Thursday, July 20, 2023

ዘመን ፣ ምልክት እና እርሾ

 (ሠኔ ፳፭/፪ሽ፲፭ ዓ.እ)  ቆሮ ፪፡ ፲፥ ፩-ፍ፡ም፤ ጴጥ ፩፡ ም. ፭፥ ፩-ፍም፤ ግብ፡ ሐዋ ፳፥ ፳፰-ፍ፡ም፤ መዝ. ፸፫(፸፬)፥  ፲፯-፲፰፤ ማቴ፡ ም. ፲፮፥ ፩-፲፫ ። 

የእርሻ ዑደትንና የወቅቶች መፈራረቅን የሚከተለው የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን የግብረ አምልኮ ካሌንደር ከሠኔ 25 እስከ መስከረም 25 ያለውን ጊዜ የክረምት ዘመን ብሎ ይጠራዋል።  ከሠኔ 26 እስከ ሐምሌ 18 ያለውን ጊዜ ደግሞ “የክረምት መግቢያ” ይባላል። ስለዚኽም ዛሬ የሰማናቸው ምንባቦች በሙሉ ስለዝናብ፣ ደመና፣ ዘር ስለ መዝራት ያነሣሉ። የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የገበሬዎች ቤተ ክርስቲያን ኾና ስለኖረች ሥርዓተ አምልኮዋ ከግብርና ሥራ ጋር የተስማማ እንዲኾን የተሠራ ነው። 

የወንጌል ምንባባችን ጌታ ኢየሱስ በጣም ካዘነባቸው ጊዜዎች አንዱን አሳይቶናል። ፈሪሳውያንና ሰዱቃውያን ቀርበው ከሰማይ ምልክት እንዲያሳያቸው ጠየቁት። በዚኽ ጊዜ የተሰማውን ሐዘን ሲገልጥ ወንጌላዊው ቅዱስ ማርቆስ “በመንፈሱ እጅግ ቃተተ” “ἀναστενάξας τῷ πνεύματι αὐτοῦ ይላል (ማር 8፡ 12)። በነቢዩ ኢሳይያስ (65፡2) የተነገረው “መልካም ባልኾነው መንገድ ሐሳባቸውን እየተከተሉ ወደሚኼዱ ወደ ዓመፀኛ ሕዝብ ቀኑን ሁሉ እጆቼን ዘረጋኹ!... ''እኔ ከአንተ ይልቅ ቅዱስ ነኝና ወደ እኔ አትቅረብ!' ይላሉ። እነዚኽ በአፍንጫዬ ዘንድ ጢስ፣ ቀኑንም ኹሉ የምትነድ እሳት ናቸው” ይላል። እጅግ ጥልቅ ሐዘን ነው ። የእግዚአብሔርና የሰው የተግባቦት መሥመር በሰው ኃጢኣት መሰበሩን በግልጥ ያሳያል። እግዚአብሔር ይሠራል፤ ሰው ግን የእግዚአብሔርን ሥራ ያይ ዘንድ ዓይኖቹ ተጋርደዋል። ጌታ ኢየሱስ ልቡ እጅግ ስለተሰበረ ጥያቄ ይጠይቃቸዋል፣ “በመሸ ጊዜ 'ሰማዩ ቀልቷልና ብራ ይኾናል ትላላችኹ። ማለዳም፣ 'ሰማዩ ደምኖ ቀልቷልና ዛሬ ይዘንባል' ትላላችኹ። የሰማዩን ፊትማ መለየት ታውቃላችኹ። የዘመኑንስ ምልክት መለየት አትችሉምን?” ሦስት ነጥቦችን እናንሳና ራሳችንን እንመልከት።

1. ዘመን:- በዚኽ ቦታ ላይ ዘመን ተብሎ ወደ አማርኛ የተተረጎመው የግሪክኛ ቃል καιρῶν የሚል ነው። ትርጉሙም የእግዚአብሔርን የሥራ ክንውን እንጂ ተራ ሰዓት ቆጠራ አይደለም። እዚኽ “ዘመን” ተብሎ የተገለጸው ጊዜ ከእግዚአብሔር አኳያ ሲታይ የሚኖረው ትርጉም ነው። ሰው እግዚአብሔር እንዲኽ ይሠራል ብሎ ለእግዚአብሔር የሥራ ዝርዝር አውጥቶ መቀመጥ ይፈልጋል። በዚኽም ምክንያት እግዚአብሔር በተሻለው፣ በሚበልጠው፣ ለዘለዓለም ሕይወት በሚኾነው መንገድ እየሠራ ያለውን ሥራ ሳይመለከት ይቀራል። ብዙ ጊዜም ሲቃረነው ይገኛል። ፈሪሳውያን እግዚአብሔርንና አሠራሩን እንደሚያውቁ እርግጠኞች ነበሩ። ስለኾነም፣ እያዩ ሳያዩ፣ እየሰሙም ሳይሰሙ ቀርተዋል። የእግዚአብሔርን አሠራር ባለማስተዋላቸው ጻድቁ ሰው አሳድደው ገድለውታል። በሥጋ የተገለጠውን የእግዚአብሔርን አሠራር ማስተዋል ስለተሳናቸው ለብዙ ዓመታት የጠበቁት ዕድል አምልጧቸው እነርሱም፣ ከተማቸውም ጠፍተዋል። ስለዚኽ፣ እንደእነርሱ የጥፋት መንገድን ላለመከተል የቤተ ክርስቲያን መሪዎች ዘወትር ራሳቸውም መጠየቅ አለባቸው። እያንዳንዱ የቤተሰብ ኃላፊም እግዚአብሔር በቤተሰቤ ውስጥ ምን እየሠራ ነው? ብሎ ቆም ብሎ ማጤን አለበት።  እያንዳንዳችን ምእመናንም እግዚአብሔር በእኔ ሕይወት ውስጥ ዛሬ የት ነው? በየቀኑ ራሳችንን በመፈተሽ አሠራሩን መፈለግ፣ ማግኘት፣ መከተል አለብን። ብዙ ጊዜ ልክ እንደፈሪሳውያንና ሰዱቃውያን ትኩረታችን እግዚአብሔር እንዲያደርግ የምንፈልገው ነገር እንጂ እርሱ ፈልጎ እያደረገ ያለው ነገር አይደለም። ስለዚኽም፣ ከእርሱ ሥራ ጋር መተባበር ያቅተናል። ከእርሱ ጋር አንድ በመኾን ሕይወትን መልበስ ያቅተናል። ፈሪሳውያንን “ትቷቸው ኼደ!” እኛንም ለፈቃዳችን ትቶን እንዳይኼድ ራሳችንን እንመልከት። እግዚአብሔር እኛን የማኖር ግዴታ የለበትም።                        

2. ምልክት:- የእግዚአብሔር አሠራር ምልክቶች አሉት። እነዚኽ ምልክቶችም እውነተኝነት፣ ጭምትነት፣ ጽድቅ፣ ንጽሕና፣ ፍቅር፣ መልካም ወሬ፣ በጎነት፣ ምሥጋና፣ የቅዱሳን ሐዋርያትን ኑሮ መከተል፣ ደስታ፣ ሰላም፣ ትዕግሥት፣ ቸርነት፣ በጎነት፣ እምነት፣ የውሃት፣ ራስን መግዛት ይባላሉ (ፊልጵ 4፡8፤ ገላ 5፡ 23)። እነዚኽ ባሉበት እግዚአብሔር አለ። እነዚኽ በሌሉበት እንቅስቃሴ ኹሉ ግን እግዚአብሔር የለም። ፍጻሜውም ጥፋት ብቻ ነው። ቤተሰብም ይኹን ግለሰብ፣ ማኅበረሰብም ይኹን ሀገር እነዚኽ ከሌሉት እግዚአብሔር በእርሱ ዘንድ እንደሌለ ይወቅ። ከእግዚአብሔር አሠራር ጋርም ኅብረት እንደሌለው ይረዳ። 

3. እርሾ:- የእግዚአብሔርን አሠራር ለይቶ ማወቅ ከፈሪሳውያን እርሾ ያድናል። እርሾ ጥቂት ኾኖ ሊጡን ኹሉ እንደሚያቦካው የእግዚአብሔር አሠራርን ለይቶ ዐውቆ አለመከተል እንደፈሪሳውያን እግዚአብሔርን በብሔራዊ ኩራታቸውና ሀገራዊ ሕልሞቻቸው አምሳል ለማበጀት፣ እንደሰዱቃውያን እግዚአብሔርን እናመልካለን እያሉ ለጥቅምና ለምቾት እየሰገዱ መኖርን ያመጣል። ከፈሪሳውያንና ከሰዱቃውን እርሾ ካልተጠበቅን የእግዚአብሔርን አሠራር ለማጤን አንችልም። ጌታችን ኢየሱስ ትናንት ደቀ መዛሙርቱን “ከፈሪሳውያንና ከሰዱቃውያን እርሾ ተጠበቁ!” ያላቸው፣ ዛሬም እኛን “ከፈሪሳውያንና ከሰዱቃውያን እርሾ ተጠበቁ!” እያለ የሚያስጠነቅቀን ለዚኽ ነው። ከፈሪሳውያን እርሾ የማይጠበቅ ሰው እግዚአብሔር ሕልሙን እንዲያሳካለት ይፈልገዋል እንጂ “ፈቃድኽ በሰማያት እንደኾነች እንዲኹም በምድር ትኹን!” ብሎ የኢየሱስ ክርስቶስን መንገድ አይከተልም። ራስ ወዳድነትን እንጂ ፍቅርን ስለማይከተል መስቀል ጌጥ እንጂ ድል አይኾነውም። በምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን ከክርቶስ ጋር አንድ ኾኖ የሚኖር አንድ የመካከለኛው ዘመን ክርስቲያን ግን የፈሪሳውያን እርሾ ከእርሱ እንዲርቅ እንዲኽ ሲል ጸልዮ ነበረ፦ 


ጌታ ሆይ! 

የሰላምኽ መሣሪያ አድርገኝ።

ጥላቻ ባለበት ፍቅርን እንድዘራ

ቂም ባለበት ዕርቅን እንድዘራ 

ጥርጥር ባለበት መተማመንን እንድዘራ

ሐዘን ባለበት ደስታን እንድዘራ 

ጨለማ ባለበት ብርሃንኽን እንድዘራ ስጠኝ። 

ጌታ ሆይ!

ከመጽናናት ይልቅ ማጽናናትን 

ሰዎች ይረዱኝ ከማለት ይልቅ ሰዎችን መረዳትን 

ከመወደድ ይልቅ መውደድን እንድፈልግ 

ጸጋኽን ስጠኝ። 

የምንቀበለው በመስጠት 

ይቅር የምንባለውም ይቅር በማለት 

ሕያዋን የምንኾነውም ከአንድ ልጅኽ ጋር በመሞት ነውና። 

ክብርና ምሥጋና ለቅዱሱ ስምኽ ይኹን! አሜን።  


Tuesday, November 15, 2022

“አባት ልጁን ይወዳል ሁሉንም በእጁ ሰጥቶታል።” ዮሐ. 3፡ 37

መዝሙር፦ ትዌድሶ መርዓት  

ምንባባት፦ ኤፌ 5፡ 21 ፤ ራእ 21፡ 1 ሐዋ 21፡ 31 መዝ 127፡ 2 ዮሐንስ 3፡ 25   

ዛሬ የሰማናቸው ምንባቦች በሙሉ (ከሐዋርያት ሥራ በስተቀር) “ሙሽራ” “ሙሽሪት”፣ ባል፣ ሚስት የሚል ቃል አላቸው። የዕለቱ መዝሙርም “ትዌድሶ መርዓት” (ሙሽሪቱ ታወድሰዋለች [ሙሽራዋን]) ይባላል። ዮሐንስ መጥምቅ “ሙሽራዪቱ ያለችው እርሱ ሙሽራ ነው” ሲል፣ ዮሐንስ ባለራእዩ “ወደዚኽ ና፣ የበጉን ሚስት ሙሽራዪቱን አሳይኻለኹ” የሚል ድምፅ ከመሪው መልአክ መስማቱን ይነግረናል። ቅዱስ ጳውሎስም “ክርስቶስ ቤተክርስቲያንን እንደወደዳት… ስለእርሷ ራሱን አሳልፎ እንደሰጠ” ሲል ሰምተነዋል። ስለዚኽ ሙሽርነት ለመነጋገር ግን መነሻው ነጥብ ከላይ የጠቀስነው እውነት ነው። “አባት ልጁን ይወዳል፤ ኹሉንም በእጁ ሰጥቶታል።” ሦስት ነጥቦችን እናንሣ፦  

  1. የሙሽርነት መጀመሪያ 

እግዚአብሔር አብ ልጁን በፍጹም ፍቅር፣ በፍጹም ልግስና ይወድዳል። ስለዚኽም እርሱ በአባትነቱ፣ በእግዚአብሔርነቱ ያለውን ኹሉ አምላክነቱን፣ ብርሃንነቱን፣ ሕይወትነቱን ያለ አንዳች ንፍገት፣ በፍጹም ልግስና ሰጠው። አብ ለወልድ ያልሰጠው አንዳችም ነገር የለም፤ እውነተኛ አባት ነውና። ከልግስናው ብዛት የተነሣም በልጁ በኩል የእርሱን ሕይወት የሚወርስ ፍጥረትን መፍጠር ወደደ። ወድዶም በቃሉ ካለመኖር ወደ መኖር አመጣት፤ ከእርሱ ሕያውነት የተነሣ ከዘለዓለም ሕያው በኾነው ልጁ በኩል የእርሱን ሕይወት ወርሳ የምትኖር፣ የሰው ልጅ ራሷ፣ ጉልላቷ የኾነላት ፍጥረትን በአንድ ልጁ አበጀ። በልጁ፣ ለልጁ ስላበጃት፣ የልጁን ሕይወት ወርሳ የምትኖር ስለኾነችም የልጁ ትዳር፣ የልጁ ሙሽራ ተባለች። እግዚአብሔር ለልጁ ሙሽርነትን ሰጠ። ልጁም የፍጥረት ሙሽራ ተባለ። ይኽ እግዚአብሔርና በፍጥረት መካከል እንዲኖር እግዚአብሔር ከዘለዓለም የወሰነው ትዳር የሰው ልጅና እግዚአብሔር በሚኖራቸው ግንኙነት ይገለጣል፤ የሰው ልጅ የፍጥረት ጉልላት፣ የፍጥረት ራስ፣ የፍጥረት ተወካይ ነውና። የዚኽ ትዳር መነሻ ነጥቡ ሙሽሪት አይደለችም፤ የሙሽራው አባት ለልጁ ያለው ፍቅር ነው። የዚኽ ትዳር ጽናቱም ሙሽራው ወልድ አባቱ እርሱን በወደደበት ፍቅር የአባቱ ስጦታ የኾነችው ሙሽራውን መውደዱ ነው። የዚኽ ትዳር ፍጻሜውም ሙሽሪት በተወደደችበት ፍጹም ለጋስ ፍቅር ተመልታ በፍጹም ልግስና መልሳ የወደዳትን ለመውደድ ራሷን ስትሰጥ ነው። የዚኽ ትዳር ዓላማው መረዳዳት፣ ከዝሙት መራቅ፣ ልጅ መውለድ አይደለም። ፍጹም ፍቅር ብቻ ነው።        

  1. ሙሽርነት፣ ጫጉላና መስቀል

መጽሐፍ ቅዱስ ከዘፍጥረት እስከ ራእይ የሚነግረን ይኽንን በሰው ልጅና በእግዚአብሔር መካከል ያለውን ትዳር ነው፤ “የእግዚአብሔርና የሰው ልጅ ፍቅር እስከመቃብር” ልንለው እንችላለን። ግን መቃብር ላይ አያበቃም። እስከ ትንሣኤ፤ እስከ ዕርገት ድረስ ደርሶ የሰው ልጅ በሥላሴ መንበር ተቀምጦ ለዘለዓለም ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ ሲባል እንጂ። ሙሽሪት “መች መጣሽ ሙሽራ መች ቆረጠምሽ ሽምብራ” እንዲሉ የተፈጠረችበትን፣ የተጠራችበትን ዓላማ ትታ ሕይወትን ለፍቅር ሳይኾን ለመኖር ብቻ ፈለገችው። ክፉና ደግን በራሷ ፍላጎት ከእርሷ አንጻር ብቻ ወስና ራሷ የራሷ ብቸኛ አፍቃሪ ኾና መኖር ፈለገች። አፍቃሪዋን ፍቅርን ገፋችው። ከኑሮዋ ጋር አመነዘረች። ፍቅርን ገፍታለችና ኑሮዋ ፍቅር ተለየው። ሕይወቷም የተሰጣት ከፍቅር ነበረና ፍቅርን ስትገፋው ሕይወት ተለያት። ሞተች። እንደሸንኮራ እየመጠመጠችና እያጣጣመች ለብቻዋ እስከመጨረሻው እንጥፍጣፊ ልትልሰው የተመኘችው መኖር የሚባል ነገር እያደሩ መሞት ኾነባት። ክፉና ደግን ከሚያሳውቀው ዛፍ በበላሽ ቀን ትሞቻለሽ ተብላ ነበረ። አልሰማችም፤ ገና በጫጉላዋ አመነዘረች፤ ስለዚኽም ከሙሽርነት ሰገነቷ ወደቀች፤ ጭቃ ነበረችና ወደ ጭቃ ተንከባለለች፤ ሙሽሪቱ ሞተች። ፍቅሩ የተገፋ ሙሽራ ምን ማድረግ ይችላል? “ሙሽራዬ ቀረች፤ ከዳችኝ፤ የሚገባትን አገኘች” እያለ ይቀመጥ ይኾን? ቅዱስ ጳውሎስ እንዲኽ ይለናል፦ “ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያንን እንደወደዳት … በውኃ መታጠብና ከቃሉ ጋር አንጽቶ እንዲቀድሳት ስለእርሷ ራሱን አሳልፎ ሰጠ። እድፈት ወይም የፊት መጨማደድ ወይም እንዲኽ ያለ ነገር ሳይኾንባት ቅድስትና ያለነውር ትኾን ዘንድ ክብርት የኾነች ቤተክርስቲያንን [ሙሽሪትን] ለራሱ ሊያቀርብ ፈለገ።” ኤፌ 5፡ 21

የእርሷ ታማኝነት ማጣት፣ የእርሱን መታመን ሳያስቀር፣ የእርሷ ማፍቀር አለመቻል የእርሱን አፍቃሪነት ሳያስቀረው የአባቱን ዘለዓለማዊ ስጦታ ከተጣለችበት ያነሣት ዘንድ ከወደቀችበት ድረስ ወረደ። ሞት በሚባል በሽታ ተይዛ ቢያገኛት ከእርሷ ከመለየት አብሯት መሞትን መረጠ። በመስቀል ላይ ተቸንክሮ ጫጉላውን ፈጸመ። እነሆ ሙሽራው ሙሽሪትን እንደሚወድድ ማንም ሊጠራጠር አይችልም። እስከሞት ድረስ ጨክኖላታልና። መስቀል የጌታ ኢየሱስ ቤተ ክርስቲያንን ያገባበት የጫጉላ አልጋ ይባላል። (ውዳሴ መስቀልን ተመልከት)። 

ስለዚኽም ዛሬ ቤተክርስቲያን በኼደችበት ኹሉ ከፍ አድርጋ ትይዘዋለች፤ የመወደዷ ምልክት፤ የቃል ኪዳኗ ማኅተም ነውና። እነሆ ሙሽራው ሙሽራዪቱን ከሞተችበት አነሣት፤ አዲሲቱ የእግዚአብሔር ከተማ አደረጋት፤ “የድካምኽን ፍሬ ትበላለኽ” “ፍሬ ፃማከ ተሴሰይ፤ ብፁዕ አንተ ወሠናይ ለከ፤ ብእሲትከ ከመ ወይን ሥሙር ውስተ ጽርሐ ቤትከ” ተብሎ የተነገረለትም ተፈጸመ። እስከ መስቀል ድረስ ደክሞ ሥጋውን አብልቶ፣ ደሙን አጠጥቶ፣ ከስማ የነበረችውን ዛፍ አለመለማት። ሥጋውን ሥጋዋ ደሙንም ደሟ አድርጎላት “ይኽቺ ሥጋ ከሥጋዬ ናት” የሚላትን “ፍሬ” አፈራ። እርሷም ወይን ደሙን ጠጥታ እንደወይን ቆንጅዬ ኾና ለሚቀበሏት ኹሉ በእግዚአብሔር ክብር ተሞልታ ከእግዚአብሔር ዘንድ ትወርድላቸዋለች። እርሷን የሚያገኟት በመካከልዋ የሚኖረውን እግዚአብሔርን ያገኙታል። እግዚአብሔር በአንደበቷ ይናገራል፤ “እግዚአብሔር ይፍታሕ” በሚል ቃሏ እግዚአብሔር ከኃጢኣት እሥራት ይፈታል። እነሆ ዓለሙን ለማዳን ትኖራለች። ጥያቄ፦ በእኔ ኑሮ የሚድን ሰው ይኖር ይኾን?        

  1. የጫጉላ አልጋዋን ተሸክማ የምትዞር ሙሽራ

አኹን እርሷም “በዘለዓለም ፍቅር ወድጄሻለኹ” የተባለችበት ፍቅር ተገልጦላታል። ስለዚኽም፣ ያለፈውን አሮጌውን ለመኖር መኖር የሚባልን ጣዖት አሽቀንጥራ ጥላ ለፍቅር ትኖራለች። በጥምቀት “እክሕደከ ሰይጣን” ብላ አሮጌውን ኑሮ ያስተማራትን የድሮ መምህሯን ትረግማለች። “አአምነከ ክርስቶስ” ብላ በመስቀል ቀለበት ከታሠረላት ሙሽራዋ ኢየሱስ ጋር አንድ ልትኾን መስቀሏን ዕለት ዕለት በፍቅር ትሸከማለች። መከራዋ የፍቅሯ መግለጫ ነውና መከራውን ትታገሠዋለች፤ “እግዚአብሔር በመከራችን ኹሉ የትዕግሥትን ፍጻሜ ይሰጠን ዘንድ ስለነፍሳችን ትዕግሥት እንማልዳለን!” እያለች ጽንዐት አጥታ ከፍቅሯ ሸርተት እንዳትል ስለ ጽንዐት ትማልዳለች። መስቀሏን እንዳትዘነጋ መስቀሉን በፍቅር በስስት ትስማለች። የመስቀል ስጦታዋን ከፍ አድርጋ “አሜን አምናለኹ፤ ይኽ በእውነት ሥጋኽ እንደኾነ አምናለኹ” ብላ ትቀበላለች። መስቀላቸውን የተሸከሙትን ከፍ አድርጋ ሥዕል ሥላ፣ መታሰቢያ ቀን ቆርጣ ታስባቸዋለች። በተለይ በዚኽ ጊዜ በዚኽ የመስቀል ኑሮ እውነተኛ ምሳሌ የኾነችውን ቅድስት ድንግልን የመከራ ኑሮዋን፣ ጨቅላ ልጇን ይዛ ሀገር ለሀገር መንከራተቷን፣ ስደቷን፣ እንግልቷን ታስባለች። እመቤታችን በመከራዋ እንደጸናች እንድትጸናም “እርሱን በማመን ያጸናን ዘንድ” “ድንግል ሆይ! ከሚያስብ ኹሉን ከማይዘነጋ ከልጅሽ ዘንድ አሳስቢ!” “ቅድስት ሆይ! ለምኚልን!” ከሚለው ጸሎቷ እንድንሳተፍ ትጋብዘናለች። 

ለመኖር የሚኖረውን ሟቹን አሮጌውን ሰው አስወግደን በሥጋም በመንፈስም የቤተክርስቲያን አባላት ስንኾንም ሙሽርነቷን እንሳተፋለን፤ ከእርሷ ጋር “ሙሽራዪቱ”፣ “ዐዲሲቱ የእግዚአብሔር ከተማ” እንባላለን። የአንድ ልጁ ወንድሞች በመኾን “የእግዚአብሔር ልጆች” እንደተባልን፤ የአንዲቱ ሙሽሪት አባላት በመኾን ደግሞ እያንዳንዳችንም የቤተ ክርስቲያን የሙሽርነት ሕይወት የሚገለጥብን “ሙሽሮች” እንኾናለን። እግዚአብሔር ፈጣሪያችን እስከመጨረሻዪቱ ሕቅታ ድረስ የምንኖርለት ባላችን ይኾናል፤ “ፈጣሪሽ ባልሽ ነው” ተብሎ ተጽፏልና (ኢሳ 54፡ 5)። 

ሁሉን ለልጁ ለሰጠ ለእግዚአብሔር አብ፣ አባቱ እርሱን በወደደበት ፍቅር በወደደን በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ፣ በመንፈስ ቅዱስ ኃይል ከቤተክርስቲያን ክብር ምሥጋና ይኹንለት። ለዘለዓለም። አሜን።         


Thursday, November 3, 2022

ተስፋ ምንድነው?

የዕለቱ ምንባቦች ፦

፩ ቆሮ፡ ም. ፲፥ ቍ. ፩-፲፬ ራእየ፡ ዮሐ፡ ም. ፲፬፥ ቍ. ፩- ፮ ግብ፡ ሐዋ፡ ም. ፬፥ ቍ. ፲፱-፴፩  ማቴዎስ፡ ም. ፲፪፥ ቍ.፩-፳፪

መዝሙሩ ፦ “ ወመኑ መሓሪ ዘከማከ ፤ ወኵሉ፡ ይሴፎ፡ ኪያከ ” 

የወንጌሉ ንባብ ማሳረፊያው “አሕዛብም በስሙ ተስፋ ያደርጋሉ።” (ይኽ ቃል ከኢሳይያስ 42፡1-6 ድረስ ይገኛል።) 


ተስፋ ምንድነው?

  1. ተስፋ በሚታወቅ ነገር ላይ የሚኖር መተማመን ነው። 

Ἐλπίς (ኤልፒስ) የሚለው የግሪኩ ቃል መተማመን የሚል ፍቺም ይይዛል። በማይታወቅ፣ ባልተቀመሰ፣ ምልክቱ ባልታየ ነገር ላይ ተስፋ አይደረግም። የማያውቀውን፣ ያልቀመሰውን፣ ምልክቱን ያላየውን ነገር ይኾናል ብሎ የሚተማመን ሰው “የቅዠት ባለቤት” እንጂ “የተስፋ ሰው” አይባልም። ቅዠት የካርል ማርክስ Classless Society ኾነ፣ የፕሌቶ Republic፣ ወይም የአክራሪ ካፒታሊስቶች Free Market Economy እውን የማይኾኑት የቢኾን ዓለም ቅዠቶች እንጂ ተስፋ ስላልኾኑ ነው።

በብሉይ ኪዳን የነበረው የእግዚአብሔር ሕዝብ፣ የእግዚአብሔርን ማዳን ከአባቶቹ ሰምቷል፤ የእስራኤል ለቃልኪዳኗ አለመታመን የእርሱን (የእግዚአብሔርን) ታማኝ አፍቃሪነት ሳያስቀረው ምድረ ርስት ከነዓንን አውርሷቸው እንደነበረ ያውቃል፤ ይኽ በጭላንጭል የሚያውቀው የእግዚአብሔር ታማኝነት የተስፋው ምሶሶ ነበረ። ስለዚኽም፣ በነበረበት ውስጣዊ ፖለቲካዊ ምስቅልቅልና የሮማውያን ቅኝ ግዛት ውስጥ ኾኖም ነቢያቱ “የተቀጠቀጠውን ሸምበቆ የማይሰብረው፣ የሚጤስን ጧፍ የማያጠፋው፣ የእግዚአብሔር ምርጥ ብላቴና፣ እግዚአብሔር የቀባው መሢሑ ይመጣል!” እያለ ተስፋ የሚያደርግ፣ የተስፋ ሕዝብ ነበረ። 

  1. ተስፋ ዘላቂ መፍትሔ ላይ ያረፈ ዓይን ነው።

በጥንታዊ ግሪክ ሥነ ጽሑፍ ውስጥ ከማይገኙ ቃላት መካከል አንዱ ተስፋ ነው ይባላል። ምክንያቱም ከአይሁድ እምነት ውጪ የነበረው አሕዛቡ ዓለም ተስፋ የሚባለውን ነገር በፅንሰ ሐሳብ ደረጃ እንኳ ያውቀው ነበረ ብሎ ለመናገር አዳጋች ነው። የዚኽም ምክንያቱ ከሞት የሚሻገር ነገር አለማየታቸው ነው። ንጉሦቻቸውን በወርቅ በተጌጡ መቃብሮች ከብዙ ጌጣጌጥና ንብረት፣ ምግብና መጠጥ ጋር ቢቀብሩም አንዱም ንጉሥ ተነሥቶ የተጣመመ ፍርድ ሲያቃና ወይም ሀገሩን ከጠላት ሲከላከል አላዩም። ስለዚኽም በአብዛኛው ሕዝብ ዘንድ ሞት የመጨረሻው ፍጻሜ፣ የሰው ኑሮ ከንቱነት ማሳያው ነጥብ ነበረ። ከዚኽች ከሚያዩዋትና ከሚያውቋት ውጪ ያለውን ነገር በሥነ ጽሑፎቻቸው እንኳ አያዳንቁትም። ሆሜር በተባለው ባለቅኔ የተደረሰው ኦዲሴ የተሰኘ ሥራ ውስጥ አኪሊስ የሚባል ጀግና ገጸ ባሕርይ “በሞት ሀገር ጌታ ከምኾን በምድር ላይ ባርያ ኾኜ ልኑር” ማለቱ ተጠቃሽ ምሳሌ ነው። አሕዛብ የሚያዩት የሰው ልጅ ኑሮ የመጨረሻ ነጥብ ሞት ብቻ ነበረ። ዓይኖቻቸው የሞትን ጨለማ አልፈው ማየት አልተቻላቸውም። ስለዚኽም ከተቻለ ነገን በልቶ፣ ጠጥቶ፣ ተደስቶ፣ ሕይወትን እንደሸንኮራ ምጥምጥ አድርጎ እስከሞት ድረስ ማጣጣም፣ ወይም እንደፈላስፎች በትሕርምትና በተመስጦ ይኽን ፈራሽና በስባሽ ዓለም ጥሎ መመንጠቅና በሐሳብ ዓለም ከመዋኘት የዘለለ ነገር ሊያስቡ አልቻሉም። ተስፋ የሚለው ፅንሰ ሐሳቡ ራሱ ለሐሳባቸው እጅግ ሩቅ ነበረ። ቅዱስ ጳውሎስ “የሚያየውንማ ማን ተስፋ ያደርገዋል?” እንዳለ (ሮሜ 8፡ 24)።

እንደኢሳይያስ ያሉ ነቢያት የእግዚአብሔር ሕዝብ ወደ እንዲኽ ዓይነቱ የአሕዛብ አስተሳሰብ እንዳይዘቅጥ ታግለዋል። የችግሩ መንሥኤ ኃጢኣት፣ የችግሩ መፍትሔም እግዚአብሔር መኾኑን አሳስበዋል። የእግዚአብሔር ሕዝብ ዓይኑን በሞት ጨለማ ላይ ከማፍዘዝ የእግዚአብሔር ቃል ሰምቶ የተስፋ ብርሃንን እንዲያይ ጮኸዋል። ድምፃቸውም ወድደው ለሚሰሟቸው የተስፋ ብርሃን ነበረ። “ፍርድ ጎደለብን!” ብለው ለሚቆጩት “በእውነት ፍርድን የሚያወጣ” እግዚአብሔር የቀባው ንጉሥ መሢሑ ይመጣል። “የእግዚአብሔርን ቃል የሚያቀብለን ካህን፣ መንገድ የሚያሳየን ነቢይ አጣን” ብለው ለሚቆጩት እግዚአብሔር “ደግፌ የያዝኹት ባርያዬ፣ ነፍሴ ደስ የተሰኘችበት ምርጤ፣ በእርሱ ላይ መንፈሴን አድርጌያለኹ” ብሎ በእውነት የተናገረለት እውነተኛ ነቢይ ይመጣል። ከርኅራኄውም የተነሣ “የተቀጠቀጠ ሸምበቆን አይሰብርም፤ የሚጤስን የጧፍ ክር አያጠፋም”   

የነቢያቱ ጩኸት ምክንያት ሰው ዓይኑን ከእግዚአብሔር ላይ ካነሣ በምድር ላይ መኖር የሚባለው ነገር ሞት በዜሮ የሚያባዛው ትርጉም የለሽ ሩጫ፣ ወይም መልስ የሌለው አስቀያሚ ዕንቆቅልሽ ስለሚኾን ነበረ። 

የእግዚአብሔር ቃል ሥጋ ሲኾን፣ የእግዚአብሔር ልጅ የማርያም ልጅ ሲኾን፣ እግዚአብሔር ሰው፣ ሰውም እግዚአብሔር ሲኾን ይኽ ተስፋ ተፈጸመ። የሰው ልጅ ማኅበረሰባዊ የታሪክ የአዙሪት እሥርቤት ተበጠሰ። የችግራችን ምንጭ የነበረው የእግዚአብሔር መታጣት፣ በእግዚአብሔር ልጅ መገኘት መፍትሔ አገኘ። ዓለም ከመፈጠሩ በፊት እግዚአብሔር ያቀዳት ተዋሕዶ ስትፈጸም፣ ቃል ሥጋ ሲኾን፣ ዘለዓለማዊውን የእግዚአብሔርን ልጅ “ኢየሱስ” ብላ ድንግል እናቱ ስትጠራው  ጥያቄያችን ኹሉ ተመለሰ። ሐዋርያት ይኽን እግዚአብሔር ለሰው ልጅ የሰጠውን መፍትሔ ለሰዎች ለመንገር ስለጓጉ መደብደባቸው አላሳሰባቸውም፤ ይልቁንም “ጌታ ሆይ! ለመፈወስ እጅኽ ሲዘረጋ፣ በቅዱስ ብላቴናህ በኢየሱስ ስም ምልክትና ድንቅ ሲደረግ፣ ባርያዎችኽ በፍጹም ግልጥነት ቃልኽን እንዲናገሩ ስጣቸው!” ብለው ጸለዩ (ሐዋ 4፡29)። ሊነገር የሚያጓጓ ዜና ነዋ! የችግሮቻችን ኹሉ መፍትሔ! ኢየሱስ ክርስቶስ “ለበሓማን ኮኖሙ ቃለ፤ ለዕውራን ብርሃነ፣ ወለሓንካሳን ፍኖተ፣ ወለዘለምፅ መንጽሒ” እንዲል የኪዳን ጸሎት።      

  1. ተስፋ በጽናት ይገለጻል። 

 ተስፋ አስተማማኙን ዘላቂ መፍትሔ መተማመን ነው። በዚኽ መተማመን ውስጥ የሚኖር ሰው በፍርኃት፣ በተስፋ መቁረጥ፣ በሐዘን፣ በጥላቻ ሊኖር አይችልም። ቅዱስ ጳውሎስ የቆሮንቶስ ምእመናንን የሚያሳስባቸው ይኽንን ነው። ክርስቲያኖች ወደ ኃጢኣት ሸለቆ ወርደን ስንርመጠመጥ የምንገኘው በምሥጢራተ ቤተክርስቲያን፣ በተለይም በቅዱስ ቁርባን፣ ተዋሕዶን ከሚኖረው ጌታ ኢየሱስ ላይ ዓይኖቻችንን ስናነሣና ዙሪያችንን ማማተር ስንጀምር ነው። የልባችን ዓይኖች ጌታ ኢየሱስ ላይ ከተተከሉ ጨለማ ዙሪያችንን ቢከብበንም እንኳ ከጨለማው ሥራ ጋር አንተባበርም፤ ብርሃን ኢየሱስ ክርስቶስ በልባችን አለና። በጥምቀት የለበስነው ጸጋው፣ በቅዱስ ቁርባን የምንቀበለው እርሱነቱ ሞት ቢከብበን እንኳ ከሙት ሥራ ከመተባበር ያድነናል። ከራሳችን ተርፎም ለሌሎች የተስፋ ብርሃናችን ያበራል። ብርሃናችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእኛ ጋር ነውና። 

ስለዚኽም፣ ቤተ ክርስቲያን የጌታ ኢየሱስን ቅዱስ ስሙን ሙጥኝ ትላለች። ለአፍታ ከአንደበታችን ደጃፍ፣ ከልባችን ጓዳ እንዳንለየው ታሳስባለች። ቅዱስ ስሙ የደስታችን ምክንያት፣ የመከራችንም ትርጉም ነው። ጣፋጭ ስሙን ትጠራለች፤ ጽኑ ስሙን ትታመናለች፤ ታማኝ ስሙን ተስፋ ታደርጋለች። ድንግሊቱ ቤተ ክርስቲያን የበጉ ስምና የአባቱ ስም በመንፈስ ቅዱስ ግንባሯ ላይ ተጽፎ ሙሽራዋን በጉን በሄደበት እየተከለች ቅዱስ ስሙን ትዘምርለታለች (ራእ. 14፡1-5)። ክርስቲያን መኾን የጌታ ኢየሱስ ቅዱስ ስሙን ተስፋ ማድረግ ነው።

 

 

ስሙ ሕይወት ለኾነው ለእግዚአብሔር አብ፣ 

ጣፋጭ ስሙ ተስፋ ለኾነን ለአንድ ልጁ ለኢየሱስ ክርስቶስ፣ 

ቤተ ክርስቲያንን በአብና በወልድ ስም ላተማት ለመንፈስ ቅዱስ 

ክብርና ምሥጋና ይኹን። አሜን።   


Tuesday, December 25, 2018

ቃል ለምን ሥጋ ኾነ?


“አምላክ ለምን ሰው ኾነ” ለሚለው ጥያቄ አብዛኛው ሰው የሚሰጠው መልስ “ከኃጢኣታችን ሊያድነን” የሚል ኾኖ ይታያል፡፡ ይኽ መልስ ግን በአምላክ ሰው መኾን የተገኘውን ውጤትና አምላክ ሰው የኾነበትን ምክንያት የሚያደበላልቅ ደካማ መልስ ነው፡፡ አምላክ ሰው የኾነው በሰው ልጅ ኃጢኣት ምክንያት አይደለም፡፡ ከመጽሐፍ ቅዱስም፣ ከሐዋርያትም፣ ከቀደሙት አበውም “አምላክ ሰው የኾነበት ምክንያት የሰው ልጅ ኃጢኣት ስለሠራ ነው” የሚል ትምህርት አላስተማሩም፡፡ የክርስትና አስተምህሮ ፍጥረትን ካለመኖር ወደ መኖር ካመጣው ከእግዚአብሔር ሞልቶ ከሚፈስሰው የማይለወጥ የእግዚአብሔር ፍቅር እንጂ ከኃጢኣት አይጀምርም፡፡   
  
አምላክ ሰው የኾነው ዓለም ሳይፈጠር ጀምሮ የሰውን ልጅ የመለኮቱ ባሕርይ ተካፋይ ለማድረግ የነበረውን ዕቅድ ሊፈጽም ነው፡፡ ቅዱስ ሄሬኔዎስና ቅዱስ አትናቴዎስ በመጽሐፎቻቸው እንዳሰፈሩት የሰው ልጅ የእግዚአብሔር ልጅ ይኾን ዘንድ የእግዚአብሔር ልጅ የሰው ልጅ ኾነ። እርሱ በባሕርዩ የኾነውን ኹሉ እኛ በጸጋ እንኾን ዘንድ እኛን ኾነ። የአብ ብቸኛ ልጁ ከእመቤታችን ተወልዶ ወንድማችን ስለኾነልን ወንድሞቹም ስለተባልን በእርሱ የእግዚአብሔር ልጆች ተባልን። "አብ እንዴት ያለውን ፍቅር እንደሰጠን እዩ!" (1ኛ ዮሐ 3፣ 1)። በወልድ ውሉድ፣ በቅዱስነቱ ቅዱሳን፣ በክርስቶስነቱ ቤተ ክርስቲያን ተሰኘን። ይኽ ለእኛ የተሰጠው ሕያውነትም በእኛ ብቻ ወስነን እንድናስቀረው አይደለም የተሰጠን፣ በእኛ በኩል ፍጥረት ኹሉ የእግዚአብሔርን ጸጋ እንዲለብስ የጸጋ መስኮቶች እንድንኾን ነው እንጂ።  
 
ፍጥረት ኹሉ የተፈጠረው በእርሱና ለእርሱ ነውና እርሱ የፍጥረት ራስ በመኾን ፍጥረትን የመለኮቱ ባሕርይ ተካፋይ ለማድረግ ዓለም ሳይፈጠር፣ ዘመን ሳይቆጠር በፊት ወስኖልናል፡፡ የሰው ልጅ በኃጢኣት መውደቅ እግዚአብሔር ለሰው ልጅ ያቀደውን ከአእምሮ በላይ የኾነ ስጦታ እንዳይሰጥ አልከለከለውም፡፡ ከእግዚአብሔር ተለይተን እርስ በርሳችንም ተለያይተን የኖርንበት የኃጢኣታችንን ግንብ መናዱ የቃል ሥጋ መኾን ካስገኘልን ውጤቶች አንዱ ነው እንጂ አምላክ ሰው የኾነበት ምክንያት አይደለም፡፡ ከዛሬ አንድ ሺሕ ስድስት መቶ ዓመት በፊት የቁስጥንጥንያ ሊቀ ጳጳሳት የነበረው ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ የቲቶን መልእክት ባብራራበት ድርሳኑ ላይ ይኽን አስመልክቶ እንዲኽ ብሏል፡- 

መዳናችን ሐሳብን በመቀየር አኹን የተደረገ  አይደለም፤ ከመጀመሪያው የታቀደ ነበር እንጂ፡፡ ጳውሎስ ይኽንን በተደጋጋሚ ያረጋግጣል፤ ልክ በሮሜ 1፣1 ላይ “ለእግዚአብሔር ወንጌል ተለየ” ሲል እንደሚያደርገው፡፡[1] ደግሞም “አስቀድሞ ያወቃቸው የልጁን መልክ ይመስሉ ዘንድ ወስኗልና” እንዲል (ሮሜ 8፣ 29)፡፡ በዚኽም ጥንተ ታሪካችንን ያሳየናል፡፡ የወደደን አኹን አይደለም ገና ከመጀመሪያው አፈቀረን እንጂ፡፡
 
ቅዳሴ ማርያምም “ፍቅር ሰሐቦ ለወልድ ኃያል እመንበሩ ወአብጽሖ እስከለሞት” (ፍቅር ኃያል ወልድን ከዙፋኑ ሳበው እስከሞትም አደረሰው) እንዲል፡፡ 


[1] ይኽ ሐረግ የሚገኝበት ዐረፍተ ነገር “አስቀድሞ ተስፋ ለሰጠው” የሚል ሐረግ አለው፡፡ ዮሐንስ አፈወርቅም በዚኽ አባባሉ እርሱን እየጠቆመ ነው፡፡

ልበስዎ ለሐዲስ ብእሲ (“ዐዲሱን ሰው ልበሱ”)(ኤፌ. 4፣ 24)


ይኽ ቃል የሚገኘው ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በእሥር ቤት ኾኖ ለኤፌሶን ምእመናን በጻፈው መልእክት ውስጥ ነው፡፡ መልእክቱ በዋናነት የኤፌሶን ቤተ ክርስቲያን ምእመናን እግዚአብሔር በልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል የገለጠውንና ያለ ዋጋ እንካችኹ ያለውን ፍጹም ፍቅር በማስተዋል፣ ይኽን ፍቅሩ አስተማማኝ የኾነ እግዚአብሔርን በማመን ጸንተው እንዲቆዩ ለማድረግ የተጻፈ ነው፡፡ በሌላ አባባል ክርስቲያን መኾን ማለት ምን ማለት እንደኾነ እንዲያስተውሉ፣ አስተውለውም ክርስትናቸውን አጽንተው እንዲኖሩ የሚያደርግ ትምህርት ያስተላለፈበት ደብዳቤ ነው፡፡ ትምህርቱ ለኤፌሶን ምእመናን ብቻ ሳይኾን በየዘመኑ ለሚነሡ ክርስቲያኖች ኹሉ እጅግ ጠቃሚ መኾኑን አምነውበትም አበው ከቅዱሳት መጻሕፍት ውስጥ እንዲካተት አድርገዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያንም ክርስቲያን የመኾናቸውን ትርጉም የሚዘነጉ ምእመናን ልባቸውን እንዲያነቁበት ላለፉት ኹለት ሺሕ ዓመታት ስትጠቀምበት ቆይታለች፡፡ ዛሬም ትጠቀምበታለች፡፡  

በዚኽም መሠረት፣ ቅዱስ ጳውሎስ ዛሬ እኛን “ዐዲሱን ሰው ልበሱ” ይለናል፡፡ እሺ ብለን ዐዲሱን ልብስ እንልበስ ስንል ግን ዐዲሱን ልብስ ለመልበስ አንድ መስፈርት እንዳለ ይናገራል፡፡ ጥቅሱን ከፍ ብለን ስናነብበው ቁጥር 22 ላይ የሚከተለውን ቃል እናገኛለን፡- “በሚያታልል ምኞት የሚጠፋውን አሮጌውን ሰው አስወግዱ”፡፡ ዐዲሱን ሰው ከመልበስ በፊት አሮጌውን ሰው ማስወገድ ግድ ይላል፡፡

አሮጌው ሰው ማን ነው?

አንደኛ፣ አሮጌ ነው፡፡ አርጅቷል፡፡ ከፊቱ ሞትና መፍረስ እንጂ ሕይወትና ደስታ አይጠብቁትም፡፡ 

ኹለተኛ፣ የምኞትና የመጎምዠት እሥረኛ ነው፡፡ ልቡ ዕረፍት የለውም፡፡ ከሰዎች ክብርን የመቀበል ሱስ ስለተጠናወተው በሰዎች ዘንድ ያስከብረኛል የሚለውን ነገር ለመያዝና የዚያ ነገር “ጌታ” ኾኖ ለመታየት የማይፈነቅለው ደንጊያ የለም፡፡ በቃኝ አያውቅም፡፡ ኹሌ እንደሮጠ፣ ኹሌ አንዳች ነገር ተከትሎ እንደበረረ ይኖራል፡፡ እርካታ የለውም፡፡ እንዲኽ ዓይነቱ ሰው በሰዎች ዘንድ የሚያስከብረው እስከኾነ ድረስ ክፉ ነገር ብቻ ሳይኾን ደግ ነገርንም ሊያደርግ ይችላል፡፡ ለእርሱ ዋናው ነገር በሰዎች ዓይን ከፍ ብሎ መታየቱ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ሲያሠራ፣ ገዳማት ሲዞር፣ ሲጾም፣ ሲጸልይ፣ ባስ ሲልም ደግሞ ዐውደ ምሕረት ላይ ወጥቶ ሲሰብክ፣ ቤተ መቅደስ ገብቶ ሲቀድስ ሊታይ ይችላል፡፡ አንዱንም ነገር ግን ለእግዚአብሔር ክብር አያደርገውም፡፡ በእግዚአብሔር ፈንታ በራሱ ልብ ውስጥ ራሱን አንግሦ፣ ራሱን እያመለከ፣ ራሱን “ቅዱስ፣ ቅዱስ፣ ቅዱስ” እያለ የሚኖር፣ ዓለም በዙሪያው የምትሽከረከርለት የሚመስለው ዕብሪተኛ ሰው ነው፡፡ የሚያደርገው ክፉም ኾነ “በጎ” የሚመስል ድርጊት ኹሉ ከዚኽ የመመለክ፣ የመከበር፣ በሌሎች ላይ ጌታ የመኾን ጥማቱ ይመነጫል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ይኽንን እግዚአብሔርን ያለማመንና በልብ ላይ ያለማንገሥ በሽታ “ኃጢኣት” ሲል ይጠራዋል፡፡ የዚኽ በሽታ ታማሚዎች (ነጻ ፈቃዳቸውን ኃጢኣት የተቆጣጠረባቸው ሰዎች) ኃጢኣተኞች ሲል ይጠራሉ፡፡ ከእነዚኽ አንዱ “ቃየን” ይባላል፡፡ 

ቃየን በእግዚአብሔር ፊት መሥዋዕት አቅርቦ ነበር፤ መሥዋዕቱ ግን ተቀባይነት አላገኘም፡፡ መሥዋዕት ማቅረብ በጎ ሥራ ነበር፡፡ ነገር ግን ቃየን ልቡ እግዚአብሔርን ያነገሠ አልነበረምና እግዚአብሔር መሥዋዕቱን አልተቀበለውም፡፡ መሥዋዕቱን ሳይቀበለው ሲቀር ደግሞ ለምን መሥዋዕቴን ሳይቀበልልኝ ቀረ ብሎ ራሱን ከመመርመር ይልቅ፣ የወንድሙ መሥዋዕት ተቀባይነት በማግኘቱ ተናደደ፡፡ ምክንያቱም መሥዋዕት ያቀረበው እግዚአብሔርን “እንዲኽ ስላደረግኹልኽ በል አንተ ደግሞ እንዲኽ አድርግልኝ” ብሎ እግዚአብሔርን እንደባርያ ለማዘዝ እንጂ እግዚአብሔርን ለማምለክ አልነበረምና፡፡ በእግዚአብሔር ላይ የነበረውን ቁጭት ነው ወንድሙን አቤልን በመግደል የተወጣው፡፡  

እንግዲኽ ቅዱስ ጳውሎስ ይኽን በእግዚአብሔር ጌትነት የማያምነውን፣ ሰብአዊ ፈቃዱን ለእግዚአብሔር ፈቃድ ያላስገዛውን እከብር ባይ፣ ዕብሪተኛ ልቡና ነው “አስወግዱት” የሚለን፡፡ በእውነትም ይኽ የሰውን ልጅ ግላዊም ኾነ ማኅበራዊ ሰላም እንዳይኖረው ያደረገው፣ አምላክ ሳይኾን አምላክ ነኝ ብሎ “ፈቃዴን ፈጽሙልኝ፤ ለግዛቴ ተጋደሉልኝ፡፡ ለክብሬ ሙቱልኝ፡፡” እያለ መከራችንን የሚያሳየን ሐሰተኛ፣ ራስ ወዳድ፣ አሮጌ ሰውነታችን መወገድ አለበት፡፡ ለምን ምክንያቱም አለበለዚያ ዕረፍት፣ ሰላም፣ እርካታ፣ ደስታ የሉምና፡፡ የቤተ ክርስቲያን ሊቅ ቅዱስ አጎስጢኖስ “ጌታ ሆይ አንተ ለአንተነትኽ ፈጥረኸናልና ልባችን በአንተ እስኪያርፍ ድረስ ዕረፍተ ቢስ ኾኖ ይኖራል፡፡” እንዳለው፡፡