Wednesday, May 1, 2013

ውዴን ያያችኹ ንገሩኝ


ውዴን ያያችኹ ንገሩኝ፤
ነፍሴ በፍቅሩ ታምማለች፤
ልቡናዬ በናፍቆቱ እጅጉን ተንሰፍስፋለች፡፡



 ነፍሴ ሆይ ያው! ያውልሽ!
ከሩቅ ይታያል ውድሽ
በወዳጆቹ ተክዶ
በሠላሣ ብር ተሸጦ
በግፍ ታስሮ ይጎተታል
መስቀሉ ከብዶት ይወድቃል
ደግሞም ይነሣል
          ይ
    ወ
         ድ
             ቃ
                 ል፡፡




ነፍሴ ያውልሽ ውድሽ!
ተደበደበ፤ ተናቀ፤
          ተገፋ፤
ተጣለ፤
ምራቅ……………..ተወረቀ፤
ተ…ጎ…ተ…ተ…፤
ተ…ገፈፈ፤ ታሠረ፤ ተቸነከረ፡፡

ዘውዱ የሾኽ አክሊል፣
ዙፋኑ እርጥብ መስቀል፣
ትከሻው በሸክም ቆስሎ፣
እጁ በችንካር ተቀድዶ፣
እግሩ ጎልጎታ ቆሟል፣
ደሙ እንደውኃ ይወርዳል፡፡


ጀርባው ታርሷል በአለንጋ፤
ጎኑም በጦር የተወጋ፣
ጠረኑ ሽቱና ከርቤ፣
ከበፍታ ልብሱ ዐወደ፣
ከእንግዳ መቃብር ተአንገደ፡፡

ነፍሴ ሆይ ! ያው ያውልሽ፤
በመከራው የወደደሽ፣
በሞቱ የወለደሽ፣
በትንሣኤው ሊያድስሽ፣
ተቀበረልሽ፡፡

No comments:

Post a Comment