Thursday, February 21, 2013

“ከቶ አታጥበኝም!”



ታጥቀኽ ጨርቅን ለማበሻ፣
ልታጥበኝ እግሬን ስትሻ፣
“ከቶ አታጥበኝም!” ብዬ፣
በግብዝነት ተሰናክዬ፣
መስቀሌን ከእኔ እንዳላርቅ፣
   በ“እኔ” ታንቃ ነፍሴ እንዳትማቅቅ::


የጌቴሴማኒን ሐዘን ጭንቀት፣ የጲላጦስን አለንጋ፣
የጭፍሮችን የሾኽ አክሊል፣ የሄሮድስን ቀይ ካባ፣
የመስቀልን ጽዋ ተርታ፣
የጎልጎታን ዕድል ፈንታ፣
ፈርታ…
ሳትካፈል እንዳትቀር የትንሣኤኽን ሰላምታ…

አሜን! ውዴ ሆይ! እጠበኝ፡፡





ገመዴ ባማረው ስፍራ፣ በአንተነትኽ ላይ ትውደቅ፤
ርስቴም መስቀልኽ ኾኖ ዘለዓለም ፏ! ብሎ ይድመቅ፤
ነፍሴ ካለማመኗ፣ ከፍርኀቷ ዕድፍ ትላቀቅ፡፡

አሜን፡፡ አባቴ፡፡
በሂሶጵ እርጨኝ እጠበኝና፣
ዕድሌ በዕድልኽ ይጽና፡፡
                                 

Tuesday, February 19, 2013

አንተ ትሕትና ነኽ፡፡


ሙሴን መሪ ሊያደርገው ከቤተመንግሥት አውጥቶ የበግ እረኛ ያደረገ፣ ሳዖልን ለአህያ ፍለጋ በወጣበት ለንግሥና የቀባ፣ በቤተሰቦቹ ዘንድ ሳይቀር ከቁብ የሚቆጥረው የሌለውን በግ ጠባቂውን ዳዊትን የ12 ነገድ እረኛ አድርጎ የሾመ፣ ከዳዊት ድካም ሰሎሞንን ያኽል ጠቢብ የፈጠረ፣ በበረት ተወልዶ እጅ መንሻ የተቀበለ፣ በግርግም ተኝቶ ሰብአ ሰገል የሰገዱለት፣ በከብቶች ተከብቦ መላእክት የዘመሩለት እርሱ እነሆ ከነመፈጠራቸው እንኳ ለማንም ትዝ የማይሉ፣ እዚህ ግባ የሚባል ቦታ በማኅበረሰቡ ውስጥ የሌላቸውን ዓሣ አጥማጆች ለወንጌል ሥራ ጠራ፡፡ 
አዎን ጌታ ሆይ! አንተ ትሕትና ነኽ፡፡


ጴጥሮስ ገራገሩ የቤተሰብ ኀላፊነቱን ትቶ አዲስ ናዝራዊ ይከተል ዘንድ እንዴት አስቻለው ?

ያዕቆብና ዮሐንስስ አባታቸውን ከነጀልባው ትውት አድርገው ለመጓዝ እንዴት ጨከኑ?

ሌዊስ የቀራጭነት ወንበሩን፣ የተደላደለ ኑሮውን ትቶ ለመኼድ ምን አተጋው?

ጌታ ሆይ ! በልባቸው ስላበራኸው ፍቅርኽ እነርሱ ይህን ኹሉ ትተውታል፡፡ እኔንም በፍቅርኽ ብርሃን አጥለቅልቀኝና እስከ መጨረሻዋ ኅቅታ ድረስ ኹሉን እየተውኹ ልከተልኽ፡፡

በአሳራፊው ቅዱስ ስምኽ፡፡

አሜን፡፡