Monday, February 27, 2012

“ከማያውቁት መልአክ የሚያውቁት ሰይጣን ይሻላል”

የዛሬው ወሬዬ መሠረት የሚያደርገው “The Road Less Travelled” ከተሰኘው መጽሐፍ ያገኘሁትን ትምህርት ነው፡፡ የዚህ መጽሐፍ ደራሲ ስኮት ፔክ የሚባል ሳይኮቴራፒስት ሲሆን ከጻፋቸው መጻሕፍት ውስጥ እንደዚህኛው የተወደደለት የለም ይባላል- 10000000 ቅጂ ተሸጦለታል፡፡

እንደስኮት ፔክ አባባል ብዙዎቻችን ለበጎ ነገር ሰነፎች ነን፡፡ በዚህም የተነሣ በጎ ነገር መሆኑን ብናውቅም እንኳ አዲሱን በጎ ነገር ከማድረግ ይልቅ በለመድነው መጥፎ ነገር ውስጥ መዘፍዘፍ ይመቸናል፡፡ በሱስ ተጠምደን ሱሱ ሥነልቡናዊ ጤንነታችንን፣ አካላዊ በጎነታችንን፣ ቤተሰባችንን፣ ሥራችንን፣ ማኅበራዊ ኑሯችንን ወዘተ. እያቃወሰው፣ እየበጠበጠው እያየንና ጉዳቱም በእጅጉ እየተሰማን፣ ሱሱን ማቆም እንዳለብንም እያወቅን ሱሱን ለማቆም ግን እንሰንፋለን፡፡ ሱሱን ለማቆም ልናደርጋቸው የሚገቡ ነገሮችን ሁሉ ስናስባቸው ዳገት ይሆኑብናል፡፡ ውጤቱ ጥሩ መሆኑን ብናውቅም ልፋቱን ላለመልፋት ድካሙንም ላለመድከም ሳንጀምረው እንዝላለን፡፡ በለውጥ ሒደት ላይ ከመንገላታት ይልቅ እንደደረቀ ግንድ እየበሰበስን፣ ምሥጥ እየበላን ባለንበት መገተርን እንመርጣለን፡፡

ታማሚዎች ሆነን ጤናችን ሴቻና ሲቀላ እየረገጠ ሲያስቸግረን የታዘዘልንን መድኃኒት ወስዶ መጨረሱ አቀበት ይሆንብናል፡፡ በመድኃቱ ፍጻሜ ከምናገኘው ጤንነት ይልቅ በመድኃኒቱ ምሬት፣ ወይም መጎምዘዝ፣ ወይም መብዛት እንማረራለን፡፡ ተማርረንም እንተወዋለን፡፡

Friday, February 24, 2012

ዝም


ዛሬ የማካፍላችሁ ግእዝ፣ ዕብራይስጥ፣ ጽርእ (ግሪክ)፣ ላቲን፣ ጣልያንኛ፣ ጀርመንኛ፣ ፈረንሳይኛ፣ እንግሊዘኛ፣ ግእዝና አማርኛ ከሚያውቁት፣ መጽሐፍ ቅዱስን በጉንጫቸው የያዙ የሚመስሉት ግን ትሑት መንፈሳቸው የኔ መምህር ካደረጋቸው የዋኅ መምህሬ የሰማሁትን ነው፡፡

አይሁዳውያን በሒትለር በሚመራው የናዚ ፓርቲ የደረሰባቸውን ጭፍጨፋ ዓለም “Holocaust” ብሎ ይጠራዋል፡፡ የቃሉ መነሻ ግሪክ ሲሆን ትርጉሙም በአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ “የሚቃጠል መሥዋዕት”፣ በእንግሊዘኛ (Burnt offering) ተብሎ የሚጠራውን አንድም ተረፍ ሳይኖረው ሙሉ በሙሉ በመቃጠል ለአዶናይ ይቀርብ የነበረውን የብሉይ ኪዳን መሥዋዕት ያመለክታል፡፡   


ናዚዎችም አይሁዳውያንን እንደ መሥዋዕቱ ብን ብለው ከገጸ ምድር እንዲጠፉ ለማድረግ ነበርና ዓላማቸው ዓለም የሰጠው “Holocaust” የሚለው ስም ተገቢ ይመስላል፡፡ ጽዮናውያኑ ግን በዚህ አይስማሙም፡፡ መሥዋዕት ከሰው ለአምላክ የሚቀርብ ነገር ነው፡፡ በእኛ ላይ የደረሰውን ግን እንኳን እንደመሥዋዕት የሚቀበል አምላክ እንደሰው የሚያስብ ሰው እንኳ ምክንያት ሊሰጥለት የሚችለው ነገር አይደለም፡፡ ስለዚህም በእኛ ላይ የደረሰውን ግፍና መከራ፣ ሰቆቃና ሐዘን ሊገልጽ የሚችል አንድም ቃል የለም ይላሉ፡፡ ነገር ግን የደረሰባቸውን ሁሉ አንድ ቃል ጠቅልሎ እንዲወክልላቸው መርጠውታል፡፡ ይኸውም “ሸቫ” ወይም “ሸዋ” ይባላል፡፡ ትርጉሙም “ዝምታ፣ ጸጥታ” ማለት ነው፡፡ በቃ የደረሰባቸውን ሁሉ፣ አንዳች ወንጀል ሳይሠሩ መሳደዱን፣ መታሰሩን፣ መታጎሩን፣ በመርዝ ጭስ ታፍኖ መገደሉን፣ በሚቆማምጥ ብርድ በረኃብ አለንጋ መለብለቡን፣ የሽማግሌውን መጣል፣ የአሮጊቷን መፈጥፈጥ፣ የእርጉዚቱን መቀደድ፣ የጨቅላውን መጨፍለቅ ወዘተ. “ዝም” ብለው ሰየሙት፡፡ ለካ ዝምታም ይናገራል፡፡ ዝም፡፡


Thursday, February 23, 2012

የቤተሰብ መርገም


ዛሬ ከግሪክ ሚቶሎጂ አንድ ተረክ እንቆንጥር፡፡

በድሮ ጊዜ አንድ አትሬዉስ የሚባል ሰው የግሪክ አማልክትን በኃይል ለመብለጥ ይገዳደራል፡፡ በዚህም የተነሣ አማልክቱ ተቆጥተው የእርሱ ውላጆች በሙሉ ሕይወት የቀናች እንዳትሆንላቸው “አትሬዉስና ቤቱ የተረገሙ ይሁኑ!” የሚል እርግማን አስተላለፉ፡፡[i] ይህ እርግማን በትዕቢቱ ያስቆጣቸውን አትሬዉስን ብቻ ሳይሆን ልጆቹንና የልጅ ልጆቹን ሁሉ የሚመለከት ነበረ፡፡  

ጊዜ ነጎደ፡፡ እርግማኑም ተረሳና ከአትሬዉስ ልጆች መካከል አንዱ የሆነው አጋሜምኖን ክሊቴምኔስትራ ከምትሰኝ ሴት ጋር በፍቅር ይወድቃል፡፡ በመጨረሻም ያገባትና ኦሬስተስ የተባለ ልጅ ይወልዳሉ፡፡ ይህቺ ክሊቴምኔስትራ ግን በልጇ አባት ላይ ሌላ ሰው ወሸመችበት፡፡[ii]  መወሸሙም ሳይበቃት አጋሜምኖን ከጦርነት ሲመለስ ከውሽማዋ ጋር ተባብራ ገደለችው- የልጇን አባት! እርሷ ለውሽማዋ ፍቅር ብላ አጋሜምኖንን ስትገድል እርግማኑን ወደልጇ ማተላለፏን አላየችም፡፡ የአፍቃሪ ነገር! ያውም የውሽማ ፍቅር ችግር እኮ ነው፡፡ አማልክቱ ይህንን ሁሉ ከኦሊምፐስ ተራራ ላይ ተጎልተው ይመለከታሉ፡፡ እርግማናቸው በመሥራቱም “ቺርስ!” እየተባባሉ አማልክታዊ ጽዋቸውን ይቀባበላሉ፡፡ አባትየው ላይ የወደቀው እርግማን በገዛ ሚስቱ በመገደል ሲጠናቀቅ ያልተባረከ ሕይወት የመመምራት አማልክታዊው እርግማን ግን ወደ ልጁ ወደ ኦሬስተስ ተላለፈ፡፡

ኦሬስተስ እናቱ የፈጸመችውን ይህንን ወንጀል ሲያውቅ ነፍሱ አጣብቂኝ ውስጥ ወደቀች፡፡ ከፊቱም ሁለት አማራጮች ብቻ ቀረቡለት፡፡ አማራጭ አንድ በግሪኮች ባህል ወንድ ልጅ የአባቱን ገዳይ መግደል አለበት፡፡ አማራጭ ሁለት አንድ ግሪካዊ ሊፈጽማቸው ከሚችሉ ኃጢኣቶች ሁሉ እጅግ ከባዱ የገዛ እናቱን መግደል ነው፡፡[iii]

የአባቱን ገዳይ አለመበቀል ከባድ ነውር ነው፡፡ የወለደችውን እናቱን መግደልም ታላቅ ኃጢኣት ነው፡፡ ምን ይሻላል? ኦሬስተስ ብዙ ካወጣና ካወረደ በኋላ የመጀመሪያውን አማራጭ በመውሰድ የአባቱን ደም ለመበቀል የወለደችውን እናቱን ሲጥ አደረጋት፡፡ እርግማኑ ሠራ! አማልክቱ አሁንም ተደስተው “ቺርስ!” ተባባሉ፡፡

Thursday, February 16, 2012

ዓለምን ሁሉ ለመለወጥ


እነዚህ ቃላት በአንድ የአንግሊካን ቤተክርስቲያን ጳጳስ በነበሩ ሰው መቃብር ላይ ተጽፈው የተገኙ ናቸው፡፡
በጉርምስናዬ ጊዜ ሐሳቤ ወሰን አልነበረውምና ዓለምን ሁሉ ለመለወጥ አስብ ነበር፡፡ እድሜዬና ብስለቴ እየጨመረ ሲመጣ ዓለምን መለወጥ እንደማይቻል ተገነዘብሁ፡፡ ስለዚህም ግቤን ጠበብ አድርጌ ሀገሬን ብቻ ለመለወጥ ወሰንሁ፡፡
ነገር ግን እርሷም ጨርሶ የምትለወጥ አልሆነችም፡፡
የጉልምስናዬ ወራት ካለፈ በኋላ ቤተሰቤንና በቅርቤ ያሉትን ሰዎች በመለወጥ ላይ አተኮርሁ፡፡ ይሁን እንጂ ይህም ውጤት አልባ ነበረ፡፡
አሁን በሞት ልጠቀለል ጥቂት በቀረኝ ሰዐት በድንገት የሚከተለውን እውነታ ተረዳሁ፡፡

መጀመሪያ ራሴን ለውጬ ቢሆን ኖሮ፣ ቤተሰቤ የእኔን ምሳሌ ተከትሎ በተለወጠልኝ፤ በቤተሰቤ ውስጥ         ባገኘሁት ለውጥ አነሳሽነትና አበረታችነትም ሀገሬን ማሻሻል በቻልሁ ነበረ፡፡ ማን ያውቃል?! ይሄኔ ዓለምንም ለውጬ ይሆን ነበር፡፡    ነበረ፡፡ ነበረ፡፡ ነበረ...
   

It is blessed to give than to receive.


A friend of mine named Paul received an automobile from his brother as a Christmas present. On Christmas Eve when Paul came out of his office, a street urchin was walking around the shiny new car, admiring it. “Is this your car, Mister?” he asked.
Paul nodded. “My brother gave it to me for Christmas.”
The boy was astounded. “You mean your brother gave it to you and it didn’t cost you anything? Boy, I wish…” He hesitated.
Of course Paul knew what he was going to wish for. He was going to wish he had a brother like that. But what the boy said jarred Paul all the way down to his heels.
“I wish,” the boy continued, “that I could be a brother like that.”
Paul looked at the boy in astonishment, and then impulsively added, “Would you like to take a ride in my automobile?”
“Oh Yes, I would love that.”
After a short ride, the boy turned and with his eyes aglow, said, “Mister, would you mind driving in front of my house?”
Paul smiled a little. He thought he knew what the boy wanted. He wanted to show his neighbors that he could ride home in a big automobile. But Paul was wrong again.
“Will you stop where those two steps are?” the boy asked.
He ran up the steps. Then in a little while Paul heard him coming back, but he was not coming fast. He was carrying his little crippled brother. He sat him down on the bottom stem, then sort of squeezed up against him and pointed to the car.
“There she is, Buddy, just like I told you up stairs. His brother gave it to him for Christmas and it didn’t cost him a cent. And some day I am going to give you one just like it… then you can see for yourself all the pretty things in the Christmas windows what I have been trying to tell you about.”
Paul got out and lifted the disabled boy to the front seat of his car. The shinning- eyed older brother climbed in beside him and three of them began memorable holiday ride.
That Christmas Eve, Paul learned what Jesus meant when he had said: “it is more blessed to give than to receive” (Acts 20: 35)  

(This is not fiction. It is a true story.)

Source:- Chicken soup for the soul

Monday, February 13, 2012

የት አባቴ ኼጄ ልረፍ?

ሞባይሌን ተመለከትሁት የሳምንቱ ቅዳሜ አስራ አንደኛው ሰዐት ካለፈ ሠላሳ ደቂቃዎች መሆናቸውን ነገረኝ፡፡ የመጨረሻዋ ባለጉዳይ ገባች፡፡ መሥርያ ቤቴ ለደንበኞቹ ያዘጋጀውን ቅጽ መሙላት ጀመርሁ፡፡

“ስም”
ተናገረች፡፡ ፊቷ ላይ የፓውደር የከተራ በዓል በደመቀ ሁኔታ እየተከበረ አየሁት፡፡ ስሟን ሞላሁ፡፡ መሥሪያ ቤቴ ያዘጋጀውን ባለ ሦስት ገጽ ቅጽ ሞልቼ ጨረስሁ፡፡ ደስ ብሏት ከቢሮዬ ወጣችልኝ፡፡ እፎይ! ግልግል፡፡ ጠረጴዛ ላይ ጎብጦ ቀኑን ሙሉ ባለ ጉዳዮች በአምሳለ ጢስ ከብበውት የዋለው ትከሻዬ ላይ ቆረጠመኝ፡፡ ለነገሩ በቀን የአራት መቶ ሰው ቅጽ ሞልቼ ባይደክመኝ ይገርማል፡፡ የወጣልኝ ልማታዊ ሠራተኛ ነኝ፡፡

ረኀብ ሆዴን እንደ ድመት ይቧጥጠኝ ጀመር፡፡ ከቢሮዬ ምንጥቅ ብዬ ወጣሁ፡፡ እራቴን የመሥራት ጥንካሬው ስላልነበረኝ ጁስ ቤት ገብቼ አምባሻና ጭማቂዬን ላስኩና (መቼም በላሁ አይባል ነገር) በየወሩ የደመወዜን ግማሽ ወደምሰዋላት ቤቴ ማዝገም ጀመርሁ፡፡ ሰፈራችን መግቢያ ላይ ከክሊኒኩ ጎን ሦስት ሰዎች የሆነ ማስታወቂያ እየተከሉ ነው፡፡ አነበብሁት፤ “የዛሬው ትውልድ ቤተክርስቲያን Today’s Generation Church” ይላል፡፡ ግቢዬ በር ላይ ስደርስ የግማሽ ደመወዜን መሥዋዕት ተቀባይ እማማ እልፍነሽን አገኘኋቸው፡፡ ነጭ በነጭ ለብሰዋል፡፡ የሆነ ትራስና ጋቢ ነገር በቅርቡ ከገጠር ያመጧትንና አሁን በነጠላ የጠመጠሟትን ልጅ እግር ዘመዳቸውን በፌስታል አስይዘዋል፡፡ ትዝ አለኝ፡፡ ነገ ገደል አፋፍ ላይ የተሠራው ቤተክርስቲያን ወርኀዊ በዓል አለ፡፡ ወደዚያው እያዘገሙ እንደሆነ ገባኝ፡፡

በነገራችን ላይ እሱን ቤተክርስቲያን ለምን እዚያ ገደል ላይ ማነጽ እንዳስፈለገ ሁሌም እንቆቅልሽ ይሆንብኛል፡፡ ቤተክርስቲያን ጠፍቶ ነው እንዳይባል ከእርሱ በተቃራኒ አቅጣጫ በሁለት መቶ ሜትር ያህል ርቀት ላይ ሌላ ጥንታዊ ትልቅና በእምዬ ምኒልክ ጊዜ ከሰፈሩ ጋር አብሮ እንደተተከለ የሚነገርለት ቤተክርስቲያን አለ፡፡ አንድ ወቅት ስጠይቅ “ጠበል ፈልቆ ስለተገኘ ነው፡፡” የሚል ምላሽ አግኝቻለሁ፡፡ “ታዲያ ጠበሉን በጥንታዊው ቤተክርስቲያን ጥበቃና አገልግሎት ሥር ማድረግ አይቀልም ነበር?” ብዬ ስጠይቅ “ምነው ጥያቄ አበዛሽ?” የሚል የድምጽ ቁንጥጫ ቀመስሁ፡፡ ድምጻዊ ቁንጥጫው ወደ ዱላዊ ተግሣጽ ከማደጉ በፊት “ዝምታ ወርቅ ነው፡፡” የሚለውን ምሳሌያዊ አነጋገር ከድሮ የአማርኛ ደብተሬ ላይ አስታውሼ ራሴን አዳንሁ! (መማር ደጉ!)   
 
“እንደምን ዋሉ እማማ እልፍነሽ?
“ደኅና፡፡ ዚሃር መስጌን፡፡ ምነው ባክሽ ምነው ሌሊቱን ሙሉ መብራቱን ስታቃጥዪው ማደርሽ?
ውይይይይይይ! እኚህ ሴትዮ! የሚያከራዩዋቸውን ቤቶች 24 ሰዐት በመቆጣጠራቸውና በየሦስት ወሩ ኪራይ በመቀጠላቸው ወደፊት “ሞዴል ኪራይ ሰብሳቢ” ተብለው እንደሚሸለሙ ጥልቅ እምነት አለኝ፡፡
“የውልዎት እማማ እልፍነሽዬ በዚህ ሳምንት ትንሽ ፈተና አለችብኝ፡፡ ለዚያ ነው፡፡ ትንሽ ላጥና ብዬ፡፡ እስከ ስድስት ሰዐት…”
አላስጨረሱኝም፡፡ “ኤዲያ! ኤዲያ! ምነው እልፍነሽ!”

ዓይኖቻቸው ቆዳዬን እንደቅርፊት ከላዬ ላይ ገሸለጡት፤ ከፌስታል ነጻ የሆነ እጃቸውን በጄኪቻንኛ ይሁን በጄትሊኛ ባይገባኝም ፊቴ ላይ አወነጫጨፉብኝ፡፡ ቀድሞውንም ያልያዝሁትን መንገድ በቶኖች በሚለካ ትሕትና ለቀቅሁላቸው፡፡ ጋቢያቸውንና ነጠላቸውን በቁጣ ተጎነጻጽፈውብኝ ከባዱ ሰውነታቸው ወደፊት እየገፋቸው ኼዱ፡፡ እፎይ… ቤቴ ገባሁ፡፡ ጫማዬንና ልብሶቼን ገና ከበር ማውለቅ ጀምሬያለሁ፡፡ አንሶላ በመግለጥ ጊዜዬን ማባከን አልፈለግሁም፡፡ ከሁለት ወራት በፊት በአዲስ አበባ ምሕረት አልባ ብርድ ስሰቃይ ያየችኝ እናቴ የገዛችልኝን ወፍራም አልጋ ልብስ እንደጋዜጣ ተጠቀለልሁበትና በደረቴ ተዘረጋሁ! ከእኛ ግቢ ቀጥሎ ካለው ቡና ቤት “አድራሽ መላሽ አገልጋዬ” የሚለው የዘሪቱ ዘፈን ይሰማኛል፡፡ ዕንቅልፍ ይወስደኝ ጀመር፡፡ እፍፍፍፎይ!

“አላህ ወአክበር!” 
ከቤተክርስቲያኑ ጎን ያለው መስጊድ ደማቅና ማስጠንቀቂያ መሰል የኢሻ ጸሎት አዛን ሙእሚኖቹን ከያሉበት እኔን ግን የበለጸጉ ሀገራት እንኳ ሊለግሱኝ ከማይችሉት እንቅልፌ ጠራን፡፡ ተበሳጨሁ፡፡ ተነጫነጭሁ፡፡ ስግደቱ እስኪያበቃ ድረስ ነጎድጓዳማው ድምጽ ማጉያ አካባቢውን ተቆጣጠረው፡፡ ወይ መከራ! ዓይኖቼን መግለጥ ቢያቅተኝም መተኛት አልቻልሁም፡፡ ቶሎ መጠናቀቁን ተስፋ ማድረግ ጀመርሁ፡፡ “ኢስላም ማለት ሰላም ማለት ነው፡፡” የሚለው የእናቴ ጎረቤት የሼህ በድሩ አስተምህሮ ብልጭ አለብኝ፡፡ “ሼህ በድሩ ዘመዶችዎ እዚህ እኔን የሰላም እንቅልፍ እየነሡኝ እንደሆነ አላዩልኝም፡፡” 

ጸሎቱ ረዘም ላለጊዜ ቀጥሎ ከቆየ በኋላ ዝምታ መልሶ ሰፈነ፡፡ ቦብ ማርሌይ ከጎረቤቴ ቡና ቤት ሆኖ በለስላሳው “Don’t worry about a thing; every little thing is gonna be alright” ይለኝ ጀመር፡፡ “አልሐምዱሊላህ! አሁን መተኛት እችላለሁ፡፡” ብዬ ራሴን አጽናናሁትና ድጋሚ የዕንቅልፍ ቪዛ ለማግኘት የትራሴን ኤምባሲ ደጅ መጥናት ጀመርሁ፡፡ እ…ፎ…ይ…!

እናቴን መጣች፡፡ ካቀረቀርሁበት ወረቀት ላይ ቀና አድርጋ ሳመችኝና “ምነው ልጄ ከሳሽ?” አለችኝ፡፡ ፊቴን እየደባበሰችም “የአዲስ አበባ ብርድ አቆርፍዶሽ የለ እንዴ? ወይኔ ልጄን! ቆይ አሁን ቆንጆ እራት አዘጋጅልሻለሁ፡፡” እያለች ወደ ማድቤት ገባችና የሚጣፍጥ ምሥር ወጥ ዝንጥፍጥፍ ባለ የነጭ ጤፍ እንጀራ ላይ አድርጋ ወደእኔ መጣች፡፡

“አበባዬ እስኪ ይህቺን ላጉርስሽ፡፡ አንቺ መቼም እዚህ ወረቀት ላይ አንዴ ከተተከልሽ የሚነቅልሽ የለም፡፡” አምላክ እናቶችን የፈጠረበት እጁ በእውነት ፍቅር ነው፡፡

እንጀራውን በወጥ አጥቅሳ ጉርሻዋን ከሰማመረቻት በኋላ እጇን ወደኔ ዘረጋች፡፡ ወይኔ! የምሥሩ ወጥ ሽታ የጽጌረዳን መዓዛ ያስንቃል! አቦ አሁን የእናት ጉርሻ ከሌላ ሰው ጉርሻ ጋር እኩል ጉርሻ ይባላል? ስሕተት ነው፡፡ እንዴ! ሌላ ሰው የፈለገውን ያህል ጠቅልሎ ቢያጎርስ ጉርሻው እንጀራ በወጥ ከመሆን አይዘልም፡፡ ምናልባት ከዘለለም አሳንቆ የመግደያ መሣሪያ ሊሆን ይችላል፡፡ የእናት ጉርሻ ግን እንደዚህ አይደለም፡፡ ወጡ ሽሮም ይሁን ዶሮ እናት የምታጎርሰው እንጀራ በወጥ አይደለም- ፍቅር በፍቅር እንጂ፡፡ በተለይ ደግሞ ወጡ እንደዚህ እንደኔ እናት ምሥር ወጥ ትክትክ ብሎ የተከሸነ ከሆነማ በቃ! አፌን ወደጉርሻዋ ቀረብ አደረግሁ፡፡

ምን ያደርጋል! የጎረቤታችን ቡና ቤት ዲጄ ከአንድ የጥቁር ፈረንጅ ጋር በመመሳጠር “Can’t touch this!” ብሎ ጮኸብኝና እርሱ ላይበላው የእናቴን ጉርሻ ነጠቀኝ፡፡ ጠላታችሁ ብን ይበል! ብንን ብዬ ተነሣሁና በድንጋጤ ጆሮዎቼን እኮረኩር ጀመር- ዲጄው ጆሮዬ ውስጥ የገባ መስሎኝ፡፡ ውይ ሐበሻ! አሁን እናቴ እኔን አንድ ሴት ልጇን በሕልሜ እንኳን ብታጎርሰኝ ምናለበት?! አቦ ሐበሻ ምቀኛ ነው፡፡ እንደ ዐረብ ሀገር ስደተኛ እኅቶቼ ከሀገረ እንቅልፍ በጥረዛ መባረሬ ካልቀረ ምናለ የእናቴን ጉርሻ እንኳ እስክጎርስ ቢጠብቀኝ ኖሮ፡፡
*                                           *                          *                                   *                    *
“እንዲህ ቢሆን ኖሮ! እንዲያ ቢሆን ኖሮ!
ኖሮ እያሉ ኖሮ
ከመኖር አማርሮ”
አሁን ያለሁበትን ሁኔታ በዘመናchin Journalists አማርኛ ስገልጸው “ዲጄው የሙኒትን ዘፈን እጅግ ከፍ ባለ ድምጽ በማጫወት ላይ ያለበት ሁኔታ ነው ያለው፡፡” ልል እችላለሁ፡፡ አብረውት ያሉት የቡና ቤቱ ታዳሚዎችም ባልተገራ ጉሮሮ በጃምቦ-ጀትኛ ያጓሩ ጀምረዋል፡፡ ለነገሩ የጠጡት ጃምቦ ብዛትም ሊሆን ይችላል፡፡ ይህ ታዋቂ ዘፈኗ እኛ ሰፈር አካባቢ እንዲህ ያለ ያለመዜም አሰቃቂ አደጋ እንደደረሰበት ራሷ ሙኒት ብትሰማ ኖሮ ከድንጋጤዋ ብዛት የተነሣ ቦሌ አካባቢ የሚገኘው አማርኛዋ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ከሀገር ይኮበልልባት ነበር፡፡ ደግነቱ ቴዎድሮስ ታደሰ “ነገር ካልሰሙት መቼም አይቆጭም፡፡” ብሏል፡፡


አሁን ዲጄው ከድምጽ ማጉያው ጋር ተቧድኗል፡፡ ታዳሚዎቹ ደግሞ በአንድ ላይ ሆነው በባዶ ጉሮሮ እየተፎካከሩት ይገኛሉ፡፡ እንቅልፌን አባረሩብኝ፡፡ “ምነው ጉሮሯችሁ እንደ አክርማ ከሁለት በተሰነጠቀ!” ብዬ ልራገም አማረኝ፡፡ ግን ያን የመሰለ የእናቴን ጉርሻ ሊቀበል የነበረ አፌ እንዲህ ያለ መራራ ነገር አይመጥነውም ብዬ ተውሁት፡፡ ደግሞ የእናቴ መንፈስ ሰምቶኝ ሰዎቹን በሙሉ ጉሮሮ አልባ ቢያደርጋቸውስ? 
እነሆ በአንድ ሌሊት እንቅልፌን ለሁለተኛ ጊዜ ተነጠቅሁ፡፡ ወይ ነዶ! የብስጭቴ ብዛት ውስጥ እግሬ ድረስ ዘልቆ ስለተሰማኝ ነው መሰለኝ ልቤ በኃይል ትመታ ጀመር፡፡ ውስጥ እግርና ልብ እንዴት ይገናኛሉ? የሚለው ጥያቄ ለሥነ ሕይወት ተማሪዎች፣ ተመራማሪዎች ወይም ተማራሪዎች የቤት ሥራ ይሁናቸው፡፡  
ሞባይሌን አየሁት፡፡ ከሌሊቱ 7፡13 ደቂቃ ይላል፡፡ ነገ 4፡00 ላይ የምፈተነው ፈተና አለኝ፡፡ ምንም እንኳ የምማረው ለሁለተኛ ዲግሪዬ ቢሆንም ቅሉ ውጤቴ ላይ ቀልድ አላውቅም፡፡ ምክንያቱም አሁን ከምሠራበት መሥሪያ ቤት አሰልቺ ልማታዊ ስብሰባና አቆርቋዥ የቢሮ ፖለቲካ ልላቀቅ የምችለው ይህቺን ዲግሪዬን ስይዝ ብቻ እንደሆነ ጠንቅቄ አውቃለሁ፡፡ እርግጥ ነው ሰሞኑን አብዛኛውን ከዕንቅልፌ፣ ጥቂት ጥቂት ደግሞ ከሻይ ሰዐቴም፣ ከቢሮ ወሬ ሰዐቴም፣ ከታክሲ ላይ ቆይታዬም እየቀነጣጠብሁ ጥሩ ስቸክል ከርሜያለሁ፡፡ ትምህርቱ ደግሞ ደስ ይላል፡፡ A ማምጣት እንዳለብኝ ከራሴ ጋር ተስማምተናል፡፡ ዛሬ ሌሊት እስከ 9፡30 ድረስ ተኝቼ ከዚያ በኋላ ያሉትን ሰዐታት ለመጠቀም አስቤ ነበር፡፡ እድሜ ለጎረቤቶቼ እነሆ ለሊቷ ዓይኔ እያያት ሔደች፡፡ ራሴ ይወቅረኝ ጀመረ፡፡ እማማ እልፍነሽ መውጣታቸውን ማየቴ አደፋፈረኝና የመጣው ይምጣ ብዬ መብራቱን አበራሁት!
እንደምንም ራሴን አበረታታሁትና ከአልጋዬ ወርጄ ፊቴን ታጠብሁ፡፡ ወረቀቶቼን ከቦርሳዬ ውስጥ አውጥቼ አልጋዬ ላይ ቁጭ አልሁ፡፡ አንድ ሰዐት ያህል እንዳነበብሁ ዓይኔ ይቆጠቁጠኝ ጀመር፡፡ ዕንቅልፌ እንዳያሸንፈኝ ብዬ ከአልጋዬ ወረድሁና ቆሜ ማንበብ ጀመርሁ፡፡ ብርዱ ሊሰማኝ ሲጀምር አልጋ ልብሱን ለብሼ አልጋ ላይ ቁጭ አልሁ፡፡ የዲጄው ሙዚቃ እየቀነሰ ሔዷል፡፡
*                                  *                           *                                   *
የድሮ ትምህርት ቤታችን ውስጥ ነን፡፡ አባዬ የገዛልኝን አዲሱን ሮዝ ቀሚሴን ለብሻለሁ፡፡ የዓመቱ መጨረሻ ነው፡፡ ሁላችንም ወላጅ አምጥተናል፡፡ የመረብ ኳስ ዳችን ላይ የክፍል ዴስኮቻችን ወጥተው ወላጆቻችንና እኛ ተደርድረንባቸዋል፡፡ ከየክፍሉ ከአንደኛ እስከ ሦስተኛ የወጡ ተማሪዎች እየተሸለሙ ነው፡፡ የኛ ክፍል ተራ ደረሰ፡፡ የአካባቢ ሳይንስ ቲቸራችን መነጽራቸውን አስተካከሉና
“ከሦስተኛ ኤ ተማሪ ምሥራቅ ቢተርፍ ሦስተኛ!” በማለት ጮሁ፡፡
ወላጆቻችን አጨበጨቡ፡፡
ወንዳታ! ሦስተኛ አልወጣሁም ማለት ነው፡፡ አባባ ደግሞ ከአንድ እስከ ሁለት ከወጣሽ የቦሊ ቦሊ ኳስ እገዛልሻለሁ ብሎኛል፡፡
ጓደኛዬ ምሥራቅ ሽልማቷን ተቀብላ ተመለሰች፡፡ ሱዚና ገመድ ዝላይ የሚችላት የለም፡፡ ቦሊ ቦሊ ግን እኔ እበልጣታለሁ፡፡
“ተማሪ ደቻሳ ግርማይ ሁለተኛ!” የስ! አንደኛ ነው የወጣሁት ማለት ነው!
ደቻሳ ስዘልል አየኝና አኮረፈ፡፡ ስለበለጥኩት ነው፡፡ ግን ሽልማቱን ሔዶ ወሰደ፡፡
“ተማሪ በፍቅር አዘዘ አንደኛ! አጨብጭቡላት!” ሰዉ ሁሉ አጨበጨበልኝ፡፡ ምሥራቅ ግን አላጨበጨበችልኝም፡፡ እኔ ግን አጨብጭቤላት ነበረ፡፡
አባዬ ዕቅፍ አድርጎ ሳመኝና “ሒጂ ሽልማትሽን ውሰጂ፡፡” አለኝ፡፡
“አባዬ የቦሊቦሊ ኳሴን ትገዛልኛለህ አይደል?”
“እሺ፡፡ እሱ በኋላ ይደርሳል፡፡ አሁን ሒጂና ተሸለሚ፡፡”
ዳይሬክተራችን በቢጫ ወረቀት የተሸፈነ ነገር ይዘዋል፡፡ ለኔ ነው፡፡ ፈገግ ብለው እያዩኝ ነው፡፡ አካባቢ ሳይንስ አስተማሪያችንም እያጨበጨቡልኝ ነው፡፡ መድረኩ ጋር ልደርስ ነው፡፡ ከኋላዬ የነበረው ጭብጨባ በድንገት ጸጥ አለና “ተንሥኡ ለጸሎት!” የሚል ትእዛዝ ሰማሁ፡፡ ወደኋላዬ ዞር አልሁ፡፡

የእማማ እልፍነሽ ቤተክርስቲያን ዲያቆን ከሞት ለመቀሰቅስ በሚመስል ጩኸት ሽልማቴን ነጠቀኝ፡፡ እስኪ ምናለ በሕልም እንኳ ብሸለምበት?

“እግዚኦ ተሣሃለነ፡፡” ሌላ ድምጽ ተቀብሎ አካባቢውን አንቀጠቀጠው፡፡ ከመሬቷ በስተቀር ሁሉ ነገሯ ቆርቆሮ የሆነችው ቤተክርስቲያኗ አናቷ ላይ የሰቀሉባትን ይህን አገር ገልብጥ ድምጽ ማጉያ እንዴት እንደቻለችው አላውቅም፡፡ "ቆይ ደግሞ “ለጸሎት ተነሡ!” የሚለው ትእዛዝ ቤተክርስቲያን ውስጥ ላለሰው እንጂ እሥራ ላይ ውሎ ደክሞት ቤቱ አልጋ ላይ ማንንም ሳያስቸግር የተኛ ሰውን ነው እንዴ?" ተነጫነጭሁ፡፡ ወረቀቶቼ አልጋው ላይ ተበታትነዋል፡፡ ደብተሬም መሬት ላይ ወድቋል፡፡ ወይ ነዶ!
ሰዐት አየሁ፡፡ ከሌሊቱ 10፡10 ይላል፡፡

“ሰላም ለኵልክሙ!” ቄሱ ቀጠሉ፡፡ ወይ ሰላም! አጠገቤ ቢሆኑ ኖሮ ብዬ ተመኘሁ፡፡
“ለእኔ አሁን ሰላሜ እንቅልፌ ስለሆነ አይበጥብጡኝ! አይጩሁብኝ! ልተኛበት! እኔ እንደእርስዎ በወር ሁለት ሳምንት ሳይሆን በወር አራት ቀናት ብቻ እንዳርፍ የተፈቀደልኝ ግብር ከፋይ ዜጋ ነኝ፡፡ እሑዴን አይሸራርፉብኝ፡፡ እማማ እልፍነሽን ከሆነ እርስዎ ጋር ስለሆኑ በሹክሹክታም ቢናገሩ ይሰሙዎታል፡፡ እኔን ለእንቅልፌ ይተዉኝ፡፡ አሁን ጸሎትዎን ለመካፈልም ሆነ የድምጽዎን መረዋነት ለማድነቅ ጊዜዬ አይደለም፡፡” እላቸው ነበር፡፡ 

ዕንቅልፌ ሲሸሽ ጥሎት በሔደው የድካም ጓዝ ሰውነቴ ደቀቀብኝ፡፡ ትራሱ ቆልምሞኝ ነበረ መሰለኝ አንገቴን በጣም አመመኝ፡፡ አጠገቤ የነበሩትን ወረቀቶች በማንሣት ጥናቴን ለመቀጠል ሞከርሁ፡፡ ከአንድ ሰዐት በላይ ግን መቀጠል አልቻልሁም፡፡ ዓይኖቼ እጅግ ያቃጥሉኝ ጀመር፡፡ ቢያንስ አእምሮዬ በቂ ዕረፍት ካገኘ እስከዛሬ ያጠናሁትን ፈተና ላይ ንቁ ሆኜ እንደምሠራ ራሴን አባበልሁትና የሔደውን እንቅልፌን ለመከተል ቆረጥሁ፡፡ ጠዋት ዕንቅልፍ እንዳይጥለኝም ስልኩን ዐላርም ሞላሁት፡፡ እግረመንገዴንም አሁን 11፡05 መሆኑን አየሁ፡፡ የመስጊዱ ሙአዚን በአረብኛ “ከእንቅልፍ ሶላት ይሻላል!” ሲሉ መጣራት ጀምረዋል፡፡ እኔ ግን ለጊዜው አምላኬን ከጸሎት ይልቅ በሕልም ውስጥ ማየትን መርጫለሁ፡፡ ስለዚህ ልተኛ ነው፡፡ አልጋልብሱን ወደፊቴ ሳብሁትና ተሸፋፈንሁ፡፡
*                                         *                                       *                          *
“ምእመናን ሙሽሮቹ እየገቡ ስለሆነ እልል በሉ! እልል በሉ! እልልልልልልልልልልልልልልልል!”
“በጽሐ መርዓዊ ፍሥሐ ለኵሉ
በሰላም ጻኡ ተቀበሉ፡፡”
ወይ ሰላም! የትልቁ ቤተክርስቲያን ትልቁ ድምጽ ማጉያ በቤተክርስቲያኑ ውስጥ ሁለት ሰዎች ከሁለትነት ወደአንድነት በመምጣት ላይ በመሆናቸው እኔ በምንም ምክንያት ለብቻዬ እንቅልፌን ማጣጣም እንደማልችል ነገረኝ፡፡ ወይ ጣጣ! አሁን እነዚህን ሰዎች ለማጋባት ቤተክርስቲያኑ ውስጥ ያለው ሰው እልል ካለ አይበቃም? ቤታችን ያለን ሰዎች ሁሉ አልጋችን ውስጥ ሆነን እልል ማለት ይጠበቅብናል? ወይስ ቤተክርስቲያኑ ውስጥ የሚደረገውን ነገር በሙሉ እኛ ልንሰማው ያስፈልጋል? እንዴ መስማት ከፈለግን እንመጣ የለም እንዴ የምን ረብሻ ነው?
የእማማ እልፍነሽ ቤተክርስቲያን ካህን ደግሞ “ለእሉ ክልኤቱ ፍጡራን ስብሐተ ፈጣሪ ይደልዎሙ” እያሉ ደመቅ አድርገው ያዜሙ ጀመር፡፡
ሦስቱም ድምጽ ማጉያዎች አንድ ላይ ሲጮሁብኝ ራሴ ዉዉዉ... ይልብኝ ጀመር፡፡
ተኝቶ ከማዳመጥ ውጪ ምንም ማድረግ አልቻልሁም፡፡ ሦስቱንም በደነዘዘ አእምሮ ማድመጥ ጀመርሁ፡፡ አስራ አንድ ሰዐት ተኩል አካባቢ ሙአዚኑ ዝም አሉ፡፡ አሁን የሁለቱ ቤተክርስቲያኖች ድምጽ ማጉያዎች እሪታ ብቻ አካባቢውን ተቆጣጥሮታል፡፡
“ተሣሃልከ እግዚኦ ምድረከ!”
“ሠርዐ ለነ ሰንበተ ለዕረፍተ ዚአነ ፍሥሐ ወሰላም ለእለ አመነ፡፡”
እንቅልፍ በዓይኖቼ ሊዞር አልቻለም፡፡ ይህቺ ሞገደኛ ውስጤ ሒጂና “እኔን ዕንቅልፌን እየነሣችሁኝ እናንተ ሰንበት ለዕረፍት ነው ብትሉ እንዴት ላምናችሁ ይቻለኛል?” በያቸው አለችኝ፡፡ እኔ ግን ዐቅሜን ስለማውቅ ለሌሊት እንቅልፍ ብዬ የቀን ሕይወቴን መቃብር አላወርዳትም ብዬ ተውሁት፡፡

ኪዳኑ አለቀ፡፡ ቅዳሴ ቀጠለ፡፡
“ኵሉ ዘገብራ ለጽድቅ ጻድቅ ውእቱ ወዘያከብር ሰንበተ፡፡”
 …
“ጻኡ ንኡሰ ክርስቲያን፡፡”
ሰዐቴን አየሁት፡፡ 1፡15፡፡ ፈተናዬ ሊጀመር ሁለት ሰዐት ከ45 ደቂቃዎች ይቀሩታል፡፡ እነዚህን ሰዐታት እንኳ ብተኛ ንቁ እሆን ነበረ፡፡ ከመንጋጭላዬ የግራ ጎን አንሥቶ እስከመሐል አናቴ ድረስ እየወጋኝ ነው፡፡ ራስ ፍልጠት የሚባለው መሆን እንዳለበት ገመትሁ፡፡ ጨጓራዬም ክፉኛ መገለባበጥ ጀምሯል፡፡ በጊዜ በወተት ካላበረድሁት እንደተለመደው ሳምንት ሊያስተኛኝ መሆኑ ነው፡፡ ወደ ትምህርት ቤት ሔጄ ቤተ መጻሕፍት ውስጥ ትንሽ ብተኛስ? እንዲያውም ከሸምሱ ሱቅ የላስቲክ ወተት እገዛና እሱን መንገድ ላይ ጠጥቼ እሔዳለሁ፡፡ ከአልጋው ላይ በፍጥነት ወረድሁና ማታ በያቅጣጫው የወረወርኳቸውን ልብሶቼን ከያሉበት ጠርቼ ለባበስሁ፡፡ ጫማዬን አስሬ ቀና ስል የማየው ነገር ሁሉ ነጭ ሆነብኝ፡፡ አዞረኝ፡፡ ቶሎ ብዬ ቁጭ አልሁ፡፡
የእማማ እልፍነሽ ዲያቆን “የተቀመጣችሁ ተነሡ!” ሲል ሰማሁት፡፡
ወይ መነሣት!

ለጥቂት ደቂቃዎች እዚያው ባለሁበት ተቀመጥሁና መለስ እንደማለት ሲልልኝ ቀስ ብዬ ተነሣሁና በሩን ቆልፌ ወጣሁ፡፡
ክሊኒኩ ጋር ስደርስ የሆነ ነገር መሬት ላይ ወድቆ ተመለከትሁ፡፡ ጎንበስ ብዬ አየሁት፡፡ ጠላታችሁ ወከክ ይበል ልቤ ወከክ አለ፡፡ መቶ ብር! እንዴ! ሌሊቱን ሙሉ በእርሱ ስም እንቅልፍ ሲነሱኝ ያደሩትን ተመልክቶ አምላክ ለካሳዬ የሚሆን ነገር አዘጋጀልኝ፡፡ ብድግ አደረግኋት፡፡ ቀና ስል ግን ሰማይ ምድሩ ተደባለቀብኝ፡፡ ምድሪቷ ከሥሬ ከዳችኝ፡፡ ጸጥታ፡፡
*                             *                                          *                                 *
 “በፍቅር! በፍቅር!”
ነቃሁ፡፡  ክንዴ ላይ ግሉኮስ ተቀጥሎልኛል፡፡ ተርፌያለሁ ማለት ነው፡፡ ነጭ ገዋን የለበሰ ረዥምና ወፍራም ሰው አጠገቤ ቆሞ ይጠራኛል፡፡ በዓይን አውቀዋለሁ፡፡ የክሊኒኩ ነርስ ነው፡፡
“አቤት”
“ምን ሆነሽ ነው፡፡” 
“አዙሮኝ፡፡” 
“ስትወድቂ እኔ ከኋላሽ ነበርሁ፡፡ አንሥቼሽ ነው፡፡ ከዚህ በፊት ያምሽ ነበር እንዴ?”
ከጨጓራ በስተቀር የማውቀው ሌላ ሕመም እንደሌለብኝና ሌሊት በእንቅልፍ እጦት እንዴት እንደተሰቃየሁ ነገርሁት፡፡ ፊት ለፊቴ የተሰቀለውን የግድግዳ ሰዐት ተመለከትሁት፡፡ 3፡00፡፡ የአራት ሰዐቱ ፈተናዬ ትዝ አለኝ፡፡ እንደምደርስ አሰብሁ፡፡ አሁን ራስምታቱ ቀለል ብሎልኛል፡፡ ጸጥ ብሏል፡፡

“ታድለህ!” ብዬ ልናገር ስል የቤቱ የፍሎረሰንት መብራት እንደጥንዚዛ መጮህ ጀመረ፡፡
“Great! መብራት መጣ ማለት ነው፡፡” አለ፡፡
በዚያው ቅጽበት ከጎረቤት “ኢየሱስ ጌታ ነው! ኢየሱስ ጌታ ነው! እልልልልልልል!” ተባለ፡፡ አዲሷ የሰፈሬ ፕሮቴስታንት ቸርች ምእመናን ናቸው፡፡ ኪይቦርዱ አጉረመረመ፡፡ አስመላኪው ምእመናኑን ለዝማሬ ጋበዘ፡፡ እስከ ሰማይ ድረስ በእነርሱ ምስጋና ምድርን እንደ ብረት ድስት ክድን እንደሚያደርጓት መንፈሳዊ መፈክር አሰማ፡፡ 
“አሜን! ሀሌሉያ! እልልልል!” ተባለ፡፡ ከዚያም አካባቢው ይቀወጥ ገባ፡፡ 

“የነፍሴ ወዳጅ አንተ በፍቅርህ ልቤን ታሳርፋለህ፡፡”
“እልልልልልል…..!”

እያሉ ይዘምሩ ጀመር፡፡ የጭብጫቦውና የእልልታው ሱናሚ የክሊኒኩን የጭቃ ግድግዳ ያናግረው ገባ፡፡ ነርሱ ምንም እንዳልተፈጠረ ሥራውን ቀጥሏል፡፡ ያው በፊዚካል ምናምን እቋቋመዋለሁ ብሎ ይሆናል፡፡ እኔ ግን “ጃፓንን ያየ በሱናሚ አይቀልድም፡፡” ብዬ የመሐሙድን “ዐቅምን ዐውቆ መኖር ጥሩ ነው፡፡” እየዘፈንሁ ከአልጋው ዱብ፡፡ የምሬን ነው የምላችሁ የሃይማኖት ድርጅቶች በሙሉ እኔ እንዳልተኛ በጠላትነት የተሰለፉብኝ መሰለኝ፡፡ እንዴ! እነርሱ ስለ እረፍታቸው የሚያመሰግኑት ሌላ ሰው ዕረፍት እየነሱ ነው እንዴ? 

ከክሊኒኩ ስወጣ አያቴ ዳዊት ሲደግሙ “መኑ ይሁበኒ ክንፈ ከመ ርግብ እስርር ወአእርፍ” ይሉ የነበረው ትዝ እያለኝ ነበር፡፡
በርሬ አርፍ ዘንድ እንደርግብ ክንፍን ማን በሰጠኝ (መዝ. 55፣6)፡፡

Sunday, February 12, 2012

ንስሐ፣ ፈሪሃ እግዚአብሔርና ፍቅር

በኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖች ዘንድ በትውፊት እጅግ ላቅ ያለ ቦታ ከሚሰጣቸው መጻሕፍት መካከል “ማር ይስሐቅ”“አረጋዊ መንፈሳዊ”ና “ፊልክስዩስ” በመባል የሚታወቁ ሦስት መጻሕፍት አሉ፡፡ የጥቅል ስማቸው “መጻሕፍተ መነኮሳት” ይባላል፡፡ በዋናነት የመነኮሳትን ሕይወት የሚመለከቱ መጻሕፍት ሲሆኑ ብዙጊዜ ለየብቻቸው አንዳንድ ጊዜ ደግሞ ሦስቱም አንድ ላይ በአንድ መድበል ተጠርዘው እንደ አንድ መጽሐፍ ይገኛሉ፡፡ ስለ“አረጋዊ መንፈሳዊ”ና ስለ “ፊልክስዩስ” መወያየቱ ለሌላ ጊዜ ይቆየንና ለዛሬ “ማር ይስሐቅ” ስለሚባለው የ1600 ዓመት የዕድሜ ባዕለ ጸጋ መጽሐፍ ጥቂት እንነጋገር፤ ጥቂትም ከሀብቱ እንካፈል፡፡

ይህ መጽሐፍ ደራሲው “ማር ይስሐቅ” የሚባል የቂሳርያ ሰው እንደሆነ ይነገራል፡፡ ቂሳርያም የተወለደባት ሳትሆን ከአጎቱ ከቅዱስ ኤፍሬም[i] ዘንድ ሆኖ በአካልና በመንፈስ ያደገባት፣ የቅዱሳት መጻሕፍትን ምሥጢር የተማረባትና በክህነት ለእግዚአብሔር የተለየባት ቦታ ናት፡፡ ይሁን እንጂ ወላጆቹ ለክህነት የሚያበቃውን ትምህርት ከተማረ በኋላ ሌላ የዕለት እንጀራውን የሚያሸንፍበት ዓለማዊ ትምህርት እንዲማርላቸው ስለፈለጉ ወደተወለደባት ወደ ሶርያ ይመለስ ዘንድ አጎቱን ቅዱስ ኤፍሬምን ጠየቁት፡፡ በጥያቄያቸው መሠረትም ወደ ወላጆቹ ሀገር ወደ ሶርያ ጉዞ ይጀምራል፡፡ በዚህ ጊዜ የተፈጠረውን ኢትዮጵያውያን ሊቃውንት እንዲህ ሲሉ ይተርኩታል[ii]፡-
ሲሔድ ሳለ ኅሊና ሥጋዊትና ኅሊና መንፈሳዊት ሰውነቱን ሜዳ አድርገው ይራወጡበት ጀመረ፡፡ ኅሊና ሥጋዊት “የካህን ሞያ ተምሬ የሰዎች የበላይ እንደሆንሁ የጨዋ[iii] ሞያ ተምሬ የበላይ እሆናለሁ፡፡ ወይም በሕግ ጸንቼ፣ ሥጋውን ደሙን ተቀብዬ፣ ገንዘቤን መጽውቼ እኖራለሁ፡፡” አለችው፡፡ ኅሊና መንፈሳዊት ደግሞ “ዓለም እንደ ጥላ ያልፋል፤ እንዳበባ ይረግፋል፡፡” ብላ ተሟገተች፡፡ እርሱም ለኅሊና መንፈሳዊ አጋዥ ሆኖ “ቆይ! እዚህ ደርሼ ልምጣ፡፡” ብሎ ዱር ለዱር ሄዶ ከአባ እብሎይ ገዳም ገብቶ መነኮሰ፡፡ በዚያም ለ25 ዓመታት በረድእነት ሲያገለግል ኖሮ አባ እብሎይ ከዚህ ዓለም ድካም በሚያርፍበት ጊዜ “እርሱን ባየሁበት ዓይኔ ማንንም አላይም ብሎ አራዊት ከበዙበት፣ ልላሜ ዕፅ፣ የውኃ ምንጭ ከሌሉበት ቦታ ሔዶ ብሕትውና ያዘ፡፡ በዚያ ብሕትውናው እያለም ይህ መጽሐፍ ተገልጾለት በጽርዕ (ግሪክ) ቋንቋ ጻፈው፡፡[iv]

መጽሐፉ በዐቢይ ጉዳይነት የመነኮሳትን ሥራዎችና ፈተናዎቻቸውን ያስተዋውቃል፡፡ ከፈተና መውጫና ማምለጫ መንገዶችንም ይጠቁማል፡፡ ነገር ግን በውስጡ ያሉ በርካታ ትምህርቶች ላልመነኮሱም ሆነ ለማይመነኩሱ ሰዎች እጅግ የሚጠቅሙ ናቸው፡፡ አንዳንዴ ያስጸልያል፤ አንዳንዴ ይገሥጻል፤ አንዳንዴ ደግሞ ያጽናናል፤ አንዳንዴም በአስተንትኖ ያፈላስፋል፡፡  ነገር ግን በቀላልና ትውልዱ ሊገባው በሚችል ቋንቋ በማቅረብ ረገድ ብዙ ሥራ ይቀራል፡፡[v] ለማንኛውም ዛሬ ከዚህ መጽሐፍ ስለ ንስሐ፣ ፈሪሃ እግዚአብሔርና ፍቅር የተማርሁትን በዘመናችን አማርኛ ላካፍላችሁ (አንቀጽ26፣ ምዕራፍ 1)[vi] ቅድስት ቤተክርስቲያን ስለ ፍቅር ያላትን እይታ ለመገንዘብ በትንሹም ቢሆን የሚረዳ ይመስለኛል፡-

ንስሐ ለተጠመቅን ሰዎች ከጥምቀታችን ቀጥሎ የተሰጠችን ታላቅ ሀብታችን ናት፡፡ በእርሷም ምክንያት የእግዚአብሔርን ቸርነት የምናገኝባት ለሚሹዋት ሰዎች ሁሉ የተከፈተች የይቅርታ በር ናት፡፡ በእርሷ በርነትም ከፈጣሪ ወደሚገኝ ቸርነት እንቀርባለን፡፡ ከእርሷ ከራቅን ግን ይቅርታን ማግኘት አንችልም- አምላካዊው መጽሐፍ እንደሚነግረን “ሁላችን በድለናልና”[vii]፡፡ በእርሷ በኩል ግን ያለአንዳች ዋጋ በነጻ በይቅርታው እንነጻለን፡፡

ንስሐ ምንጯ ምንድነው?
ንስሐ እግዚአብሔርን ከመፍራትና ከሃይማኖት የተነሣ በልቡና ውስጥ የምትወለድ ጸጋ ናት፡፡ ማለትም እግዚአብሔር ፈጣሪያችን፣ መጋቢያችን፣ አባታችን እንደሆነ አምነን ትእዛዛቱን ልንጠብቅ እንደሚገባን በመቀበል “አድርጉ!” የተባልነውን ትእዛዝ ሳናደርግ፣ “አታድርጉ!” የተባልነውን ሕግ ደግሞ ሳናከብር በመቅረታችን ልዑል እግዚአብሔር በአባትነቱ እንደሚያዝንብን፣ በአምላክነቱም እንደሚፈርድብን ማሰብ ስንጀምር ስለ ክፉ ሥራ መጸጸት የሆነችው ንስሐ በእኛ ውስጥ ትወለዳለች፡፡ ክፉ ሥራችንን ከአባታችን ከእግዚአብሔር ፍቅር አንጻር ዓይተን የምናወርደውን የጸጸት እንባ ጠጥታም ትፋፋለች፡፡ የአባታችንን የእግዚአብሔርን ምክንያትየለሽ የማይደበዝዝ ፍቅር አስታውሳም ከወደቅንበት አፈፍ ብለን በመነሣት ክርስትና በተባለው መንገድ በመገሥገሥ ወደአባታችን ቤት እንድንመለስ ትቀሰቅሰናለች፡፡[viii]
ቀስቅሳንም አትቀርም፡፡ በዚህ ከሰው ልጆች ኃጢኣት የተነሣ ሽታው እጅግ በሚከረፋ የትዕቢት ማዕበል በምትናጥ ዓለም ውስጥ ለሚካሄደው የክርስትና ጉዟችንም በሰውም በእግዚአብሔርም ፊት የተሰበረ ልቡናና ትሑት መንፈስ እንዲኖረን በማድረግ  መርከብ ትሆነናለች፡፡ ቀዛፊዎቿም በየጊዜው ፈሪሃ እግዚአብሔርን የሚያስተምሩ መምህራነ ቤተክርስቲያን ናቸው፡፡ የእነርሱን ትእዛዝ መከተልና በምንም ምክንያት ቢሆን ከመርከቧ አለመውረድ ጉዞውን ለማጠናቀቅ ዋስትና ነው፡፡ በመርከብ ያልተጫነ ሰው የውቅያኖስን ማዕበል መሻገርና ከወደብ መድረስ እንደማይቻለው ሁሉ የንስሐ ሕይወት የሌለውና በንስሐ ያገኘውን ጸጋ በተነሳሒ ትሕትና የማይጠብቅ ክርስቲያንም ከወደቡ ሳይደርስ በማዕበሉ ተውጦ ይቀራል- ጉዞው ትዕግስት የሚጠይቅ ረጅም ነውና፡፡ እዚህ ላይ ሰዎች እንደመሆናችን መጠን የጉዞውን ርዝማኔና የማዕበሉን እንግልት ተሰቅቀን የሚከተለውን የመሰሉ ጥያቄዎች በአእምሯችን መመላለሳቸው አይቀርም፡፡ “ወደኋላችን በመመለስ ጉዞውን ብንተወውስ ምን ይቀርብናል?”

ወደቡ
በፈሪሃ እግዚአብሔር በምትቀዘፈው ንስሐ የተባለችው መርከብ ላይ መጓዛችን ከአንድ ወደብ ለመድረስ ነው፡፡ ይኸውም ወደብ ፍቅር ይባላል፡፡ የክርስትና ሕይወትን ውጣ ውረድ በንስሐ መርከብ ላይ በትዕግስት ተጉዘን እስከ መጨረሻይቱ ኅቅታ ስንጸና የዮሐንስ ራእይ ላይ “የሕይወት አክሊል” ተብሎ ከተገለጸውና ሌላው ስሙ ፍቅር ከሚሰኘው ወደብ እንደርሳለን፡፡ የሚገርመው ነገር ይህ ወደብ በጉዟችን ሁሉ አብሮን ይጓዝ የነበረ መሆኑ ነው፡፡ ስሙም የተጓዦች አፍቃሪና ምሳሌ ተጓዥም፣ የደካሞች ምርኩዝና አጋዥ፣ የመንገደኞች አቅጣጫ መሪ ብሩሕ ኮከብ፣  የመርከቧም መድረሻ ወደብ የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ ይባላል፡፡ በጉዟችን ሁሉ በጥበቃውና በረድኤቱ አንድም በቅዱስ ሥጋውና በክቡር ደሙ አብሮን ነበረ፡፡ እንግዲህ ከመነሻው ጀምሮ የያዝነው የጉዟችን ዓላማ ይህንን ወደብ ፊት ለፊት ለማግኘት ነው- ምክንያቱም እዚህ ወደብ ላይ የዓይኖቻችን ቅርፊቶች በቅድስናው ሰይፍ ይገፈፉልንና እርሱን ፍቅር የተባለውን ወደብ እናየዋለንና፡፡ የማይለወጥ እርሱ እኛን ወደፍጹም መንፈሳዊነት ይለውጠናል፡፡ የፍጥረት ዓይን ልታየው የማትችል እርሱን እናየው ዘንድ የማየትን አክሊል ያቀዳጀናል፡፡ ይህ የማየት አክሊልም ራሱ ፍቅሩ ነው፡፡ እዚህ ተአምረኛ ወደብ ስንደርስ ሁሉ በእርሱ አንድ ይሆናል፡፡ ሀገሩ ስሙ ፍቅር ነው፤ የቦታው ንጉሥም ራሱ ፍቅር ነው፤ እኛ ነዋሪዎቹ የምንመገበውም እርሱኑ ፍቅርን ነው፤ ልብሳችንም እርሱው ራሱ ፍቅር ይሆናል፡፡ ዓይኖቻችንም ራሱ ውበት በሆነው በፍቅር እይታ ይነደፋሉ፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ይህን ሀገር ጎብኝቶ ሲመለስ ያየውን ውበት ለመግለጽ የሰው ቋንቋ ቢያጥርበት “ዓይን ያላየው፣ ጆሮ ያልሰማው፣ በሰው ልቡናም ያልታሰበ”[ix] በማለት ከሰው አእምሮ በላይ የሆነ “እጹብ! እጹብ!” ብቻ ብለው የሚያደንቁት መሆኑን መሰከረ፡፡

ይህ እይታ ከጣዕሙ ጣፋጭነት የተነሣ ዘማውያንን ለንጽሕና አብቅቷል[x]፡፡ በትንሣኤ ሙታን የማያምኑ ሰዱቃውያንን በትንሣኤው ሕያዋን እንዲሆኑ አስችሏል[xi]፡፡ ወይንን አብዝተው የሚወድዱትን በጾም የሚተጉ አገልጋዮች አድርጓል፡፡ ኃጢኣተኞችን የዓመጻ መንገድን አስረስቷል፡፡ ድሆችንም በመንግሥተ ሰማያት ተስፋ የከበሩ ባዕለ ጸጎች ወደመሆን ቀይሯል፡፡ ድውያን በእርሱ ተፈውሰዋል፡፡ ድኩማን በእርሱ በርትተዋል፡፡ አላዋቂዎችም በእርሱ የጠቢብነትን ካባ ተጎናጽፈዋል፡፡
ስለሆነም የማዕበሉን እንግልት ተሰቅቀን ወደኋላ ብንመለስ የምናጣው ይህንን ጥዑም ምግብ ሳንመበው እንቀራለን፤ ይህንን የሚያምር መጎናጸፊያ ሳንለብሰው ያመልጠናል፤ ይህንን ልዩ ውበት ለማየት አንችልም፤ በዚህ ልዩ ፍቅርም ሳንነካ ባለመነካታችንም ሳንቀየር እንቀራለን፡፡[xii]

ትሩፋት በመሥራት የደከሙ፣ በገድል ተቀጥቅጠው የኖሩ፣ ጥርጥር በሌለባት ሃይማኖት የጸኑ ጻድቃን የሚያዩት፣ የሚወርሱት ይህንን ሀገር ነው፡፡ ወደእርሱ መድረሻዋ መንገድም “እርስበርሳችሁ ተፋቀሩ፡፡”[xiii] የምትለው የብቸኛው መንገድ የኢየሱስ ክርስቶስ የፍቅር ትእዛዝ ናት፡፡ ፍቅርን ገንዘብ ካደረግናት ወደእግዚአብሔር እንቀርባለን፡፡ የክብር ባለቤት አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ ወደሚያወርሳት መንግሥተ ሰማይም እንደርሳለንም፡፡

ስለሆነም ለፍጹም ፍቅሩ የነቃን ያደርገን ዘንድ እንዲሁም እርሱን በመፍራት በፍቅሩ ለምትወረስ ለመንግሥተ ሰማያት የበቃን ያደርገን ዘንድ በአንድ ልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ እንለምነው፡፡ ከእርሱ ጋር ክብር ጽንዕ ያለው ለዘለዓለሙ አሜን፡፡ 






[i] ቅዱስ ኤፍሬም በኢትዮጵያውያን ትውፊት “ውዳሴ ማርያም” ብለን የምንጠራውን የእመቤታችን ውዳሴ የደረሰው የአራተኛው ክፍለ ዘመን ቅዱስ
[ii] አማርኛውን ተለምዷዊ ለማድረግ እንደዘመናችን አማርኛ አለዛዝቤዋለሁ፡፡
[iii] መሠረታዊ ትርጉሙ ካህን ያልሆነ ግን በማኅበረሰቡ ውስጥ ፍርድና አስተዳደር የተማረ የተከበረ ሰው ማለት ነው፡፡
[iv]መቅድም፡፡” በውስተ ሦስቱ መጻሕፍተ መነኮሳት፡፡ አዲስ አበባ፣ ተስፋ ገብረሥላሴ፣ 1988፡፡
[v] በተለይ አእምሮው ከ20ኛው ክፍለ ዘመን ጀምሮ እየገነነ በመጣው ባዶ ኤሮሳዊ ስብከትና የንግድ ማስታወቂያዎች ፕሮፓጋንዳ የተመላና ከዚህም የተነሣ ምንኩስናንና እስከ ጋብቻ ድረስም ንጽሕናን እጅግ የሚሰቀቀውን ትውልድ በንጽሕና የመኖርን ጥቅምና የምታስገኘውን ታላቅ ጸጋ ለማስተማር ገዳማትን የሥራ ቦታዎች ለማድረግ የሚተጋውን ያህል ገዳማቱን በዕውቀት ማዕከልነት በማበልጸግ እንዲህ ያሉ የሚያንጹ መጻሕፍትን ለትውልዱ በሚገባ ቋንቋ ተርጉሞ ማቅረብ ግድ ይላል፡፡ ለእንዲህ ዓይነቱ ሥራም እያንዳንዱ መነኮስ ታላቅ ኃላፊነት ከትከሻው ላይ እንዳለ ሊሰማው ይገባል፡፡ እንደናትናኤል “ናና እይ!” የሚል ጥሪ ለትውልዱ መቅረብ አለበት- “ወበዘርኢነ ሰማዕተ ንከውን” (“ያየነውን እንመሰክራለን፡፡”) ተብሎ በዮሐንስ ወንጌላዊ እንደተጻፈ፡፡ በኤልያስ መንፈስ የሚሔድና ኤልሳዕን ለእግዚአብሔር አገልጋይነት የሚመለምል፣ የሚያሠለጥን፣ የሚያበቃ አባት ያስፈልጋል፡፡ ልክ እንደቅዱስ ዮሐንስ ቦስኮና እንደኢትዮጵያዊው አባ ኢየሱስ ሞዓ ችግረኞችን ብቻ ሳይሆን ችግኞችንም የሚወድድና የሚፈልግ፣ ፈልጎም በዕውቀትና በመንፈሳዊነት ኮትኩቶ የሚያሳድግ አባት ዛሬ በእጅጉ ያስፈልጋል፡፡ ክርስትና ዛሬ በምዕራቡ ዓለም ውስጥ እየደረሰበት ያለውን ዓይነት መዳቀቅ ነገ በኢትዮጵያ ውስጥ እንዳያጋጥመው ዛሬ እረኞች በእጅጉ መትጋት ያስፈልጋቸዋል፡፡ አለበለዚያ አንድ ፈላስፋ “ከታሪክ የምንማረው ከታሪክ አለመማራችንን ነው፡፡” ያለው ነገር የሚገጥመን ይመስለኛል፡፡
[vi]ማር ይስሐቅ፡፡” በውስተ ሦስቱ መጻሕፍተ መነኮሳት፡፡ አዲስ አበባ፣ ተስፋ ገብረሥላሴ፣ 1988 (ገጽ. 214-218)፡፡
[vii] መዝ. 13
[viii] እዚህ ላይ ር.ሊ.ጳ. ቤኔዲክቶስ Dues Caritas Est (በላቲን “እግዚአብሔር ፍቅር ነው፡፡” ማለት ነው፡፡) በተሰኘው ውብ ጽሑፋቸው “በሐዲስ ኪዳን ፍቅር ትእዛዝ ሳይሆን እኛን በማፍቀር የተነሣ ሰው የሆነልን አምላክ ለሰጠን ፍቅር የምንሰጠው ምላሽ ነው፡፡” ያሉትን ማስታወስ ይቻላል፡፡
[ix] 1ኛ ቆሮ. 2፡9
[x] ጌታ በቀራጩ በስምዖን ቤት ተቀምጦ ሳለ እግሩን በእንባዋ ያራሰችው፣ በጸጉሯም ያበሰችውና ራሱን ሽቱ የቀባችው ባለሽቱዋ ማርያም
[xi] ቅዱስ ቶማስ
[xii] እግረ መንገዳችንን ይህን መዝሙር እናስብ፡-

መንገዴን እንዳልስት
ጌታዬ ሆይ!
በትዕግስት ልጠብቅ
አባቴ ሆይ!
ለሥጋዬ ምቾት
ጌታዬ ሆይ!
ጉዞዬን እንዳልተው ጠብቀኝ፤
ከጉያህ እንዳልወጣ ደጋግፈህ ያዘኝ፡፡ 

እውነተኛ ጽድቅን የምጠማ ልሁን ዘወትር በፊትህ፤
ትንሹን ፈተና ወድቄ እንዳላሳዝንህ፡፡
ውድቀቴን ለሚሻ ጠላቴም አትስጠኝ፤
በድል አክሊልህን እንድቀበል እርዳኝ፤
በድል አክሊልህን ለመቀበል አብቃኝ፡፡
[xiii] ዮሐ. 13፡34

Thursday, February 2, 2012

A Book By H.H. Pope Shenouda III

Hello Friends,

Here is Pope Shenouda III's book The Two Saints Peter and Paul. I have translated it as Brhanate Alem Petros we Paulos.

http://dl.dropbox.com/u/60149977/st.pdf

Enjoy reading,