Monday, December 12, 2011

St. Francis de Sales



ሰሞኑን አንድ በአስራ ሰባተኛው  ክፍለ ዘመን የተጻፈ መጽሐፍ እያነበብሁ ነበር፡፡ ጸሐፊው ቅዱስ ፍራንሷ ደ ሳል[i] ይባላል፡፡ የጄኔቫ ጳጳስ እንደነበረ የሕይወት ታሪኩ ያስረዳል፡፡ የመጽሐፉ ርእስ “Introduction to the Devout Life”[ii] ነው፡፡ ክርስቲያን የሆነ ሰው ሁሉ ሊያነበው እንደሚገባም አምናለሁ፡፡ ምንም እንኳ ራሱ ቅዱስ ፍራንሷ በትሕትና መጽሐፉን የጻፍሁት በዓለም ላሉ ሰዎች ነው[iii] ቢልም መጽሐፉ የያዘው በመንፈሳዊነት፣ በንባብና በልምድ ከታሸ ዕውቀት የሚፈልቅ ምክር ስለሆነ በእግዚአብሔር ምሕረት ያገኘውን የክርስቲያንነት ጸጋ ለሚያከብር ሰው ሁሉ እጅግ ጠቃሚ እንደሆነ አምናለሁ፡፡[iv]

መጽሐፉ ከኃጢአት እስከ ንስሐ፣ ከንስሐም እስከ ቅድስናን ጠብቆ መኖር ያለውን የክርስትና ጉዞ ያስተዋውቃል፡፡ ፈተናዎቹን በዝርዝር ያሳያል፡፡ ለምሳሌ አንዳንዶቻችን ከእግዚአብሔር ጋር ለመኖርና ኃጢአትን እርግፍ አድርገን ለመተው መቁረጥ ብዙም አያስቸግረንም፡፡ እንዲያውም ውሳኔያችን እንደሚያመጣልን የምናስበውን ቅድስና ለማግኘት እጅግ እንጣደፋለን፡፡ ልባችን ስቅል ይላል፡፡ እንጓጓለን፡፡

ነገር ግን እንደምታውቁት የቅድስናን ጉዞ አልጋ በአልጋ ሆኖ አያውቅምና ጥቂት ስንቆይ የኃጢአቶቻችን አጥፊ ጣዕም ይናፍቀን ይጀምራል፡፡ ጉዟችንን ስንጀምረው የነበረን መንፈሳዊነት ግለትም ይቀዘቅዝብናል፡፡ ይሄኔ የተውናት ዓለም በዓይነ ኅሊናችን ፊት ውል ማለት ትጀምራለች፤ ጠረኗ ይሸተን ይጀምራል፡፡ የጠላነው ሥጋዊ ምኞት ሊያባብለን ይሞክራል፡፡ ለመራቅ እንሞክራለን ግን የትናንቱ ዓለማችን ትዝታ በጆሯችን፣ በዓይናችን በትዝታችን ውስጥ እያደባ እንደጥላ ይከተለናል፡፡ ጸሎታችን ሰሚ ያለው አልመስል ይለናል፡፡ የጓጓንለት ቅድስና እንደሰማይ የራቀ ሆኖ ይሰማናል፡፡ መድረስ የሚቻልም አይመስለንም፡፡ ራሳችንን መጠየፍ እንጀምራለን፡፡ እንበሳጫለን[v]፡፡ ከፈተናዎቹ ጥንካሬ የተነሣም ይሁን በደካማነታችን ምክንያት አንዳንዶቻችን ከእግዚአብሔር ጋር ለመኖር የወሰንነውን ውሳኔ ትክክለኝነትም እንጠራጠራለን፡፡ ሲብስም “በቃ! ለእኔ አልተሰጠኝም ማለት ነው፡፡” ብለን በቶሎ ከጀመርነው የቅድስና ጉዞ እናፈገፍጋለን፡፡ መፍትሔው ምን ይሆን?

ቅዱስ ፍራንሷ “የችግሩን ምንጭ ማግኘት የመፍትሔውን ግማሽ ማወቅ ነው፡፡” በማለት በቅድሚያ የችግሩን ምንጭ ያሳየናል፡፡ እንደርሱ አባባል የችግሩ መነሻ ያለው አነሣሣችን ላይ ነው፡፡ “እንዴ! ደግሞ በቅድስና ለመኖር በጉጉት መነሣት ምን ችግር አለው?” ብለን ልንጠይቅ እንችላለን፡፡ ነገር ግን መነሣቱ አይደለም ችግሩ ይልቁንም መጓጓታችን ነው፡፡ በጉዟችን መጀመሪያ ላይ ለመጓዝ መነሣት እንጂ ለፍጻሜው መጓጓት አልነበረብንም፡፡ ሁሉም በጊዜው ይደርሳልና እግዚአብሔር ያልሰጣችሁን ጸጋ ከመመኘት ራቁ ይላል፡፡ ይልቁንም በተሰጠን ጸጋ እንደአቅማችን በልክ ለመኖር እንድንጥር ይነግረናል፡፡

ጸሎት ሰልችቷችሁ ያውቃል? ያን ጊዜ ምን ታደርጋላችሁ?
አንዳንዶቻችን “ልቤ የማይነካበትና ከልቤ የሚፈልቅ የማይመስለኝን ጸሎት ለአምላኬ እንዴት ብዬ አቀርባለሁ?” ብለን መጸለዩን እርግፍ አድርገን እንተወዋለን፡፡ ሌሎቻችንም ሙሉ በሙሉ ባንተወውም እንኳ ልባችን ይሰንፍብናል፡፡ ምን ይሻላል? ቅዱስ ፍራንሷ መልስ አለው፡፡

ጸሎታችን ለእኛ ደረቅ ቢሆንብንም ሰው እውነተኛ ወዳጁ ቤቱ ሲመጣበት ያለውን እንደሚያቀርብ፣ እንግዳውም የቀረበውን ነገር ትንሽነት ሳይሆን ያቀረበውን ታዛዥና አፍቃሪ ልብ እንደሚመለከት፣ ስለፍቅርም ብሎ የቀረበለትን በደስታ እንደሚቀበል ሁሉ ደካማነታችንን የሚያውቅ እግዚአብሔርም ጸሎታችንን እንደማይተውብን ያሳስበናል፡፡ በትዕግስት ከጠበቅንም የመንፈሳዊነት ድርቅ ያጠቃውን እኛነታችንን በጸጋው ዝናብ ዳግም ያረሰርሰዋል ይለናል፡፡[vi]
በትዕግስት ጠብቀው በዝምታ
ዘንበል ይላል ጌታ፡፡” (አንድ ኢትዮጵያዊ ዘማሪ)


በሌላም በኩል ይህ የመንፈሳዊነት በረኃ እግዚአብሔር ለእኛ ለልጆቹ ዕድገት የሚያዘጋጀው የጉዞው አካል ነው- እንደ ቅዱስ ፍራንሷ አባባል፡፡ እናት ለሕጻን ልጇ ጣፋጭ ነገር ስትሰጠው ያቅፋታል ይስማታል፡፡ ነገር ግን መሳሙ በጣፋጩ የተነሣ የመጣ ይሁን በእናትነቷ እዚህ ላይ ማወቅ አንችልም፡፡ ነገ መራራ ነገር ብትሰጠው እንደሚስማት እርግጠኛ መሆንም ከባድ ነው፡፡ ይህንን ለማረጋገጥም ሆነ ልጁን በእናትነት ፍቅሯ ለማበልጸግ ልጁ ያለ ጣፋጭ እናቱን እንዲያገኝ ማድረግ ይገባል፡፡ በዚህም እናቱን ለእናትነቷ ሲል ማፍቀርንም ይማራል[vii]፡፡ እግዚአብሔርም ጸጋው በእኛ ላይ እንዳለች እንድናውቅና ተጠንቅቀንም እንድንይዛት አንዳንዴ ጸጋውን ከእኛ ይሰውራል፡፡ ቅዱስ ዳዊት “ደለወኒ ዘአሕመምከኒ” (ያስጨነቅኸኝ ለመልካም ሆነልኝ፡፡) (መዝ 118፡ 71) እንዳለው፡፡ 

ስለ ፈተና ዓይነቶች፣ ስለ ፈተናና ኃጢአት ተዛምዶ፣ ፈተናን እንዴት ማራቅ እንደሚገባ፣ በዕለት ተዕለት ሕይወት ውስጥ ፈተናን እንዴት ማለፍ እንደሚቻል ይተነትናል፡፡ ለምሳሌ ቀጥሎ ያለውን የሲየናዋን ቅድስት ካተሪን ተጋድሎ እንዲህ አቅርቦታል (አራተኛ ክፍል ምዕራፍ አራት)፡-

ሰይጣን የዚህችን ድንግል ንጽሕና ይፈታተን ዘንድ እግዚአብሔር ፈቀደለት፤ ነገር ግን አካሏን በምንም ዓይነት መልኩ እንዳይነካት ከለከለው፡፡ በዚህም የተነሣ ዲያብሎስ ርኩሳን የሆኑ ምክሮችን ለልቧ ያቀርብ ጀመር፡፡ ከአጋሮቹ ጋር በመሆንም በወንድና በሴት አምሳል እየቀረበ እጅግ አጸያፊ የሆኑ ድርጊቶችን አሳያት፡፡ እጅግ የረከሱ ንግግሮችንም አሰማት፡፡ እነዚህ ሁሉ ነገሮችም ምንም እንኳ የሚከናወኑት ከእርሷ ውጪ ቢሆንም በስሜት ሕዋሳቶቿ በኩል ወደ ልቧ ጠልቀው ገቡ፡፡ ራሷ በኑዛዜዋ እንደ ገለጠችውም ልቧ በእነርሱ ተመላ፡፡ ነገር ግን የነፍሷን ፈቃድ ለዚህ ርኵሰትና ሥጋዊ እርካታ አሳልፋ አልሰጠችም፡፡ ይህ ፈተና ጌታችን ወደ እርሷ እስከመጣበት ቀን ድረስ ለረጅም ጊዜ አብሯት ቆየ፡፡ ጌታችን በታያት ጊዜም
“ውዱ ጌታዬ ሆይ! ልቤ በጨለማና በርኵሰት ሲሞላ የት ነበርህ?” በማለት ጠየቀችው፡፡
እርሱም “ልብሽ ውስጥ ነበርሁ ልጄ፡፡” ሲል መለሰላት፡፡
እርሷም መልሳ “በርኵሰት በተመላው ልቤ ውስጥ እንዴት ልታድር ቻልህ? እንደዚህ ንጹሕ ባልሆኑ ስፍራዎች ውስጥ ትገኛለህ ማለት ነውን?” አለች፡፡
ጌታም “እስኪ ንገሪኝ፤ የልብሽ ክፉ ሐሳቦች እርካታን ሰጡሽ ወይስ ሐዘንን አመጡብሽ? መራርነትን አፈለቁብሽ ወይስ ደስታን አቀበሉሽ?” ሲል ጠየቃት፡፡
“እጅግ ከባድ መራርነትና ሐዘን” ብላ መለሰች፡፡      
እርሱም፡- “ይህንን ሐዘንና መራርነት ማን የፈጠረው ይመስልሻል? በመንፈስሽ ጥልቅ ውስጥ ተሰውሬ የነበርሁት እኔ ነኝ፡፡ እመኚኝ ልጄ፤ እኔ ባልኖር ኖሮ እነዚህ ፈቃድሽን የከበቡ ነገር ግን ሊረቱት ያልቻሉ ሐሳቦች ባሸነፉሽና ወደ ውስጥ በዘለቁ፣ ፈቃድሽም በተቀበላቸውና ለነፍስሽም ሞትን ባስከተሉባት ነበር፡፡ ነገር ግን እኔ ውስጥ ስለነበርሁ ጥላቻውንና መቋቋሙን ፈጠርሁልሽ፡፡ በዚህም ልብሽ ፈተናውን በሙሉ ዐቅሙ እንዲከላከል አስቻልሁት፡፡ ነገር ግን መከላከል የሚፈልገውን ያህል አልተከላከለምና አሁንም ፈተናውንና ራሱን በእጅጉ ይጠላል፡፡ ስለሆነም ትግሎችሽ መልካምነትሽንና ጥንካሬሽን ይጨምሩልሻልና የታላቅ በጎነትና የጥልቅ ጥቅምሽ ምንጮች ናቸው፡፡” ብሎ መለሰላት፡፡

መጽሐፉ ክርስቲያኖችን ከሚገጥሙ ፈተናዎች መካከል ያላነሣው ዐቢይ ነጥብ ያለ አይመስለኝም፡፡ ነጥቦቹን የሚያነሣበት መንገድና መፍትሔዎቻቸውን የሚያመጣበት አቀራረብ ቀላልነትና ቀጥተኛነት መጽሐፉ ከዐራት መቶ ዓመታት በፊት የተጻፈ መጽሐፍ መሆኑን እንድትረሱ ያደርጋል፡፡ ስለ ሐሜት ያነሣውን ጥቂት ላቃምሳችሁ፡-

የሰው ልጅ ሦስት ሕይወት አለው፡-
ሀ. በእግዚአብሔር ጸጋ የሆነው መንፈሳዊ ሕይወት
ለ. ከነፍስ የተነሣ የሆነው ሥጋዊ ሕይወት
ሐ. በመልካም ስም ላይ የሚመሠረተው ማኅበራዊ ሕይወት
የመጀመሪያውን (በእግዚአብሔር ጸጋ የምናገኘውን መንፈሳዊ ሕይወት) ኃጢአት ከእኛ ትወስድብናለች፤ ሁለተኛውን (ነፍሳችንን) ሞት ይነጥቀናል፤ ሦስተኛውን (በመልካም ስም ላይ የሚመሠረተውን ማኅበራዊ ሕይወት) ሐሜት ይገፍፈናል፡፡ ሐሜት ግድያ የሚሆነውም በዚህም የተነሣ ነው፡፡
ሐሜተኛ በአንዲት የምላስ ስንዘራ ሦስት ግድያዎችን ይፈጽማል፡፡ በቅድሚያ የራሱንና የሰሚውን ነፍሶች በመንፈሳዊ ግድያ ከጸጋ እግዚአብሔር ያርቃል፡፡ ቀጥሎም የሚታማውን ሰው ማኅበራዊ ሕይወት ይገድላል፡፡ ቅዱስ በርናርዶስ “ሐሜተኛ በምላሱ ላይ፣ ሐሜት አድማጩ ደግሞ ጆሮው ውስጥ ሰይጣን አለባቸው፡፡” ይላል፡፡ ዳዊትም ሐሜተኛን አስመልክቶ “ምላሳቸውን እንደ እባብ አሰሉ፡፡” (መዝ 141፡ 3) ይላል፡፡ አሪስጣጣሊስ ደግሞ “የሐሜተኛ ምላስ እንደእባብ ምላስ ጫፉ መንታ ነው በአንዱ የሰሚውን ጆሮዎች በሌላኛውም ጫፍ የሚታማውን ሰው ስም ይመርዛልና፡፡” ማለቱ ይጠቀስለታል፡፡
ስለሆነም የእግዚአብሔር ወዳጅ ሆይ አንቺ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ስለሰዎች ክፉ እንዳትናገሪ፡፡ ጎረቤትሽ ያላደረገውን ኃጢኣትም እንዳትጭኚበት፣ ምሥጢር የሆኑትን ስሕተቶቹንም የግድና አስፈላጊ ካልሆነ በስተቀር እንዳታወጪበት፣ የሚታወቁትንም እንዳታጋንኚበት ተጠንቀቂ፡፡ መልካም ሥራውን በክፉ እንዳትተረጉሚ፤ የምታውቂውን በጎ ጎኑንም እንዳትክጂ፡፡ በክፋት ወይም በቃላት እንዳታንኳስሺው፡፡ ምክንያቱም በእነዚህ ሁሉ መንገዶች በተለይም ደግሞ በሐሰት በመክሰስና እውነትን ሸፍጠሽ ጎረቤትሽን በማንኳሰስ እግዚአብሔርን በእጅጉ ታስቀይሚዋለሽና፡፡    

አንዳንድ ከሁሉም የባሱ ረቂቅና መርዘኛ ተቺዎች ደግሞ ሐሜታቸውን በአክብሮት ወይም በሙገሳ ይጀምራሉ፤ ወይም ቀልዶችን ጣል ጣል ያደርጉበታል፡፡ “እርግጥ ነው  እወደዋለሁ” ወይም “እርግጥ ነው ጎበዝ ሰው ነው፡፡ ነገር ግን እውነቱ መነገር አለበት፡፡ እንዲህ ዓይነት ስሕተት ተሳስቷል፡፡” “በጣም መልካም ሴት ነበረች፤ እንደው በትንሽ ነገር ተሳሳተች፡፡” ይላሉ፡፡ ዘዴያቸውን ትመለከታለህ? ቀስትን አርቆ ለመወርወር የሚሻ ሰው ፍላጻውን በተቻለው መጠን ወደራሱ ይስበዋል፡፡ ዓላማው ግን ቀስቱን ላቅ ባለ ኃይል ርቆ እንዲጓዝ ማስቻል ነው፡፡ እነኚህ ተቺዎችም ሐሜታቸውን ወደራሳቸው የሚያቀርቡት ይመስላሉ ዓላማቸው ግን የአድማጮቻቸውን ልብ በኃይል በስቶ እንዲገባ ማድረግ ነው፡፡     

በቀልዶች መልክ የሚነገሩ ማንኳሰሶች ደግሞ ከሁሉም የበለጠ ጭካኔን የተመሉ ናቸው፡፡ ሄምሎክ ብቻውን ከባድ መርዝ አይደለም፤ በቀላሉ ሊረክስም ይችላል፡፡ ከወይን ጠጅ ጋር በመቀላቀል የተወሰደ እንደሆነ ግን ፈጽሞ ለማዳን አይቻልም፡፡ ልክ እንደዚሁ ሐሜት በአድማጩ በአንዱ ጆሮ ገብቶ በሌላኛው ሊፈስ የሚችል ቢሆንም ቅሉ በቀልድ ተዋዝቶ በሚመጣበት ጊዜ በአድማጮች አእምሮ ለረጅም ጊዜ ይቀመጣል፡፡[viii] ቅዱስ ዳዊት “የእባብ መርዝ በምላሳቸው ሥር አለ፡፡” ይላል፡፡ (መዝ 12፡3 እና መዝ 140፡ 3)፡፡

ይህ መጽሐፍ የማይዳስሰው የሕይወት ጥጋጥግ ብዙ አይመስለኝም፡፡ ከምግብ ጠረጴዛ እስከ አልጋ፣ ከሥራ ቦታ እስከ መዝናኛ ያሉት መገኛዎቻችን ተዳስሰዋል፡፡ ለወጣቶችም ሆነ ለአረጋውያን፣ ላገቡትም ሆነ ለማያገቡት፣ ለደናግልም ሆነ ለመዓስባን፣ ለወጣንያንም ሆነ ለፍጹማን፣ ለመካሪዎችም ሆነ ለተመካሪዎች የሚለው ነገር አለው፡፡ ምናልባት ዐቅሙና ጊዜው ያላቸው ሰዎች በግል ወይም በቡድን ይህን መጽሐፍ ወደ ኢትዮጵያውያን ቋንቋዎች ቢተረጉሙት እጅግ መልካም ፍሬ የሚሆን ይመስለኛል፡፡


[i] St. Francis de Sales
[ii] ምናልባት በአማርኛ “የመሰጠት ሕይወት መግቢያ” ልንለው የምንችል ይመስለኛል፡፡
[iii] My purpose is to instruct people living in towns, the married, and those at princely courts (preface)
[iv] በነገራችን ላይ ከሰዎች መካከል መርጦ ክርስቲያን ስላደረገን አመስግነን የምናውቅ ምን ያህል ነን?
[v] መጽሐፉ ስለ ብስጭትም ራሱን በቻለ ምዕራፍ ይናገራል፡፡
[vi] እዚህ ላይ የእማሆይ ሜላኒ ስቦቮዳ “Meeting God in Small Things” (እግዚአብሔርን በትንንሽ ነገሮች ውስጥ ማግኘት) የተባለው መጽሐፍ ውስጥ ያየሁት አንድ የቻይኖች ጥቅስ እንዲህ ይላል፡- “መቆምን እንጂ ቀስ ብሎ ማደግን አትፍራ፡፡” አንድ ሌላ ጸሐፊም ስለ አሲሲው ቅዱስ ፍራንቸስኮስ ሲናገሩ “ለእርሱ ወደፊት አለመሔድ ማለት ወደኋላ መመለስ ነው፡፡” ማለታቸውን አስታውሳለሁ፡፡ 
[vii] ይህ የቅዱስ ፍራንሷ አባባል የአንዲት ራቢያ የተባለች በእስልምና ሃይማኖት የሱፊ ዘውግ ተከታይ የነበረችን ተማሐላዪ (Mystic) የአስራ ሁለተኛው ክፍለ ዘመን ሴት ያስታውሰኛል፡፡ ብላለችና፡-
Oh my God, if I worship you for the fear of hell, burn me in hell.
If I worship you to enter to paradise, exclude me from paradise.
But, if I worship you for your own being, withhold not your beauty from me.
አምላኬ ሆይ!
የማመልክህ ሲዖልን ስለምፈራ ከሆነ በሲዖል አቃጥለኝ፡፡
ገነትን ለማግኘት ሽቼ ከሆነም ከገነት አስቀረኝ፡፡
ግና አንተን ለአንተነትህ የማመልክህ ከሆነ ውበትህን አትሰውርብኝ፡፡

[viii] በነገራችን ላይ በምዕራፍ 27 ላይ “ሰውነትን የሚመርዝ ነገር የሚገባው በአፍ እንደሆነ ሁሉ ልብን የሚመርዘው ነገር ደግሞ በጆሮ ይገባል፡፡” በሌላም ቦታ እንዲሁ “የልብ መተንፈሻዎቿ ጆሮና አንደበት ናቸው፡፡ በጆሮ ወደውስጥ በአንደበት ደግሞ ወደ ውጭ ትተነፍሳለች፡፡” ይላል፡፡







Saturday, January 1, 2011

ልደተ እግዚእ


ምድረ ፍልስጥኤም እንደ ሌሎቹ የመካከለኛው ምስራቅ፣ የሰሜን አፍሪካና የታናሸ እስያ አገሮች በሮም ቅኝ ግዛት ሥር ነበረች፡፡ በውስጧ ነበሩ ሕዝቦችም የተከፋፈለ የሃይማኖትና የፖለቲካ ቡድን ነበራቸው፡፡ ከነዚህም ዋናዎቹ የፈሪሳውያንና የሰዱቃውያን ቡድኖች ነበሩ፡፡ የሰዱቃውያን ቡድን የሀብታሞችና የካህናት ቡድን ነው፡፡ ይህ ቡድን ለባህል፣ ለሥነ ሥርዓትና ና ለሃይማኖት ግድ የሌለው፣ ክኝ ገዥዎች ጋር ተስማምቶ በነሱ ሥልጣኔ መጠቀምን ብቻ የሚፈልግ ቡድን ነበር፡፡ ከሃይማኖት መጻሕፍትም የሙሴን ሕግ ብቻ እንጂ የነቢያትን ትንቢትና ሌሎችንም የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት አይቀበሉም ነበር፡፡ የሙታንን ትንሣኤና የመሢሕንም መምጣት አያምኑም ነበር፤ ሌላው ቡድን የፈሪሳውያን ቡድን ነው፡፡ ፈሪሳዊ “ፓራሽ” ከሚለው የዕብራይስጥ ቃል የወጣ ነው ትርጉሙም “የተለየ” ማለት ነው፡፡ እነዚህ ፈሪሳውያን ምንም የቅኝ አገዛዝ ቀንበር መላልሶ ቢያደቃቸውም ባህልና ልምዳችን አይነካ፤ በሃይማኖትም የሙሴን ሕግና የነቢያትን መጻሕፍት የምንጠብቅ እኛ ብቻ ነን ባዮች ነበሩ፡፡ ስለዚህ ከአይሁድ ዘር ውጭ ከሆነ ማንኛውም ጎሳና ዘር ጋር በባህልና በሥልጣኔ መቀራረቡን እንደመርከስና ሕግን እንደመተላለፍ ይቆጥሩት ነበር፡፡ የመሲሕንም መምጣ ነቅተውና ተግተው ይጠባበቁ ነበር፡፡ ለዚህም ዋናው ምክንያቸው ሀገራቸው ፍልስጥኤምን ከሮምግዛት ነጻ የማውጣት የቆየ ጉጉት ስላላቸው ነው፡፡

እንደነሱ አስተሳሰብ መሲሕ ሲመጣ የጦር ኃል አቋቁሞ ራሱ የጦር መሪ በመሆን የሮማን የቅኝ ግዛት ቀንበር አውልቆ ጥሎ የዳዊትን ቤተ መንግሥት የሚያድስ መሲሕ ይጠባበቁ ነበር ማለት ነው፡፡ ምንም እንኳ ከትንሣኤ በኋላ ሥጋዊ ኑሮ አለ ብለው ቢያምኑም ትንሣኤ ሙትን መኖሩን ያውቁ ነበር፡፡ ፈሪሳውያን በዕለታዊ ኑሯቸው ብዙ ሀብት የሌላቸውና በዕውቀትም መጠነኞች ነበሩ፡፡ መሲሕ መጥቶ የጦር ኃይል አቋቁሞ በጦር ኃይል ፍልስጤምን ነጻ ያወጣል የሚለውን የፈሪሳውያን እምነትና ተስፋ በመቃወም ሌላ ንዑስ ቡድን ከፈሪሳውያን ተከፍለው በሙት ባሕር አካባቢ ገዳም መሥርተው ይኖሩ ነበር፡፡ የእነሱም ዓላማቸው እንደ ፈሪሳውያ መሲሕን መጠበቅ ነው፡፡ ኤሤይ በመባል የሚታወቁት እነዚሁ ክፍሎች ከፈሪሳውያ የሚለዩት ፈሪሳውያን በጦር ኃይል ነጻ እንወጣለን ሲሉ ኤሤይ የሚባሉት ደግሞ በተአምራት በእግዚአብሔር ኃይል ፍልስጥኤም ነጻ ትወጣለች ብለው ያምኑ ነበር፡፡  በቤተልሔም በስተደቡብ ልዩ ሰሙ ኩምራን በሚባል ቦታ የሚኖሩ እነዚህ ሰዎች መጻሕፍትን በመጻፍ ጸሎትን በማድረስ ብዙ ጊዜ ቆይተዋል፡፡ ኤሴዎችና ፈሪሳውያ ባንድ አንድ ሐሳብ ቢለያዩም መሲሕ መምጣቱንና የተወሰኑ ምርጥ ጎሳዎችን ነጻ እንደሚያወጣ ዓለማቀፋዊ መሲሐዊ መንግሥት እንደሚያቋቁምና እነሱም መንግሥቱ ባለሟች እንደሚሆኑ ሁለቱም ቡድኖች ያምኑ ነበር፡፡ በእስራኤል የሃይማኖትና የነገድ ቤተሰብ ውስጥ ይህ ልዩነት ተፈጥሮ መከራቸውን ሲያዩ በፍልስጥኤምና ከፍልስጥኤም ውጭ የነበረው የሮማ መንግሥት ፖለቲካ ደግሞ ከቅኝ ግዛቱ ስፋት የተነሣ ያነገንግ ነበር፡፡ የነጻ አውጭ ግንባሮች በየጊዜው የሚጥሉትን አደጋና ግጭት ለመቆጣጠር እንዲያመች በየጊዜው የሕዝብ ቆጠራ እንዲደረግ ታዞ ነበር፡፡ ሕዝቡ በጠቅላላ ገበሬውም ሆነ ነጋዴው የመንግሥም ባለሥልጣን በሚሠራው ሥራ ሁሉ ባለ ጸጋ ስለነበር የሮም ግዛት ተወዳዳሪ የሌላት ታላቅ አገር ነበረች፡፡ ታዲያ ምን ያደርጋል እነዚህ ሁሉ ሀብታት ለሕዝቡ ደስታንና ውስጣዊ ዕረፍትን ሊያስገኙለት አልቻሉም፡፡ ሁልጊዜ በአካባቢው ከሚሰማው የሽብራ የሁከት ድምጽ የተነሣ ባልታሰበ ቀን እንደመሰሳለን የሚል ቀቢጸ ተስፋ ገዝቶት ነበር፤ ያመልኳቸው ከነበሩ ጣዖታትም አንዳችም የተስፋ ድምጽ አልነበረም፡፡ በቀቢጸ ተስፋ ባሕር ውስጥ ገብቶ የሚማቅቀውና መውጣትም የተሳነው አማኛቸውን ሊያረጋጉት አልቻሉም፡፡ ዳዊት እንደተናገረው ዓይን እያላቸው የማያዩ፣ ጆሮ እያላቸው የማይሰሙ፣ እጅ እያላቸው የማይዳስሱ፣ አፍ እያላቸው የማይናገሩ፣ እግር እያላቸው የማይሄዱ ግዑዛን ናቸውና፡፡ ከዚህም የተነሣ ማለት የሚያመልኳው ጣዖታት ሊረዷውና ሊያረጋጓቸው ስላልቻሉ ሕዝቡ “አማልክቶቻችን የዋኃና ግድ የለሾች ናቸው” እያለ በጣዖታቱ ይዘብት ነበር፡፡ የሰው ልጅ ሥልጣኔም በክፋትና በደግነት መካከል ያለውን ልዩነት ለማመልከት አልቻለም፡፡

በዚህ አኳኋን ስለሰው ልጅ የወደፊት ዕድል ምንም የተስፋ ጭላንጭል አልነበረም፡፡

ሰው በተፈጥሮው ከወዴት መጣሁ? ወዴትስ ነው የምሄደው? ብሎ ራሱን በራሱ የመጠየቅና የመመርመር ስጦታ ያለው ባለ አእምሮ ፍጡር ስለሆነ እነዚህ ጥያቄዎች ሁል ጊዜም ከፊቱ ይደቀኑበታል፡፡ ነገር ግን ለነዚህ ጥያቄዎች ከውስጥ ከራሱም ሆነ ከውጭ ከሌላ አጥጋቢ መልስ ስላላገኘ ከላይ   ንደገለጥነው የደስታን ኑሮ ጣዕሙንና ምሥጢሩን ሊያውቀው አልቻለም፡፡ በሮም ቅኝ ግዛት ውስጥ የሚኖሩ ሁሉ በዚህ ሁኔታ በቀቢጸ ተስፋ ስለተሞሉ እነርሱም ሆኑ ሥርዓተ ማኅበራቸው ጠባቂ እንደሌለው መንጋ ወይም ቀዛፊ ሊቀ ሐመር (ካፒቴን) እንደሌለው መርከብ አቅጣጫው የማይታወቅ ሆነ፡፡ ሕዝቡን ለማስደሰት በሮም የቴያትር ሰገነት ላይ የሚቀርበው የጨዋታ ዓይነትም እንኳ ደም መፋሰስና መደባደብ ሰስለነበር በጨለማ ላይ የዛፍና የገደል ጥላ ሲጨመር ጨለማው እንደሚጸና ሰቀቀኑን አባብሶት ነበር፡፡ ሀብታሙ በሀብቱ ደስታን ለመሸመት አልሆንለት ብሎ ሲጨነቅ፣ ሲጠበብ በዝቅተኛው ሕዝብ ዘንድ ደግሞ ዕጓለማውታንና መበለታትን ወዴት ወደቃችሁ የሚላቸው አልነበረም፡፡ በሽተኞችና ረሃብተኞች ጥርኝ ጥሬ፣ ኩባያ ውኃ የሚላቸው አጥተው በረሀብ ይተላለቁ ነበር፡፡ ሲሞቱም ያውሬ ራት እንጂ የሚቀብራቸው አልነበረም፡፡ ባጠቃላይ ፍርድ ተጓደለ ድሀ ተበደለ የሚል ታዛቢ ተመልካች የሌለበት የአስረሽ ምቺውና የብላ ተባላ  ዘመን ነበር፡፡ “የሰው አውሬው ሰው ነው” (homo homini Lupus est) የሮማውያን ተረት የተፈጸመው በዚህ ጊዜ ነበር፡፡



እነ አውግስጦስ ቄሣር የሰላም እመቤት ብለው የሰየሟት ወይም ራሷን ሰላም ብለው የጠሯት ፓክስ ሮማና ፍቅርና ሰላምን አላስገኘችላቸውምና ይህ ሁሉ የሁከትና የሽብር ጥላ ባንዣበበት ወራት የቤተክርስቲያን መሠረት፣ የአሕዛብ ብርሃን፣ የእስራኤል ዘነፍስ ክብር መድኅነ ዓለም በሮም ቅኝ ግዛት ሥር በነበረች ክፍል ፍልስጥኤም ልዩ ስሟ ቤተልሔም በምትባል በይሁዳ ክፍል ተወለደ፡፡

በተወለደም ጊዜ ትንቢት ያልተነገረላቸው፣ ሱባኤ ያልተቆጠረላቸው ከአሕዛብ ወገን የሆኑ ሰብአሰገል መድኅን መወለዱን አውቀው ከምድረ አሕዛብ ወርቅ፣ ዕጣን፣ ከርቤ ይዘውለት መጡ ገበሩለትም፡፡ የመወለዱም ዓላማ የሰውን ዘር ከጠፋበት ለመፈለግ፣ ወደፊተኛው ክብሩ ለመመለስ፣ ስለ ጽድቅ ለማስተማርና ለመመስከር ነው፡፡ በመድኅን መወለድ ሰዎች ብቻ ሳይሆኑ መላእክትም ተደስተዋል፡፡ “በሰማይ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይገባዋል በምድርም ሰላም” እያሉ ዘምረዋል፡፡ ይህ ሁሉ በአንድ ወገን የነበረው የአቀባበል ሥነ ሥርዓት ሲሆን በሌላ በኩል የነበረው የአቀባበል ሥነ ሥርዓት ደግሞ የሚያሳዝን ነበር፡፡ ለምሳሌ “ሥርዓተ ኦሪትን፣ ትንቢተ ነቢያትን በሚገባ እንከታተላለን፡፡” ይሉ የነበሩ ፈሪሳውያን ክንዱ የሚያደቅ፣ ግርማው የሚንቀጠቅጥ፣ ሮማውያንን አባሮ አገራቸውን ነጻ የሚያወጣ ኃይለኛ መሲሕ ሲጠባበቁ ይኖሩ እንደነበር ተገልጧል፡፡ የኛ መሲሕ ክርስቶስ ግን እነሱ እንደጠበቁት ሁኖ አልመጣም፡፡ እንዲያውም ከላይ እንደተገለጠው ዘመኑ የሁከትና የሽብር ስለነበር አውግስጦስ ቄሣር በየጊዜው ዜጎቹን ያስቆጥር ነበርና ድንግል ማርያም ለመመዝገብ፣ ለመቆጠር አገር ጥላ ስንቋን ቋጥራ በሔደችበት ቦታ መጠጊያ እንኳ በሌለበት በተጨናነቀ አካባቢ ከብቶች በሚያድሩበት ቦታ መሲሕ ተወለደ፡፡ በዚያም የሀብታሞች ነገሥታት ልጆች ሲወለዱ በሚነጠፍላቸው ወርቀ ዘቦ ግምጃ ሳይሆን ሉቃስ እንደ ነገረን እናቱ በጨርቅ ጠቀለለችው፡፡                       
   

ይህን ጽሑፍ የወሰድሁት የሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የነበሩት አቡነ ጎርጎርዮስ “የቤተክርስቲያን ታሪክ በዓለም መድረክ” ብለው ካሳተሙት መጽሐፍ ላይ ነው፡፡  

በረከታቸው ይደርብን!