Tuesday, November 11, 2014

ልማትና ባርነት

ልማትና ባርነት አይተዋወቁም፤ ለምን? ዋናውና መሠረታዊው ምንያት ባርያ ለነገ አለመጨነቁ ነው፤ ባርያ ከራሱ ውጭ የሆነ ነገር ምንም የለውም፤ ለራሱም ቢሆን ባለቤት አይደለም፤ ባርያ የጌታው ዕቃ ወይም መሣሪያ ነው፤ ለዕቃ ወይም ለመሣሪያ የሚያስፈልገውን ነገር ሁሉ የሚያስብለት ጌታው ነው፤ ባርያ ለነገ ምን እበላለሁ? ነገ ምን እጠጣለሁ? የት እውላለሁ? የት አድራለሁ? እያለ አይጨነቅም፤ ባርያ ኃላፊነት የለበትም፤ በቅሎ ወይም ፈረስ፤ ወይም ቢላዋ፣ ወይም ማገዶ፣ ወይም ጩቤ፣ ወይም ጠመንጃ ምን ኃላፊነት አለባቸው? ባርያ መብት የለውም፤ ያለው ግዴታ ብቻ ነው፤ ጌታው ለጥቅሙ ሲል ለባርያው ከሚያደርገው ሌላ ግዴታ የለበትም፤ በባርያው ላይ ግን ሙሉ መብት አለው፡፡ በጌታውና በባርያው መሀከል ያለው ግንኙነት በዕቃና በባለቤቱ መሀከል እንዳለው ግንኙነት ነው፡፡ በአጭሩ ባርያ ከሰውነት ደረጃ ወርዶ ዕቃ ሆኖአል፡፡ ለባርያ ትልቁ ነገር ሆዱ ነው፤ በሆዱ ለሆዱ ይገዛል፤ አንዱ ባርያ ለነጻነት እንዳይታገል የሚጠብቀው ሌላው ባርያ ነው፡፡
ልማትና ባርነት አይተዋወቁም ስል ልማት ከሰውነት ባሕርይ የሚመነጭ መሆኑንና ባርነት የሰው ልጅን ከሰውነት ደረጃ የሚወጣ መሆኑን ለመግለጽ ነው፡፡ ልማት የራሱ ባለቤት የሆነን ሰው ይፈልጋል፤ ልማት ለራስ ኑሮና ሁኔታ ኃላፊነትን የሚቀበል ሰውን ይጠይቃል፤ ልማት ማሰብንና ዓላማ መቅረጽን የሚችል ሰውን ዘዴዎች ይፈልጋል፡፡ በአጠቃላይ ልማት ሰው መሆንን ይጠይቃል፡፡ ሰው መሆን ቆሞ ከመሄድ ይበልጣል፡፡

 
መስፍን ወልደ ማርያም፡፡ 2003፡፡ የክሕደት ቁልቁለት፡፡ ንግድ ማተሚያ ድርጅት፣ አዲስ አበባ፡፡   

Tuesday, November 4, 2014

ለግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ንጉሠ ነገሥት ዘኢትዮጵያ
አዲስ አበባ
ግርማዊ ሆይ፣

በአሁኑ ጊዜ በኢትዮጵያ ማኅበራዊ ሕይወት የሚታየውን ምሬትና ግፍ፣ የፍትሕም መጓደል ምክንያት በማድረግ ወደ አገሬ ለመግባት ያለኝን አሳብ ማቆየት ግድ እንደሆነብኝ ለግርማዊነትዎ መግለጥ አስፈላጊ መስሎ ታይቶኛል፡፡ ይህ ሁኔታ የሚታረምበትን በኅብረት ለመሥራት ባንሞክር ታላቅ ብጥብጥ እንደሚያስከትልብን ከታሪክ መማር ካልቻልን፣ ከተከታዩ መቅሰፍት የምናመልጥበትና የምንከለልበት ሰው ሠራሽ ዘዴ ይገኝለታል ብሎ ራስን መደለል በሕልም ዓለም ውስጥ ለመኖር እንደ መፈተን ይቆጠራል፡፡

ከዚህም በቀር ለተተኪው ትውልድ አቋም ይሆናሉ ብለን ተከባክበን ልናሳድጋቸው አላፊነት ያለብንን ሕፃናትና ውለታ ትተው ለማለፍ የተደራጁትን ሽማግሎቻችንንም ደህና ዕረፍት እንዳያገኙ ከአገሪቱ በተፈጥሮ ያገኙትን ዕድል መንፈግ ያሰኛል፡፡ በዚህም ምክንያት በፈጸምነው ስህተት ታሪክ ምሕረት ሊያደርግልን በፍጹም አይችልም፡፡

ይህን የመሳሰለው ሁኔታ በብርቱ የሚያሳስበን መሆኑን ስንገልጥ ምንም እንኳ አንዳንድ ሰዎች ‹‹አንተ ምን አገባህ?›› በማለት በጉዳዩ ባለቤትነት ክፍያ ድርሻችንን ለማሳነስ ቢሞክሩም በኢትዮጵያዊነት ትክለኛ መብት ላይ አጥብበው ያሰመሩትን የወሰን ክልል አሜን ብሎ ለመቀበል ከቶ ስለሚያስቸግር እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ አላፊነቱን የማስወረድ ተግባር እንዳለበት አይካድም፡፡ እኔም ይህን ምክንያት አድርጌ በአሁኑ የመንግሥት አስተዳደር የደረሰውን ሕገ ወጥ አፈጻጸም ሁሉ ለማረምና ፍትሕን ለማደላደል የሚቻልበትን አሳብ በነፃ ለመግለጥ ስል እውጭ አገር መቆየትን መረጥሁ፡፡

በአሁኑ አያያዝ እንዲቀጥል የተተወ እንደሆነ በኢትዮጵያ የወገን መለያየትና የደም መፍሰስ እንደሚያሠጋ የመላው ኢትዮጵያውያን ግምት የወደቀበት ነው፡፡ ዋናው አላማ ይህ እልቂት የሚወገድበት መድኃኒቱ ምንድነው? ለተባለው ጥያቄ ለመመለስ እንደሆነ ጥርጥር የለውም፡፡ መቸም እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ በሚመስለውና በሚያምንበት ረገድ መልሱን ለመስጠት ሞክሯል፡፡ አሁን የጐደለ መስሎ የሚታየው ከዙፋኑ በኩል የሚጠበቀው ይሁንታ ብቻ ነው፡፡ ነገሩን በመጠኑ ለማብራራት ያህል በሚከተሉት መስመሮች አስተያየቴን ለመግለጥ እሰነዝራለሁ፡፡

የኢትዮጵያ ሕዝብ ለዙፋኑ የሰጠው ልባዊ አክብሮት ዘላቂ ሆኖ በታሪካዊ ቅርስነት እንዲጠበቅ በቤተ መንግሥቱ በኩል አልታሰበበትም ለማለት ያስደፍራል፡፡ ባለፈው ‹‹መለኮታዊ መብት›› የተባለው የዘውድ ቴዎሪ የተሳሳተ መሆኑን ቢረዳውም፣ ሕዝቡ፣ ዘውዱን ታሪካዊ ሲምቦል ወይም ምሳሌ አድርጐ በክብር ሊያኖረው ሲፈቅድ ወደ መለኮታዊ መብት አስተያየት እንደገና እንዲመለስና ጣኦታዊ ስግደት እንዲያደርግ ማስገደድ፣ በእልህ ዘውዱን ለማስረገጥ ካልሆነ በቀር ለሌላ አያገለግልም፡፡
ጃንሆይ፣ ባለዘውድ፣ አስተዳዳሪ፣ ሕግ አውጭ፣ ዳኛ፣ ምስለኔ፣ ፖሊስ፣ ጭቃ ሹም ሆኜ ልሥራ ሲሉ፣ በ፳ኛው [20ኛው] ክፍለ ዘመን የሚገኝ ሕዝብ ይህን መብት አጠቃሎ በፈቃዱ ለዘውዱ ብቻ ይለቃል ማለት የማይታመን ነው፡፡ መቸም እየተደጋገመ የሚሰጠው ምክንያት ‹‹ሕዝቡ ኃላፊነትን ለመቀበል አልደረሰም›› የሚል መሆኑን በየጊዜው ሰምተናል፡፡ በውነቱ ከአፍሪካና ከኤሻ ሕዝብ መካከል አልደረሰም ተብሎ በኢትዮጵያ ሕዝብ መፍረድ ይገባልን? ደግሞስ ያለመድረስ ትርጓሜው ምንድነው? ምናልባት የማሰብ፣ የመምረጥ፣ የማመዛዘን፣ የመፍረድ ሴንስ አልተፈጠረለትም ማለት ነው? እንደዚህማ ከሆነ በ፫ሺሕ [በ3 ሺሕ] ዘመን ውስጥ ለዚህ ሕዝብ ጭንቅላት ሆኖ ያሰበለት፣ ዓይን ሆኖ ያየለት፣ ጆሮ ሆኖ የሰማለት የዛሬው ዘውድ ነው ማለት ነዋ! የሚፈተነው ይህን የመሰለ አስተያየት ለማቅረብ እንደሆነ ምሕረት የሌለው በደል ነው፡፡

ይልቁንስ ጃንሆይ የሕግ ጠባቂነትን ልብስ ተጐናጽፈው በዚህ መንፈስ ፍትሕን ከሚያጓድሉ፣ ሥልጣኑን ለሕዝብዎ ሰጥተው እርሱ ቢጨነቅበት እንደሚሻል ጥርጥር የለውም፡፡ ያለዚያ ከዚህ ማስታወሻዬ ውስጥ ለስማቸው እንኳ ሥፍራ ለመስጠት ዋጋ የሌላቸውና ሕሊና ቢሶች የሚያቀርቡልዎትን ‹‹ደህና ታይቷል›› እያሉ ፍትሕን ለግል ስሜት መወጫ ማድረግ የቱን ያህል ለትውልድ መተዛዘቢያ ሆኖ እንደሚኖር የተሰወረ ሊሆን አይችልም፡፡

ይህን ተስፋ አስቆራጭ ሁኔታ ለማሻሻል የሚቻለው ጃንሆይ ዘውዱን ለራስዎ አስቀርተው አስተዳደሩን ለሕዝብ በመስጠትና የዴሞክራሲን መንፈስ በማስገባት ነው፡፡ ነገር ግን ይህ አስተያየት ለግርማዊነትዎ ሰውነት አለርጂ ሆኖ ቢያስቸግርም እንኳ ሌላ ማማረጫ ይኖራል፡፡ ይኸውም ዘውዱን ለልዑል አልጋ ወራሽ ማስተላለፍና አብዲኬት ማድረግ ነው፡፡ እርሳቸው ሕገ መንግሥት ጠብቀው ለመኖር ፈቃደኛ እንደሆኑ አያሌ ሰዎች ሲመሰክሩላቸው ሰምቻለሁ፡፡ ያለዚያ ተከታዩ ትርምስና ደም መፋሰስ እንደሚሆን ጥርጥር የለውም፡፡

ይህ አቤቱታ ከኔ ብቻ የቀረበ አይደለም፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ በፍርኃት ታፍኖ ነጋም መሸም የሚያጕተመትመው ይህንኑ ነው፡፡ ድምፁን ከፍ ለማድረግ ግን አካባቢው አልፈቀደለትም፡፡ እኔም ከርሱ የተለየሁ መስዬ ታይቼ እንደሆነ ያጋጣሚ ነገር ብቻ ነው፡፡ አዲስ አበባ የታፈንኩትን ያህል እዚህ ከተነፈስሁ በኋላ ወደ አገሬ እንድመለስ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ ምናልባት ይህን አቤቱታ በመጻፌ እወነጀል ይሆናል፡፡ ግድ የለም፡፡ የሆነ ሆኖ በትእዛዝ ሳይሆን በነፃ የሚፈርድና በግልጽ የሚያስችል ፍርድ ቤት ተቋቁሞ ራሴን በሕጋዊ ጠበቃ አማካይነት ለመከላከል ጃንሆይ የሚፈቅዱልኝ ከሆነ በአገሬ ውስጥ ለመተንፈስ ዕድል ተሰጠኝ ማለት ነው፡፡
ከዚህም ሁሉ ጋር ላስታውሰው የምፈቅደው፣ ይህን ማስታወሻ በመጻፌ ተቀይመው የእኔን ሕይወት ለማስጠፋት በሺሕ የሚቆጠር ገንዘብ እንደሚወጣ ጥርጥር የለውም፡፡ አዝናለሁ፡፡ እኔ ለሞት የተዘጋጀሁ ስለሆነ ገንዘቡ ባይባክንና ለነፍሰ ገዳይ በመስጠት ፈንታ ለጦም አዳሪ ችግረኛ ቢውል የበለጠ እንደሚጠቅም ጥርጥር የለውም፡፡ በበኩሌ በአገራችን ሬሾሉሽን እንዲነሣና የማንም ደም እንዲፈስ አልፈቅድም፡፡ በዚህ ባቤቱታዬ የምወተውተውም ሰላማዊ ለውጥ እንዲሆንና የምንፈራው ደም መፋሰስ እንዳይደርስ ስለሆነ ጃንሆይ አንድ ቀን ‹‹ለካ ብርሃኑ ውነቱ ኖሯል!›› ሳይሉ አይቀርም፡፡

እንኳን ዘውድ የጫነ ሰውነትንና ማናቸውንም ሰው የማክበር ልምድ ስላለኝ፣ ይህ አቀራረቤ ክብርን ለመድፈር እንደማያስቆጥርብኝ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ ውነት ሁል ጊዜ መራራ ናት፡፡ የመድኃኒት ፈውሱ እንጂ ምሬቱ አይታሰብም እንደተባለው ይህ በቅን ልቡና የቀረበው ውነተኛ አቤቱታዬ የግርማዊነትዎን ልብ አራርቶ ለኢትዮጵያ ማኅበራዊ ሕይወት አንድ ፈውስ እንዲያመጣለት ተስፋ አደርጋለሁ፡፡

ጃንሆይ! በኢትዮጵያ ወጣቱ ሽማግሌው ሴቱ ወንዱ የአኗኗሩ ዘዴ ውሉ ተዘባርቆበታል፡፡ አምላካችን፣ ፈጣሪያችን እያለ ቢደልልዎት አይመኑት፡፡ ጨንቆት ነው፡፡ ከልብ የሚመርቅዎት ግን ራስህን አስተዳድር ብለው አርነት ሲያወጡትና ወደ ዴሞክራሲ ሲመሩት ነው፡፡ ይህንንም ስል ሕዝብ በራሱ ሲተዳደር ችግር አይገጥመውም ማለቴ አይደለም፡፡ እስከዚህ አልሳሳትም፡፡ ነገር ግን ሌላው ለፍቶ ከሚጥለውና ላንሣህ ከሚለው፣ ራሱ ወድቆ በራሱ መነሣትን ይመርጣል፡፡ ይኽም በሥሕተት መማር ይባላል፡፡ ስለዚህ ጃንሆይም ተሳሳቱ እያለ ከሚከስዎት እርሱ ለሥሕተት እንዲጸጸትና እንዲማር ቢያደርጉት ትልቅ ውለታ ይቆጠራል፡፡
የዛሬው ሕገ መንግሥት ዴሞክራሲን ለማስገንባት የሚረዳ ካለመሆኑም በላይ ያንኑም ቅሉ አክብሮ ለመጠበቅ በአንቀጽ ፳፩ [21] እንደተመለከተው ከንጉሠ ነገሥቱ በመሐላ የተሰጠው ቃል ፈርሷል እያሉ አያሌ ኢትዮጵያውያን እንደሚያማርሩ ግርማዊነትዎ ሳይሰማው አይቀርም፡፡ መቸም ሕገ መንግሥቱን፣ ለመጣስ አንድ የጽሕፈት ሚኒስቴር ደብዳቤ ይበቃል፡፡ እንግዴህ ሕዝቡ ወይም ሹማምቱ ለንጉሠ ነገሥቱ ታማኝ ነኝ እያሉ ቢምሉም፣ ንጉሠ ነገሥቱ በበኩሉ መሐላውን የሚጠብቅ ካልሆነ በመሐላቸው ታስረው እንደማይኖሩ በልጅ ኢያሱ ጊዜ የደረሰው ሁኔታ ምሳሌ ሊሆን ይችል ይመስለኛል፡፡

በአሁኑ ጊዜ የገጠመንን ፕሮብሌም እንደ መጠኑ ለመግለጥ ‹‹በግርማዊነታቸው መንግሥት ያገኘሁት ኤክስፔሪያንስ›› የሚለው መጽሐፌ በሙሉ ታትሞ እስከወጣ ድረስ ፲፪ኛውን [12ኛውን] ምዕራፍ ከዚህ ጋር አያይዤ ለግርማዊነትዎ በትህትና አቀርባለሁ፡፡
ዋሽንግተን ግንቦት ፳፭/፶፯ [ግንቦት 25/57]
ከታላቅ አክብሮታዊ ፍርሐት ጋራ
ብርሃኑ ድንቄ

Saturday, November 1, 2014

ቡርኪና ፋሶ፤ የሐቀኞች ምድር


ከቅኝ ግዛት ወደ ነጻነት
ከ1896 ጀምሮ እስከ 1960 ድረስ ለ65 ዓመታት በፈረንሳይ ቅኝግዛት ሥር ስትማቅቅ የኖረች ሀገር ናት፡፡ ፈረንሳውያኑም “የፈረንሳይ የላይኛው ቮልታ” እያሉ ነበር የሚጠሯት- በሀገሪቱ ውስጥ የሚፈሱትን ጥቁሩ ቮልታ፣ ነጩ ቮልታና ቀዩ ቮልታ የሚባሉ የሦስት ወንዞቿን ስም መሠረት አድርገው፡፡ በ1960 ዓ.ም. ከፈረንሳይ ቅኝ ግዛት ስትላቀቅ ደግሞ ስሟ “የፈረንሳይ” የሚለውን ሸክም አራግፎ “ሰሜናዊ ቮልታ” ተባለ፡፡ የመጀመሪያ ፕሬዚደንቷም ማውሪስ ያሜዖጎ ኾኑላት፡፡
የአምባገነን አዙሪት ፅንስ
ማውሪስ ያሜዖጎ ወደ ሥልጣን በመጡ ማግሥት የቮልታ ዴሞክራሲያዊ ኅብረት ከሚባለው የእርሳቸው ፓርቲ ውጪ ሌሎች የሀገሪቱን ፓርቲዎች በሙሉ ከእንቅስቃሴ አገዱ (ልማቱን ለማቀጠል 60 ዓመት የእኛ ፓርቲ ሥልጣን ላይ መቆየት አለበት፤ ሌሎቹ ፓርቲዎች ፀረ ልማት፣ ፀረ ዴሞክራሲ፣ ፀረ ምንጥስዮ፣ ፀረ ቅብርጥስዮ፣ ወዘተ. ናቸው ብለውም ዲስኩር አሰምተውም ይኾናል፤ እንጃ!)፡፡ በድርጊታቸው ያዘነው ፖለቲካዊ ተሳትፎው የታፈነበት ሕዝብ በ1966 በተማሪዎች፣ የሠራተኛ ማኅበራትና የመንግሥት ሠራተኞች ሀገሪቷን በአድማና በሰልፍ አንቀጠቀጧት፡፡ 
የሀገሪሽ መረበሽን ለማስቆም በሚል ሰበብም ጦር ሠራዊቱ በጉዳዩ ላይ እጁን አስገባና ሕገ መንግሥቱን አገደ፤ ፓርላማውን በተነ፤ ፕሬዚደንት ያሜዖጎንም ከሥልጣናቸው አባረራቸው፡፡ ከዚያ በኋላ ሀገሪቱ ምንም የተረጋጋና ኹሉን ያማከለ መንግሥት ልታገኝ አልቻለችም፡፡ አንዱ ወታደር በሌላው እየተፈነቀለ እስከ 1987 ድረስ ሌተፍናንት ኮሎኔል ሳንጎሌ ላሚዛና፣ ኮሎኔል ሳዬ ዜርቦ፣ ሜጀር ዣንክላውድ ኦዌድራዖጎ፣ ካፒቴን ቶማስ ሳንካራ የሚባሉ አራት ወታደሮችን መሪዎች አድርጋ አፈራርቃለች፡፡ 

ቶማስ ሳንካራ ጠቅላይ ሚኒስትር ሲኾኑ “ለውጥ ያስፈልጋል!” በሚል መፈክር ነበር፡፡ “ሀገሪቱ ለውጥ ያስፈልጋታል፤ ለውጡ የሚጀምረው ደግሞ ከስሟ ነው፡፡” በማለትም የሀገሪቷን ስም ከሰሜናዊ ቮልታነት ወደ ቡርኪና ፋሶ ቀየሩት፡፡ ስሙን የፈጠሩት ራሳቸው ቶማ ሳንካራ ናቸው፡፡ ቃሉን ለማበጁትም ሙሬ እና ዲዮላ ከሚባሉ የሀገሪቱ ኹለት ዐበይት ቋንቋዎች አንድ፣ አንድ ቃል ተውሰዋል፡፡ በሙሬ ቋንቋ “ቡርኪና” ማለት “ሐቀኛ” ሲኾን፣ “ፋሶ” ደግሞ በዲዮላኛ “አባት ሀገር” ማለት ነው፡፡ እነዚኽን ኹለት ቃላት አገጣጠሙና ቡርኪና ፋሶ አሏት- “የሐቀኞች ምድር”፡፡

ልማታዊው ካምፖሬና እንከን የለሽ ምርጫዎቹ 

ይኹን እንጂ፣ የቶማስ ሳንካራ መንግሥት ብዙም አልከረመም፡፡ በ1987 በካፒቴን ብሌይስ ካምፖሬ የተመራ መፈንቅለ መንግሥት ቶማስ ሳንካራን ገድሎ የመፈንቅለ መንግሥቱን መሪ፣ ብሌይስ ካምፖሬን፣ የሀገሪቱ ፕሬዚደንት አደረገ፡፡ ከ1987 ጀምሮም እስከ 2014 ድረስ ካምፖሬ ሀገሪቱን ሕዝቧን እንደ ሰም አቅልጦ እንደ ገል ቀጥቅጦ ገዛቸው፡፡ ምዕራባውያን ወዳጆቹም፣ በተለይም ደግሞ የቀድሞዋ ቅኝ ገዢ ፈረንሳይ፣ ቡርኪና ፋሶ በካምፖሬ ዘመን ፈጣን ምጣኔ ሀብታዊ ዕድገት እንዳሳየች፣ ሰላም እንደሰፈነባት መሰከሩለት፡፡ እርሱም ዴሞክራሲያዊነቱን ለማመስከር በ1990፣ በ1998፣ በ2005፣ በ2010 “እንከን የለሽ” ሀገር ዐቀፍ ምርጫዎችን አካኺዷል፡፡ የምርጫዎቹ ኹሉ አሸናፊም “ልማታዊው ካምፖሬ” ነበር፡፡ 

ሀገሪቱ ፓርላማ ቢኖራትም ፓርላማው ካምፖሬ አፍንጫውን ሲሠረስረው የሚያስነጥስ፣ ካምፖሬ ሲከፋው የሚያለቅስ፣ ካምፖሬ ሲቀልድ የሚስቅ የአሻንጉሊቶች ሸንጎ ኾኖ ነበር፡፡ 



 እንደ አምነስቲ ኢንተርናሽናል ያሉ ዐለምዐቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች ካምፖሬን ዐይንኽ ላፈር ካሉት ቆይተዋል፡፡ አገዛዙ በየጊዜው በጋዜጠኞችና የሀገራቸው ዕድል ፈንታ ጽዋ ተርታ ያገባናል በሚሉ ዜጎች ላይ የሚያደርሰው አፈና፣ ወከባ፣ ሥቃይ፣ ግድያና ምንዳቤ ምን ያኽል ከባድ እንደኾነ በየጊዜው ተጽፏል፤ ተነግሯልም- ካምፖሬ የዝኆን ዦሮ ይስጠኝ አለ እንጂ፡፡ ሕዝቡም “ሸጌዋ መቻል ምን ይከፋል፤ ሆድ ካገር ይሰፋል” እያለ ቻለው፡፡

የሕዝብ ቁጣ

ካምፖሬ ሥልጣን ላይ ከወጣ በኋላ እንደቀልድ 27 ዓመታት ነጎዱ፡፡ እርሱ ግን “የልማቱ ጉዳይ በጥብቅ ስላሳሰበው”ና እርሱ ከሌለ ልማቱ እንደሚቋረጥ ስላመነ "የልማቱን ቀጣይነት ለማረጋገጥ" የአሻንጉሊቶቹን ሸንጎ ሰብስቦ የሥልጣን ዘመኑን የሚያራዝም ሕግ እንዲያወጡለት ጠየቃቸው፡፡