነውና፡፡ እግዚአብሔር በነቢዩ ኢሳይያስ አንደበት (ትን. ኢሳ. 58) እንዲህ ዓይነቱን ግፍ እየሠሩ የሚጾም ጾም እንደማይቀበለው በግልጥ ነግሮናል፡፡

[ii] እንደተለመደው ኣማርኛውን ለተነሣንበት ዓላማ እንዲሆን አለዛዝቤዋለሁ፡፡

[iii] አንዳንዶቻችን የምናደርገውን “ቢራ ጾም የለውም ወይስ አለው?” “ዓሳ ጾም የለውም ወይስ አለው?” እያልን የምናደርገውን ጉንጭ አልፋና ጥቅም አልባ ክርክር ትተን እንደነቢዩ ዳንኤል ኃጢኣታችንንና የሕዝቡን ሁሉ ኃጢኣት እያሰብን “ኃጢኣት ሠርተናል፤ በድለንማል፤ ክፋትንም አድርገናል፤ ዐምፀንማል፤ ከትእዛዝኽና ከፍርድኽም ፈቀቅ ብለናል፡፡” በማለት ልንጸልይ ይገባናል (ትን. ዳን. 9፣ 5)፡፡ ሆዳችን ከመራቡ በፊት ልባችን እግዚአብሔርን ለማግኘት መራብ አለባት- ልባችን እግዚአብሔርን ሳይራብ ልማድ እንዳይቀርብን ብቻ የምናደርገው ጾም ለነፍሳችን የሚያተርፈው ነገር እምብዛም ነውና፡፡

Monday, February 27, 2012

“ከማያውቁት መልአክ የሚያውቁት ሰይጣን ይሻላል”

የዛሬው ወሬዬ መሠረት የሚያደርገው “The Road Less Travelled” ከተሰኘው መጽሐፍ ያገኘሁትን ትምህርት ነው፡፡ የዚህ መጽሐፍ ደራሲ ስኮት ፔክ የሚባል ሳይኮቴራፒስት ሲሆን ከጻፋቸው መጻሕፍት ውስጥ እንደዚህኛው የተወደደለት የለም ይባላል- 10000000 ቅጂ ተሸጦለታል፡፡

እንደስኮት ፔክ አባባል ብዙዎቻችን ለበጎ ነገር ሰነፎች ነን፡፡ በዚህም የተነሣ በጎ ነገር መሆኑን ብናውቅም እንኳ አዲሱን በጎ ነገር ከማድረግ ይልቅ በለመድነው መጥፎ ነገር ውስጥ መዘፍዘፍ ይመቸናል፡፡ በሱስ ተጠምደን ሱሱ ሥነልቡናዊ ጤንነታችንን፣ አካላዊ በጎነታችንን፣ ቤተሰባችንን፣ ሥራችንን፣ ማኅበራዊ ኑሯችንን ወዘተ. እያቃወሰው፣ እየበጠበጠው እያየንና ጉዳቱም በእጅጉ እየተሰማን፣ ሱሱን ማቆም እንዳለብንም እያወቅን ሱሱን ለማቆም ግን እንሰንፋለን፡፡ ሱሱን ለማቆም ልናደርጋቸው የሚገቡ ነገሮችን ሁሉ ስናስባቸው ዳገት ይሆኑብናል፡፡ ውጤቱ ጥሩ መሆኑን ብናውቅም ልፋቱን ላለመልፋት ድካሙንም ላለመድከም ሳንጀምረው እንዝላለን፡፡ በለውጥ ሒደት ላይ ከመንገላታት ይልቅ እንደደረቀ ግንድ እየበሰበስን፣ ምሥጥ እየበላን ባለንበት መገተርን እንመርጣለን፡፡

ታማሚዎች ሆነን ጤናችን ሴቻና ሲቀላ እየረገጠ ሲያስቸግረን የታዘዘልንን መድኃኒት ወስዶ መጨረሱ አቀበት ይሆንብናል፡፡ በመድኃቱ ፍጻሜ ከምናገኘው ጤንነት ይልቅ በመድኃኒቱ ምሬት፣ ወይም መጎምዘዝ፣ ወይም መብዛት እንማረራለን፡፡ ተማርረንም እንተወዋለን፡፡

Friday, February 24, 2012

ዝም


ዛሬ የማካፍላችሁ ግእዝ፣ ዕብራይስጥ፣ ጽርእ (ግሪክ)፣ ላቲን፣ ጣልያንኛ፣ ጀርመንኛ፣ ፈረንሳይኛ፣ እንግሊዘኛ፣ ግእዝና አማርኛ ከሚያውቁት፣ መጽሐፍ ቅዱስን በጉንጫቸው የያዙ የሚመስሉት ግን ትሑት መንፈሳቸው የኔ መምህር ካደረጋቸው የዋኅ መምህሬ የሰማሁትን ነው፡፡

አይሁዳውያን በሒትለር በሚመራው የናዚ ፓርቲ የደረሰባቸውን ጭፍጨፋ ዓለም “Holocaust” ብሎ ይጠራዋል፡፡ የቃሉ መነሻ ግሪክ ሲሆን ትርጉሙም በአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ “የሚቃጠል መሥዋዕት”፣ በእንግሊዘኛ (Burnt offering) ተብሎ የሚጠራውን አንድም ተረፍ ሳይኖረው ሙሉ በሙሉ በመቃጠል ለአዶናይ ይቀርብ የነበረውን የብሉይ ኪዳን መሥዋዕት ያመለክታል፡፡   


ናዚዎችም አይሁዳውያንን እንደ መሥዋዕቱ ብን ብለው ከገጸ ምድር እንዲጠፉ ለማድረግ ነበርና ዓላማቸው ዓለም የሰጠው “Holocaust” የሚለው ስም ተገቢ ይመስላል፡፡ ጽዮናውያኑ ግን በዚህ አይስማሙም፡፡ መሥዋዕት ከሰው ለአምላክ የሚቀርብ ነገር ነው፡፡ በእኛ ላይ የደረሰውን ግን እንኳን እንደመሥዋዕት የሚቀበል አምላክ እንደሰው የሚያስብ ሰው እንኳ ምክንያት ሊሰጥለት የሚችለው ነገር አይደለም፡፡ ስለዚህም በእኛ ላይ የደረሰውን ግፍና መከራ፣ ሰቆቃና ሐዘን ሊገልጽ የሚችል አንድም ቃል የለም ይላሉ፡፡ ነገር ግን የደረሰባቸውን ሁሉ አንድ ቃል ጠቅልሎ እንዲወክልላቸው መርጠውታል፡፡ ይኸውም “ሸቫ” ወይም “ሸዋ” ይባላል፡፡ ትርጉሙም “ዝምታ፣ ጸጥታ” ማለት ነው፡፡ በቃ የደረሰባቸውን ሁሉ፣ አንዳች ወንጀል ሳይሠሩ መሳደዱን፣ መታሰሩን፣ መታጎሩን፣ በመርዝ ጭስ ታፍኖ መገደሉን፣ በሚቆማምጥ ብርድ በረኃብ አለንጋ መለብለቡን፣ የሽማግሌውን መጣል፣ የአሮጊቷን መፈጥፈጥ፣ የእርጉዚቱን መቀደድ፣ የጨቅላውን መጨፍለቅ ወዘተ. “ዝም” ብለው ሰየሙት፡፡ ለካ ዝምታም ይናገራል፡፡ ዝም፡፡


Thursday, February 23, 2012

የቤተሰብ መርገም


ዛሬ ከግሪክ ሚቶሎጂ አንድ ተረክ እንቆንጥር፡፡

በድሮ ጊዜ አንድ አትሬዉስ የሚባል ሰው የግሪክ አማልክትን በኃይል ለመብለጥ ይገዳደራል፡፡ በዚህም የተነሣ አማልክቱ ተቆጥተው የእርሱ ውላጆች በሙሉ ሕይወት የቀናች እንዳትሆንላቸው “አትሬዉስና ቤቱ የተረገሙ ይሁኑ!” የሚል እርግማን አስተላለፉ፡፡[i] ይህ እርግማን በትዕቢቱ ያስቆጣቸውን አትሬዉስን ብቻ ሳይሆን ልጆቹንና የልጅ ልጆቹን ሁሉ የሚመለከት ነበረ፡፡  

ጊዜ ነጎደ፡፡ እርግማኑም ተረሳና ከአትሬዉስ ልጆች መካከል አንዱ የሆነው አጋሜምኖን ክሊቴምኔስትራ ከምትሰኝ ሴት ጋር በፍቅር ይወድቃል፡፡ በመጨረሻም ያገባትና ኦሬስተስ የተባለ ልጅ ይወልዳሉ፡፡ ይህቺ ክሊቴምኔስትራ ግን በልጇ አባት ላይ ሌላ ሰው ወሸመችበት፡፡[ii]  መወሸሙም ሳይበቃት አጋሜምኖን ከጦርነት ሲመለስ ከውሽማዋ ጋር ተባብራ ገደለችው- የልጇን አባት! እርሷ ለውሽማዋ ፍቅር ብላ አጋሜምኖንን ስትገድል እርግማኑን ወደልጇ ማተላለፏን አላየችም፡፡ የአፍቃሪ ነገር! ያውም የውሽማ ፍቅር ችግር እኮ ነው፡፡ አማልክቱ ይህንን ሁሉ ከኦሊምፐስ ተራራ ላይ ተጎልተው ይመለከታሉ፡፡ እርግማናቸው በመሥራቱም “ቺርስ!” እየተባባሉ አማልክታዊ ጽዋቸውን ይቀባበላሉ፡፡ አባትየው ላይ የወደቀው እርግማን በገዛ ሚስቱ በመገደል ሲጠናቀቅ ያልተባረከ ሕይወት የመመምራት አማልክታዊው እርግማን ግን ወደ ልጁ ወደ ኦሬስተስ ተላለፈ፡፡

ኦሬስተስ እናቱ የፈጸመችውን ይህንን ወንጀል ሲያውቅ ነፍሱ አጣብቂኝ ውስጥ ወደቀች፡፡ ከፊቱም ሁለት አማራጮች ብቻ ቀረቡለት፡፡ አማራጭ አንድ በግሪኮች ባህል ወንድ ልጅ የአባቱን ገዳይ መግደል አለበት፡፡ አማራጭ ሁለት አንድ ግሪካዊ ሊፈጽማቸው ከሚችሉ ኃጢኣቶች ሁሉ እጅግ ከባዱ የገዛ እናቱን መግደል ነው፡፡[iii]

የአባቱን ገዳይ አለመበቀል ከባድ ነውር ነው፡፡ የወለደችውን እናቱን መግደልም ታላቅ ኃጢኣት ነው፡፡ ምን ይሻላል? ኦሬስተስ ብዙ ካወጣና ካወረደ በኋላ የመጀመሪያውን አማራጭ በመውሰድ የአባቱን ደም ለመበቀል የወለደችውን እናቱን ሲጥ አደረጋት፡፡ እርግማኑ ሠራ! አማልክቱ አሁንም ተደስተው “ቺርስ!” ተባባሉ፡፡

Thursday, February 16, 2012

ዓለምን ሁሉ ለመለወጥ


እነዚህ ቃላት በአንድ የአንግሊካን ቤተክርስቲያን ጳጳስ በነበሩ ሰው መቃብር ላይ ተጽፈው የተገኙ ናቸው፡፡
በጉርምስናዬ ጊዜ ሐሳቤ ወሰን አልነበረውምና ዓለምን ሁሉ ለመለወጥ አስብ ነበር፡፡ እድሜዬና ብስለቴ እየጨመረ ሲመጣ ዓለምን መለወጥ እንደማይቻል ተገነዘብሁ፡፡ ስለዚህም ግቤን ጠበብ አድርጌ ሀገሬን ብቻ ለመለወጥ ወሰንሁ፡፡
ነገር ግን እርሷም ጨርሶ የምትለወጥ አልሆነችም፡፡
የጉልምስናዬ ወራት ካለፈ በኋላ ቤተሰቤንና በቅርቤ ያሉትን ሰዎች በመለወጥ ላይ አተኮርሁ፡፡ ይሁን እንጂ ይህም ውጤት አልባ ነበረ፡፡
አሁን በሞት ልጠቀለል ጥቂት በቀረኝ ሰዐት በድንገት የሚከተለውን እውነታ ተረዳሁ፡፡

መጀመሪያ ራሴን ለውጬ ቢሆን ኖሮ፣ ቤተሰቤ የእኔን ምሳሌ ተከትሎ በተለወጠልኝ፤ በቤተሰቤ ውስጥ         ባገኘሁት ለውጥ አነሳሽነትና አበረታችነትም ሀገሬን ማሻሻል በቻልሁ ነበረ፡፡ ማን ያውቃል?! ይሄኔ ዓለምንም ለውጬ ይሆን ነበር፡፡    ነበረ፡፡ ነበረ፡፡ ነበረ...
   

It is blessed to give than to receive.


A friend of mine named Paul received an automobile from his brother as a Christmas present. On Christmas Eve when Paul came out of his office, a street urchin was walking around the shiny new car, admiring it. “Is this your car, Mister?” he asked.
Paul nodded. “My brother gave it to me for Christmas.”
The boy was astounded. “You mean your brother gave it to you and it didn’t cost you anything? Boy, I wish…” He hesitated.
Of course Paul knew what he was going to wish for. He was going to wish he had a brother like that. But what the boy said jarred Paul all the way down to his heels.
“I wish,” the boy continued, “that I could be a brother like that.”
Paul looked at the boy in astonishment, and then impulsively added, “Would you like to take a ride in my automobile?”
“Oh Yes, I would love that.”
After a short ride, the boy turned and with his eyes aglow, said, “Mister, would you mind driving in front of my house?”
Paul smiled a little. He thought he knew what the boy wanted. He wanted to show his neighbors that he could ride home in a big automobile. But Paul was wrong again.
“Will you stop where those two steps are?” the boy asked.
He ran up the steps. Then in a little while Paul heard him coming back, but he was not coming fast. He was carrying his little crippled brother. He sat him down on the bottom stem, then sort of squeezed up against him and pointed to the car.
“There she is, Buddy, just like I told you up stairs. His brother gave it to him for Christmas and it didn’t cost him a cent. And some day I am going to give you one just like it… then you can see for yourself all the pretty things in the Christmas windows what I have been trying to tell you about.”
Paul got out and lifted the disabled boy to the front seat of his car. The shinning- eyed older brother climbed in beside him and three of them began memorable holiday ride.
That Christmas Eve, Paul learned what Jesus meant when he had said: “it is more blessed to give than to receive” (Acts 20: 35)  

(This is not fiction. It is a true story.)

Source:- Chicken soup for the soul

Monday, February 13, 2012

የት አባቴ ኼጄ ልረፍ?

ሞባይሌን ተመለከትሁት የሳምንቱ ቅዳሜ አስራ አንደኛው ሰዐት ካለፈ ሠላሳ ደቂቃዎች መሆናቸውን ነገረኝ፡፡ የመጨረሻዋ ባለጉዳይ ገባች፡፡ መሥርያ ቤቴ ለደንበኞቹ ያዘጋጀውን ቅጽ መሙላት ጀመርሁ፡፡

“ስም”
ተናገረች፡፡ ፊቷ ላይ የፓውደር የከተራ በዓል በደመቀ ሁኔታ እየተከበረ አየሁት፡፡ ስሟን ሞላሁ፡፡ መሥሪያ ቤቴ ያዘጋጀውን ባለ ሦስት ገጽ ቅጽ ሞልቼ ጨረስሁ፡፡ ደስ ብሏት ከቢሮዬ ወጣችልኝ፡፡ እፎይ! ግልግል፡፡ ጠረጴዛ ላይ ጎብጦ ቀኑን ሙሉ ባለ ጉዳዮች በአምሳለ ጢስ ከብበውት የዋለው ትከሻዬ ላይ ቆረጠመኝ፡፡ ለነገሩ በቀን የአራት መቶ ሰው ቅጽ ሞልቼ ባይደክመኝ ይገርማል፡፡ የወጣልኝ ልማታዊ ሠራተኛ ነኝ፡፡

ረኀብ ሆዴን እንደ ድመት ይቧጥጠኝ ጀመር፡፡ ከቢሮዬ ምንጥቅ ብዬ ወጣሁ፡፡ እራቴን የመሥራት ጥንካሬው ስላልነበረኝ ጁስ ቤት ገብቼ አምባሻና ጭማቂዬን ላስኩና (መቼም በላሁ አይባል ነገር) በየወሩ የደመወዜን ግማሽ ወደምሰዋላት ቤቴ ማዝገም ጀመርሁ፡፡ ሰፈራችን መግቢያ ላይ ከክሊኒኩ ጎን ሦስት ሰዎች የሆነ ማስታወቂያ እየተከሉ ነው፡፡ አነበብሁት፤ “የዛሬው ትውልድ ቤተክርስቲያን Today’s Generation Church” ይላል፡፡ ግቢዬ በር ላይ ስደርስ የግማሽ ደመወዜን መሥዋዕት ተቀባይ እማማ እልፍነሽን አገኘኋቸው፡፡ ነጭ በነጭ ለብሰዋል፡፡ የሆነ ትራስና ጋቢ ነገር በቅርቡ ከገጠር ያመጧትንና አሁን በነጠላ የጠመጠሟትን ልጅ እግር ዘመዳቸውን በፌስታል አስይዘዋል፡፡ ትዝ አለኝ፡፡ ነገ ገደል አፋፍ ላይ የተሠራው ቤተክርስቲያን ወርኀዊ በዓል አለ፡፡ ወደዚያው እያዘገሙ እንደሆነ ገባኝ፡፡

በነገራችን ላይ እሱን ቤተክርስቲያን ለምን እዚያ ገደል ላይ ማነጽ እንዳስፈለገ ሁሌም እንቆቅልሽ ይሆንብኛል፡፡ ቤተክርስቲያን ጠፍቶ ነው እንዳይባል ከእርሱ በተቃራኒ አቅጣጫ በሁለት መቶ ሜትር ያህል ርቀት ላይ ሌላ ጥንታዊ ትልቅና በእምዬ ምኒልክ ጊዜ ከሰፈሩ ጋር አብሮ እንደተተከለ የሚነገርለት ቤተክርስቲያን አለ፡፡ አንድ ወቅት ስጠይቅ “ጠበል ፈልቆ ስለተገኘ ነው፡፡” የሚል ምላሽ አግኝቻለሁ፡፡ “ታዲያ ጠበሉን በጥንታዊው ቤተክርስቲያን ጥበቃና አገልግሎት ሥር ማድረግ አይቀልም ነበር?” ብዬ ስጠይቅ “ምነው ጥያቄ አበዛሽ?” የሚል የድምጽ ቁንጥጫ ቀመስሁ፡፡ ድምጻዊ ቁንጥጫው ወደ ዱላዊ ተግሣጽ ከማደጉ በፊት “ዝምታ ወርቅ ነው፡፡” የሚለውን ምሳሌያዊ አነጋገር ከድሮ የአማርኛ ደብተሬ ላይ አስታውሼ ራሴን አዳንሁ! (መማር ደጉ!)   
 
“እንደምን ዋሉ እማማ እልፍነሽ?
“ደኅና፡፡ ዚሃር መስጌን፡፡ ምነው ባክሽ ምነው ሌሊቱን ሙሉ መብራቱን ስታቃጥዪው ማደርሽ?
ውይይይይይይ! እኚህ ሴትዮ! የሚያከራዩዋቸውን ቤቶች 24 ሰዐት በመቆጣጠራቸውና በየሦስት ወሩ ኪራይ በመቀጠላቸው ወደፊት “ሞዴል ኪራይ ሰብሳቢ” ተብለው እንደሚሸለሙ ጥልቅ እምነት አለኝ፡፡
“የውልዎት እማማ እልፍነሽዬ በዚህ ሳምንት ትንሽ ፈተና አለችብኝ፡፡ ለዚያ ነው፡፡ ትንሽ ላጥና ብዬ፡፡ እስከ ስድስት ሰዐት…”
አላስጨረሱኝም፡፡ “ኤዲያ! ኤዲያ! ምነው እልፍነሽ!”

ዓይኖቻቸው ቆዳዬን እንደቅርፊት ከላዬ ላይ ገሸለጡት፤ ከፌስታል ነጻ የሆነ እጃቸውን በጄኪቻንኛ ይሁን በጄትሊኛ ባይገባኝም ፊቴ ላይ አወነጫጨፉብኝ፡፡ ቀድሞውንም ያልያዝሁትን መንገድ በቶኖች በሚለካ ትሕትና ለቀቅሁላቸው፡፡ ጋቢያቸውንና ነጠላቸውን በቁጣ ተጎነጻጽፈውብኝ ከባዱ ሰውነታቸው ወደፊት እየገፋቸው ኼዱ፡፡ እፎይ… ቤቴ ገባሁ፡፡ ጫማዬንና ልብሶቼን ገና ከበር ማውለቅ ጀምሬያለሁ፡፡ አንሶላ በመግለጥ ጊዜዬን ማባከን አልፈለግሁም፡፡ ከሁለት ወራት በፊት በአዲስ አበባ ምሕረት አልባ ብርድ ስሰቃይ ያየችኝ እናቴ የገዛችልኝን ወፍራም አልጋ ልብስ እንደጋዜጣ ተጠቀለልሁበትና በደረቴ ተዘረጋሁ! ከእኛ ግቢ ቀጥሎ ካለው ቡና ቤት “አድራሽ መላሽ አገልጋዬ” የሚለው የዘሪቱ ዘፈን ይሰማኛል፡፡ ዕንቅልፍ ይወስደኝ ጀመር፡፡ እፍፍፍፎይ!

“አላህ ወአክበር!” 
ከቤተክርስቲያኑ ጎን ያለው መስጊድ ደማቅና ማስጠንቀቂያ መሰል የኢሻ ጸሎት አዛን ሙእሚኖቹን ከያሉበት እኔን ግን የበለጸጉ ሀገራት እንኳ ሊለግሱኝ ከማይችሉት እንቅልፌ ጠራን፡፡ ተበሳጨሁ፡፡ ተነጫነጭሁ፡፡ ስግደቱ እስኪያበቃ ድረስ ነጎድጓዳማው ድምጽ ማጉያ አካባቢውን ተቆጣጠረው፡፡ ወይ መከራ! ዓይኖቼን መግለጥ ቢያቅተኝም መተኛት አልቻልሁም፡፡ ቶሎ መጠናቀቁን ተስፋ ማድረግ ጀመርሁ፡፡ “ኢስላም ማለት ሰላም ማለት ነው፡፡” የሚለው የእናቴ ጎረቤት የሼህ በድሩ አስተምህሮ ብልጭ አለብኝ፡፡ “ሼህ በድሩ ዘመዶችዎ እዚህ እኔን የሰላም እንቅልፍ እየነሡኝ እንደሆነ አላዩልኝም፡፡” 

ጸሎቱ ረዘም ላለጊዜ ቀጥሎ ከቆየ በኋላ ዝምታ መልሶ ሰፈነ፡፡ ቦብ ማርሌይ ከጎረቤቴ ቡና ቤት ሆኖ በለስላሳው “Don’t worry about a thing; every little thing is gonna be alright” ይለኝ ጀመር፡፡ “አልሐምዱሊላህ! አሁን መተኛት እችላለሁ፡፡” ብዬ ራሴን አጽናናሁትና ድጋሚ የዕንቅልፍ ቪዛ ለማግኘት የትራሴን ኤምባሲ ደጅ መጥናት ጀመርሁ፡፡ እ…ፎ…ይ…!

እናቴን መጣች፡፡ ካቀረቀርሁበት ወረቀት ላይ ቀና አድርጋ ሳመችኝና “ምነው ልጄ ከሳሽ?” አለችኝ፡፡ ፊቴን እየደባበሰችም “የአዲስ አበባ ብርድ አቆርፍዶሽ የለ እንዴ? ወይኔ ልጄን! ቆይ አሁን ቆንጆ እራት አዘጋጅልሻለሁ፡፡” እያለች ወደ ማድቤት ገባችና የሚጣፍጥ ምሥር ወጥ ዝንጥፍጥፍ ባለ የነጭ ጤፍ እንጀራ ላይ አድርጋ ወደእኔ መጣች፡፡

“አበባዬ እስኪ ይህቺን ላጉርስሽ፡፡ አንቺ መቼም እዚህ ወረቀት ላይ አንዴ ከተተከልሽ የሚነቅልሽ የለም፡፡” አምላክ እናቶችን የፈጠረበት እጁ በእውነት ፍቅር ነው፡፡

እንጀራውን በወጥ አጥቅሳ ጉርሻዋን ከሰማመረቻት በኋላ እጇን ወደኔ ዘረጋች፡፡ ወይኔ! የምሥሩ ወጥ ሽታ የጽጌረዳን መዓዛ ያስንቃል! አቦ አሁን የእናት ጉርሻ ከሌላ ሰው ጉርሻ ጋር እኩል ጉርሻ ይባላል? ስሕተት ነው፡፡ እንዴ! ሌላ ሰው የፈለገውን ያህል ጠቅልሎ ቢያጎርስ ጉርሻው እንጀራ በወጥ ከመሆን አይዘልም፡፡ ምናልባት ከዘለለም አሳንቆ የመግደያ መሣሪያ ሊሆን ይችላል፡፡ የእናት ጉርሻ ግን እንደዚህ አይደለም፡፡ ወጡ ሽሮም ይሁን ዶሮ እናት የምታጎርሰው እንጀራ በወጥ አይደለም- ፍቅር በፍቅር እንጂ፡፡ በተለይ ደግሞ ወጡ እንደዚህ እንደኔ እናት ምሥር ወጥ ትክትክ ብሎ የተከሸነ ከሆነማ በቃ! አፌን ወደጉርሻዋ ቀረብ አደረግሁ፡፡

ምን ያደርጋል! የጎረቤታችን ቡና ቤት ዲጄ ከአንድ የጥቁር ፈረንጅ ጋር በመመሳጠር “Can’t touch this!” ብሎ ጮኸብኝና እርሱ ላይበላው የእናቴን ጉርሻ ነጠቀኝ፡፡ ጠላታችሁ ብን ይበል! ብንን ብዬ ተነሣሁና በድንጋጤ ጆሮዎቼን እኮረኩር ጀመር- ዲጄው ጆሮዬ ውስጥ የገባ መስሎኝ፡፡ ውይ ሐበሻ! አሁን እናቴ እኔን አንድ ሴት ልጇን በሕልሜ እንኳን ብታጎርሰኝ ምናለበት?! አቦ ሐበሻ ምቀኛ ነው፡፡ እንደ ዐረብ ሀገር ስደተኛ እኅቶቼ ከሀገረ እንቅልፍ በጥረዛ መባረሬ ካልቀረ ምናለ የእናቴን ጉርሻ እንኳ እስክጎርስ ቢጠብቀኝ ኖሮ፡፡
*                                           *                          *                                   *                    *
“እንዲህ ቢሆን ኖሮ! እንዲያ ቢሆን ኖሮ!
ኖሮ እያሉ ኖሮ
ከመኖር አማርሮ”
አሁን ያለሁበትን ሁኔታ በዘመናchin Journalists አማርኛ ስገልጸው “ዲጄው የሙኒትን ዘፈን እጅግ ከፍ ባለ ድምጽ በማጫወት ላይ ያለበት ሁኔታ ነው ያለው፡፡” ልል እችላለሁ፡፡ አብረውት ያሉት የቡና ቤቱ ታዳሚዎችም ባልተገራ ጉሮሮ በጃምቦ-ጀትኛ ያጓሩ ጀምረዋል፡፡ ለነገሩ የጠጡት ጃምቦ ብዛትም ሊሆን ይችላል፡፡ ይህ ታዋቂ ዘፈኗ እኛ ሰፈር አካባቢ እንዲህ ያለ ያለመዜም አሰቃቂ አደጋ እንደደረሰበት ራሷ ሙኒት ብትሰማ ኖሮ ከድንጋጤዋ ብዛት የተነሣ ቦሌ አካባቢ የሚገኘው አማርኛዋ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ከሀገር ይኮበልልባት ነበር፡፡ ደግነቱ ቴዎድሮስ ታደሰ “ነገር ካልሰሙት መቼም አይቆጭም፡፡” ብሏል፡፡


አሁን ዲጄው ከድምጽ ማጉያው ጋር ተቧድኗል፡፡ ታዳሚዎቹ ደግሞ በአንድ ላይ ሆነው በባዶ ጉሮሮ እየተፎካከሩት ይገኛሉ፡፡ እንቅልፌን አባረሩብኝ፡፡ “ምነው ጉሮሯችሁ እንደ አክርማ ከሁለት በተሰነጠቀ!” ብዬ ልራገም አማረኝ፡፡ ግን ያን የመሰለ የእናቴን ጉርሻ ሊቀበል የነበረ አፌ እንዲህ ያለ መራራ ነገር አይመጥነውም ብዬ ተውሁት፡፡ ደግሞ የእናቴ መንፈስ ሰምቶኝ ሰዎቹን በሙሉ ጉሮሮ አልባ ቢያደርጋቸውስ? 
እነሆ በአንድ ሌሊት እንቅልፌን ለሁለተኛ ጊዜ ተነጠቅሁ፡፡ ወይ ነዶ! የብስጭቴ ብዛት ውስጥ እግሬ ድረስ ዘልቆ ስለተሰማኝ ነው መሰለኝ ልቤ በኃይል ትመታ ጀመር፡፡ ውስጥ እግርና ልብ እንዴት ይገናኛሉ? የሚለው ጥያቄ ለሥነ ሕይወት ተማሪዎች፣ ተመራማሪዎች ወይም ተማራሪዎች የቤት ሥራ ይሁናቸው፡፡  
ሞባይሌን አየሁት፡፡ ከሌሊቱ 7፡13 ደቂቃ ይላል፡፡ ነገ 4፡00 ላይ የምፈተነው ፈተና አለኝ፡፡ ምንም እንኳ የምማረው ለሁለተኛ ዲግሪዬ ቢሆንም ቅሉ ውጤቴ ላይ ቀልድ አላውቅም፡፡ ምክንያቱም አሁን ከምሠራበት መሥሪያ ቤት አሰልቺ ልማታዊ ስብሰባና አቆርቋዥ የቢሮ ፖለቲካ ልላቀቅ የምችለው ይህቺን ዲግሪዬን ስይዝ ብቻ እንደሆነ ጠንቅቄ አውቃለሁ፡፡ እርግጥ ነው ሰሞኑን አብዛኛውን ከዕንቅልፌ፣ ጥቂት ጥቂት ደግሞ ከሻይ ሰዐቴም፣ ከቢሮ ወሬ ሰዐቴም፣ ከታክሲ ላይ ቆይታዬም እየቀነጣጠብሁ ጥሩ ስቸክል ከርሜያለሁ፡፡ ትምህርቱ ደግሞ ደስ ይላል፡፡ A ማምጣት እንዳለብኝ ከራሴ ጋር ተስማምተናል፡፡ ዛሬ ሌሊት እስከ 9፡30 ድረስ ተኝቼ ከዚያ በኋላ ያሉትን ሰዐታት ለመጠቀም አስቤ ነበር፡፡ እድሜ ለጎረቤቶቼ እነሆ ለሊቷ ዓይኔ እያያት ሔደች፡፡ ራሴ ይወቅረኝ ጀመረ፡፡ እማማ እልፍነሽ መውጣታቸውን ማየቴ አደፋፈረኝና የመጣው ይምጣ ብዬ መብራቱን አበራሁት!
እንደምንም ራሴን አበረታታሁትና ከአልጋዬ ወርጄ ፊቴን ታጠብሁ፡፡ ወረቀቶቼን ከቦርሳዬ ውስጥ አውጥቼ አልጋዬ ላይ ቁጭ አልሁ፡፡ አንድ ሰዐት ያህል እንዳነበብሁ ዓይኔ ይቆጠቁጠኝ ጀመር፡፡ ዕንቅልፌ እንዳያሸንፈኝ ብዬ ከአልጋዬ ወረድሁና ቆሜ ማንበብ ጀመርሁ፡፡ ብርዱ ሊሰማኝ ሲጀምር አልጋ ልብሱን ለብሼ አልጋ ላይ ቁጭ አልሁ፡፡ የዲጄው ሙዚቃ እየቀነሰ ሔዷል፡፡
*                                  *                           *                                   *
የድሮ ትምህርት ቤታችን ውስጥ ነን፡፡ አባዬ የገዛልኝን አዲሱን ሮዝ ቀሚሴን ለብሻለሁ፡፡ የዓመቱ መጨረሻ ነው፡፡ ሁላችንም ወላጅ አምጥተናል፡፡ የመረብ ኳስ ዳችን ላይ የክፍል ዴስኮቻችን ወጥተው ወላጆቻችንና እኛ ተደርድረንባቸዋል፡፡ ከየክፍሉ ከአንደኛ እስከ ሦስተኛ የወጡ ተማሪዎች እየተሸለሙ ነው፡፡ የኛ ክፍል ተራ ደረሰ፡፡ የአካባቢ ሳይንስ ቲቸራችን መነጽራቸውን አስተካከሉና
“ከሦስተኛ ኤ ተማሪ ምሥራቅ ቢተርፍ ሦስተኛ!” በማለት ጮሁ፡፡
ወላጆቻችን አጨበጨቡ፡፡
ወንዳታ! ሦስተኛ አልወጣሁም ማለት ነው፡፡ አባባ ደግሞ ከአንድ እስከ ሁለት ከወጣሽ የቦሊ ቦሊ ኳስ እገዛልሻለሁ ብሎኛል፡፡
ጓደኛዬ ምሥራቅ ሽልማቷን ተቀብላ ተመለሰች፡፡ ሱዚና ገመድ ዝላይ የሚችላት የለም፡፡ ቦሊ ቦሊ ግን እኔ እበልጣታለሁ፡፡
“ተማሪ ደቻሳ ግርማይ ሁለተኛ!” የስ! አንደኛ ነው የወጣሁት ማለት ነው!
ደቻሳ ስዘልል አየኝና አኮረፈ፡፡ ስለበለጥኩት ነው፡፡ ግን ሽልማቱን ሔዶ ወሰደ፡፡
“ተማሪ በፍቅር አዘዘ አንደኛ! አጨብጭቡላት!” ሰዉ ሁሉ አጨበጨበልኝ፡፡ ምሥራቅ ግን አላጨበጨበችልኝም፡፡ እኔ ግን አጨብጭቤላት ነበረ፡፡
አባዬ ዕቅፍ አድርጎ ሳመኝና “ሒጂ ሽልማትሽን ውሰጂ፡፡” አለኝ፡፡
“አባዬ የቦሊቦሊ ኳሴን ትገዛልኛለህ አይደል?”
“እሺ፡፡ እሱ በኋላ ይደርሳል፡፡ አሁን ሒጂና ተሸለሚ፡፡”
ዳይሬክተራችን በቢጫ ወረቀት የተሸፈነ ነገር ይዘዋል፡፡ ለኔ ነው፡፡ ፈገግ ብለው እያዩኝ ነው፡፡ አካባቢ ሳይንስ አስተማሪያችንም እያጨበጨቡልኝ ነው፡፡ መድረኩ ጋር ልደርስ ነው፡፡ ከኋላዬ የነበረው ጭብጨባ በድንገት ጸጥ አለና “ተንሥኡ ለጸሎት!” የሚል ትእዛዝ ሰማሁ፡፡ ወደኋላዬ ዞር አልሁ፡፡

የእማማ እልፍነሽ ቤተክርስቲያን ዲያቆን ከሞት ለመቀሰቅስ በሚመስል ጩኸት ሽልማቴን ነጠቀኝ፡፡ እስኪ ምናለ በሕልም እንኳ ብሸለምበት?

“እግዚኦ ተሣሃለነ፡፡” ሌላ ድምጽ ተቀብሎ አካባቢውን አንቀጠቀጠው፡፡ ከመሬቷ በስተቀር ሁሉ ነገሯ ቆርቆሮ የሆነችው ቤተክርስቲያኗ አናቷ ላይ የሰቀሉባትን ይህን አገር ገልብጥ ድምጽ ማጉያ እንዴት እንደቻለችው አላውቅም፡፡ "ቆይ ደግሞ “ለጸሎት ተነሡ!” የሚለው ትእዛዝ ቤተክርስቲያን ውስጥ ላለሰው እንጂ እሥራ ላይ ውሎ ደክሞት ቤቱ አልጋ ላይ ማንንም ሳያስቸግር የተኛ ሰውን ነው እንዴ?" ተነጫነጭሁ፡፡ ወረቀቶቼ አልጋው ላይ ተበታትነዋል፡፡ ደብተሬም መሬት ላይ ወድቋል፡፡ ወይ ነዶ!
ሰዐት አየሁ፡፡ ከሌሊቱ 10፡10 ይላል፡፡

“ሰላም ለኵልክሙ!” ቄሱ ቀጠሉ፡፡ ወይ ሰላም! አጠገቤ ቢሆኑ ኖሮ ብዬ ተመኘሁ፡፡
“ለእኔ አሁን ሰላሜ እንቅልፌ ስለሆነ አይበጥብጡኝ! አይጩሁብኝ! ልተኛበት! እኔ እንደእርስዎ በወር ሁለት ሳምንት ሳይሆን በወር አራት ቀናት ብቻ እንዳርፍ የተፈቀደልኝ ግብር ከፋይ ዜጋ ነኝ፡፡ እሑዴን አይሸራርፉብኝ፡፡ እማማ እልፍነሽን ከሆነ እርስዎ ጋር ስለሆኑ በሹክሹክታም ቢናገሩ ይሰሙዎታል፡፡ እኔን ለእንቅልፌ ይተዉኝ፡፡ አሁን ጸሎትዎን ለመካፈልም ሆነ የድምጽዎን መረዋነት ለማድነቅ ጊዜዬ አይደለም፡፡” እላቸው ነበር፡፡ 

ዕንቅልፌ ሲሸሽ ጥሎት በሔደው የድካም ጓዝ ሰውነቴ ደቀቀብኝ፡፡ ትራሱ ቆልምሞኝ ነበረ መሰለኝ አንገቴን በጣም አመመኝ፡፡ አጠገቤ የነበሩትን ወረቀቶች በማንሣት ጥናቴን ለመቀጠል ሞከርሁ፡፡ ከአንድ ሰዐት በላይ ግን መቀጠል አልቻልሁም፡፡ ዓይኖቼ እጅግ ያቃጥሉኝ ጀመር፡፡ ቢያንስ አእምሮዬ በቂ ዕረፍት ካገኘ እስከዛሬ ያጠናሁትን ፈተና ላይ ንቁ ሆኜ እንደምሠራ ራሴን አባበልሁትና የሔደውን እንቅልፌን ለመከተል ቆረጥሁ፡፡ ጠዋት ዕንቅልፍ እንዳይጥለኝም ስልኩን ዐላርም ሞላሁት፡፡ እግረመንገዴንም አሁን 11፡05 መሆኑን አየሁ፡፡ የመስጊዱ ሙአዚን በአረብኛ “ከእንቅልፍ ሶላት ይሻላል!” ሲሉ መጣራት ጀምረዋል፡፡ እኔ ግን ለጊዜው አምላኬን ከጸሎት ይልቅ በሕልም ውስጥ ማየትን መርጫለሁ፡፡ ስለዚህ ልተኛ ነው፡፡ አልጋልብሱን ወደፊቴ ሳብሁትና ተሸፋፈንሁ፡፡
*                                         *                                       *                          *
“ምእመናን ሙሽሮቹ እየገቡ ስለሆነ እልል በሉ! እልል በሉ! እልልልልልልልልልልልልልልልል!”
“በጽሐ መርዓዊ ፍሥሐ ለኵሉ
በሰላም ጻኡ ተቀበሉ፡፡”
ወይ ሰላም! የትልቁ ቤተክርስቲያን ትልቁ ድምጽ ማጉያ በቤተክርስቲያኑ ውስጥ ሁለት ሰዎች ከሁለትነት ወደአንድነት በመምጣት ላይ በመሆናቸው እኔ በምንም ምክንያት ለብቻዬ እንቅልፌን ማጣጣም እንደማልችል ነገረኝ፡፡ ወይ ጣጣ! አሁን እነዚህን ሰዎች ለማጋባት ቤተክርስቲያኑ ውስጥ ያለው ሰው እልል ካለ አይበቃም? ቤታችን ያለን ሰዎች ሁሉ አልጋችን ውስጥ ሆነን እልል ማለት ይጠበቅብናል? ወይስ ቤተክርስቲያኑ ውስጥ የሚደረገውን ነገር በሙሉ እኛ ልንሰማው ያስፈልጋል? እንዴ መስማት ከፈለግን እንመጣ የለም እንዴ የምን ረብሻ ነው?
የእማማ እልፍነሽ ቤተክርስቲያን ካህን ደግሞ “ለእሉ ክልኤቱ ፍጡራን ስብሐተ ፈጣሪ ይደልዎሙ” እያሉ ደመቅ አድርገው ያዜሙ ጀመር፡፡
ሦስቱም ድምጽ ማጉያዎች አንድ ላይ ሲጮሁብኝ ራሴ ዉዉዉ... ይልብኝ ጀመር፡፡
ተኝቶ ከማዳመጥ ውጪ ምንም ማድረግ አልቻልሁም፡፡ ሦስቱንም በደነዘዘ አእምሮ ማድመጥ ጀመርሁ፡፡ አስራ አንድ ሰዐት ተኩል አካባቢ ሙአዚኑ ዝም አሉ፡፡ አሁን የሁለቱ ቤተክርስቲያኖች ድምጽ ማጉያዎች እሪታ ብቻ አካባቢውን ተቆጣጥሮታል፡፡
“ተሣሃልከ እግዚኦ ምድረከ!”
“ሠርዐ ለነ ሰንበተ ለዕረፍተ ዚአነ ፍሥሐ ወሰላም ለእለ አመነ፡፡”
እንቅልፍ በዓይኖቼ ሊዞር አልቻለም፡፡ ይህቺ ሞገደኛ ውስጤ ሒጂና “እኔን ዕንቅልፌን እየነሣችሁኝ እናንተ ሰንበት ለዕረፍት ነው ብትሉ እንዴት ላምናችሁ ይቻለኛል?” በያቸው አለችኝ፡፡ እኔ ግን ዐቅሜን ስለማውቅ ለሌሊት እንቅልፍ ብዬ የቀን ሕይወቴን መቃብር አላወርዳትም ብዬ ተውሁት፡፡

ኪዳኑ አለቀ፡፡ ቅዳሴ ቀጠለ፡፡
“ኵሉ ዘገብራ ለጽድቅ ጻድቅ ውእቱ ወዘያከብር ሰንበተ፡፡”
 …
“ጻኡ ንኡሰ ክርስቲያን፡፡”
ሰዐቴን አየሁት፡፡ 1፡15፡፡ ፈተናዬ ሊጀመር ሁለት ሰዐት ከ45 ደቂቃዎች ይቀሩታል፡፡ እነዚህን ሰዐታት እንኳ ብተኛ ንቁ እሆን ነበረ፡፡ ከመንጋጭላዬ የግራ ጎን አንሥቶ እስከመሐል አናቴ ድረስ እየወጋኝ ነው፡፡ ራስ ፍልጠት የሚባለው መሆን እንዳለበት ገመትሁ፡፡ ጨጓራዬም ክፉኛ መገለባበጥ ጀምሯል፡፡ በጊዜ በወተት ካላበረድሁት እንደተለመደው ሳምንት ሊያስተኛኝ መሆኑ ነው፡፡ ወደ ትምህርት ቤት ሔጄ ቤተ መጻሕፍት ውስጥ ትንሽ ብተኛስ? እንዲያውም ከሸምሱ ሱቅ የላስቲክ ወተት እገዛና እሱን መንገድ ላይ ጠጥቼ እሔዳለሁ፡፡ ከአልጋው ላይ በፍጥነት ወረድሁና ማታ በያቅጣጫው የወረወርኳቸውን ልብሶቼን ከያሉበት ጠርቼ ለባበስሁ፡፡ ጫማዬን አስሬ ቀና ስል የማየው ነገር ሁሉ ነጭ ሆነብኝ፡፡ አዞረኝ፡፡ ቶሎ ብዬ ቁጭ አልሁ፡፡
የእማማ እልፍነሽ ዲያቆን “የተቀመጣችሁ ተነሡ!” ሲል ሰማሁት፡፡
ወይ መነሣት!

ለጥቂት ደቂቃዎች እዚያው ባለሁበት ተቀመጥሁና መለስ እንደማለት ሲልልኝ ቀስ ብዬ ተነሣሁና በሩን ቆልፌ ወጣሁ፡፡
ክሊኒኩ ጋር ስደርስ የሆነ ነገር መሬት ላይ ወድቆ ተመለከትሁ፡፡ ጎንበስ ብዬ አየሁት፡፡ ጠላታችሁ ወከክ ይበል ልቤ ወከክ አለ፡፡ መቶ ብር! እንዴ! ሌሊቱን ሙሉ በእርሱ ስም እንቅልፍ ሲነሱኝ ያደሩትን ተመልክቶ አምላክ ለካሳዬ የሚሆን ነገር አዘጋጀልኝ፡፡ ብድግ አደረግኋት፡፡ ቀና ስል ግን ሰማይ ምድሩ ተደባለቀብኝ፡፡ ምድሪቷ ከሥሬ ከዳችኝ፡፡ ጸጥታ፡፡
*                             *                                          *                                 *
 “በፍቅር! በፍቅር!”
ነቃሁ፡፡  ክንዴ ላይ ግሉኮስ ተቀጥሎልኛል፡፡ ተርፌያለሁ ማለት ነው፡፡ ነጭ ገዋን የለበሰ ረዥምና ወፍራም ሰው አጠገቤ ቆሞ ይጠራኛል፡፡ በዓይን አውቀዋለሁ፡፡ የክሊኒኩ ነርስ ነው፡፡
“አቤት”
“ምን ሆነሽ ነው፡፡” 
“አዙሮኝ፡፡” 
“ስትወድቂ እኔ ከኋላሽ ነበርሁ፡፡ አንሥቼሽ ነው፡፡ ከዚህ በፊት ያምሽ ነበር እንዴ?”
ከጨጓራ በስተቀር የማውቀው ሌላ ሕመም እንደሌለብኝና ሌሊት በእንቅልፍ እጦት እንዴት እንደተሰቃየሁ ነገርሁት፡፡ ፊት ለፊቴ የተሰቀለውን የግድግዳ ሰዐት ተመለከትሁት፡፡ 3፡00፡፡ የአራት ሰዐቱ ፈተናዬ ትዝ አለኝ፡፡ እንደምደርስ አሰብሁ፡፡ አሁን ራስምታቱ ቀለል ብሎልኛል፡፡ ጸጥ ብሏል፡፡

“ታድለህ!” ብዬ ልናገር ስል የቤቱ የፍሎረሰንት መብራት እንደጥንዚዛ መጮህ ጀመረ፡፡
“Great! መብራት መጣ ማለት ነው፡፡” አለ፡፡
በዚያው ቅጽበት ከጎረቤት “ኢየሱስ ጌታ ነው! ኢየሱስ ጌታ ነው! እልልልልልልል!” ተባለ፡፡ አዲሷ የሰፈሬ ፕሮቴስታንት ቸርች ምእመናን ናቸው፡፡ ኪይቦርዱ አጉረመረመ፡፡ አስመላኪው ምእመናኑን ለዝማሬ ጋበዘ፡፡ እስከ ሰማይ ድረስ በእነርሱ ምስጋና ምድርን እንደ ብረት ድስት ክድን እንደሚያደርጓት መንፈሳዊ መፈክር አሰማ፡፡ 
“አሜን! ሀሌሉያ! እልልልል!” ተባለ፡፡ ከዚያም አካባቢው ይቀወጥ ገባ፡፡ 

“የነፍሴ ወዳጅ አንተ በፍቅርህ ልቤን ታሳርፋለህ፡፡”
“እልልልልልል…..!”

እያሉ ይዘምሩ ጀመር፡፡ የጭብጫቦውና የእልልታው ሱናሚ የክሊኒኩን የጭቃ ግድግዳ ያናግረው ገባ፡፡ ነርሱ ምንም እንዳልተፈጠረ ሥራውን ቀጥሏል፡፡ ያው በፊዚካል ምናምን እቋቋመዋለሁ ብሎ ይሆናል፡፡ እኔ ግን “ጃፓንን ያየ በሱናሚ አይቀልድም፡፡” ብዬ የመሐሙድን “ዐቅምን ዐውቆ መኖር ጥሩ ነው፡፡” እየዘፈንሁ ከአልጋው ዱብ፡፡ የምሬን ነው የምላችሁ የሃይማኖት ድርጅቶች በሙሉ እኔ እንዳልተኛ በጠላትነት የተሰለፉብኝ መሰለኝ፡፡ እንዴ! እነርሱ ስለ እረፍታቸው የሚያመሰግኑት ሌላ ሰው ዕረፍት እየነሱ ነው እንዴ? 

ከክሊኒኩ ስወጣ አያቴ ዳዊት ሲደግሙ “መኑ ይሁበኒ ክንፈ ከመ ርግብ እስርር ወአእርፍ” ይሉ የነበረው ትዝ እያለኝ ነበር፡፡
በርሬ አርፍ ዘንድ እንደርግብ ክንፍን ማን በሰጠኝ (መዝ. 55፣6)፡፡