Friday, February 24, 2012

ዝም


ዛሬ የማካፍላችሁ ግእዝ፣ ዕብራይስጥ፣ ጽርእ (ግሪክ)፣ ላቲን፣ ጣልያንኛ፣ ጀርመንኛ፣ ፈረንሳይኛ፣ እንግሊዘኛ፣ ግእዝና አማርኛ ከሚያውቁት፣ መጽሐፍ ቅዱስን በጉንጫቸው የያዙ የሚመስሉት ግን ትሑት መንፈሳቸው የኔ መምህር ካደረጋቸው የዋኅ መምህሬ የሰማሁትን ነው፡፡

አይሁዳውያን በሒትለር በሚመራው የናዚ ፓርቲ የደረሰባቸውን ጭፍጨፋ ዓለም “Holocaust” ብሎ ይጠራዋል፡፡ የቃሉ መነሻ ግሪክ ሲሆን ትርጉሙም በአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ “የሚቃጠል መሥዋዕት”፣ በእንግሊዘኛ (Burnt offering) ተብሎ የሚጠራውን አንድም ተረፍ ሳይኖረው ሙሉ በሙሉ በመቃጠል ለአዶናይ ይቀርብ የነበረውን የብሉይ ኪዳን መሥዋዕት ያመለክታል፡፡   


ናዚዎችም አይሁዳውያንን እንደ መሥዋዕቱ ብን ብለው ከገጸ ምድር እንዲጠፉ ለማድረግ ነበርና ዓላማቸው ዓለም የሰጠው “Holocaust” የሚለው ስም ተገቢ ይመስላል፡፡ ጽዮናውያኑ ግን በዚህ አይስማሙም፡፡ መሥዋዕት ከሰው ለአምላክ የሚቀርብ ነገር ነው፡፡ በእኛ ላይ የደረሰውን ግን እንኳን እንደመሥዋዕት የሚቀበል አምላክ እንደሰው የሚያስብ ሰው እንኳ ምክንያት ሊሰጥለት የሚችለው ነገር አይደለም፡፡ ስለዚህም በእኛ ላይ የደረሰውን ግፍና መከራ፣ ሰቆቃና ሐዘን ሊገልጽ የሚችል አንድም ቃል የለም ይላሉ፡፡ ነገር ግን የደረሰባቸውን ሁሉ አንድ ቃል ጠቅልሎ እንዲወክልላቸው መርጠውታል፡፡ ይኸውም “ሸቫ” ወይም “ሸዋ” ይባላል፡፡ ትርጉሙም “ዝምታ፣ ጸጥታ” ማለት ነው፡፡ በቃ የደረሰባቸውን ሁሉ፣ አንዳች ወንጀል ሳይሠሩ መሳደዱን፣ መታሰሩን፣ መታጎሩን፣ በመርዝ ጭስ ታፍኖ መገደሉን፣ በሚቆማምጥ ብርድ በረኃብ አለንጋ መለብለቡን፣ የሽማግሌውን መጣል፣ የአሮጊቷን መፈጥፈጥ፣ የእርጉዚቱን መቀደድ፣ የጨቅላውን መጨፍለቅ ወዘተ. “ዝም” ብለው ሰየሙት፡፡ ለካ ዝምታም ይናገራል፡፡ ዝም፡፡


No comments:

Post a Comment