Friday, April 5, 2013

ዝምታ


ሄሮድስ ትርኢት ሽቶ እስረኛውን ኢየሱስን ጥያቄ ይጠይቀው ጀመር፡፡ የሰይጣን ወጥመዶች መልካቸው ቢለያይም ኹልጊዜም ቢኾን ይዘውት የሚመጡት ፍልስፍና “እኔ”ን በእግዚአብሔር ፈንታ አምላክ አድርጎ ማቆም ነው፡፡ አርባ ቀንና አርባ ሌሊት በጾመ ጊዜ “እስኪ ከዚኅ ቁልቁል ተወርወርና የእግዚአብሔር ልጅ መኾንኽን አስመስክር፡፡” ብሎ በግልጥ ጥያቄ ያቀረበው ሰይጣን አኹን ደግሞ በሄሮድስ አንደበት ተአምራት እንዲያደርግ ይወተውት ጀመር፡፡ ስንት ተአምር በፊታቸው እያደረገ “መሢሕ መኾንኽን እናምን ዘንድ ምን ተአምር ታደርጋለኽ” ብለው የጠየቁት ሰዎች የአራት ቀን ሬሳ አልዓዛርን ከሞት መነሣቱን እያዩና እየሰሙም ሌላ በእነርሱ ቀመር የተዘጋጀ ተአምር እንዲሠራ ይጠይቁታል፡፡

የሄሮድስ “ተአምር ሥራና አሳየኝ” የምትል ጥያቄ ላይ ላይዋን የሰርከስ ፍቅር ትምሰል እንጂ ውስጧ “ክብርኽን ተከላከል፤ ራስኽን አስከብር” በሌላ አማርኛም “እስኪ ከመስቀል ውረድ” የምትል እግዚአብሔርን እርሱ በወደደው ሳይኾን እኔ በቀመርኹለት ቀመር ብቻ እንዲሠራ መመኘት ናት፡፡ ለዚኽች ጥሪ የሚሰጠው መልስ ግን ዝምታ ብቻ ነው፡፡ የእኔ ክብር በፍቅር ለፈጠረኝ ፍቅር የመሚገባ የፍቅር ምላሽ መስጠት ብቻ ነው፡፡ ከዚኽ ውጪ እንኳን ክብር ትርጉምም አይኖረኝም፡፡

ሄሮድስ ምኞቱ በውትወታ አልሳካ ሲለው በንቀት በኩል ሌላ የ”ማንነትኽን አስመስክር” የዕብሪት ጥሪ ያቀርባል፡፡ ጌታ ኢየሱስ ግን በሄሮድስ የንቀት ፊት የእግዚአብሔርን የትሕትና መንገድ ገለጠ፡፡ ለስድብ መልስ የለውም፡፡ ለትርኢት ተብሎ የሚደረግ በጎ ነገርም እግዚአብሔር አይከብርበትም- “እኔ” ጣዖት ኾኜ በእግዚአብሔር ፈንታ ቆሜያለኹና፡፡

ሄሮድስ ሊዘብት ጌጠኛ ካባ አለበሰው፡፡ ጌታ ኢየሱስ ግን ለዚኽም መልስ አልሰጠም፡፡ ዝምታ ብቻ፡፡ በሰው ልጆች ክፋት ውስጥ የምትሠቃየውን የእግዚአብሔርን በጎነት፣ በሰው ልጆች ጥላቻ የምትገፋውንና የምትሠቃየውን የእግዚአብሔርን የፍቅር ዕቅፍ እያሳየ ዝም አለ፡፡ ውዴ ዝም አለ፡፡

No comments:

Post a Comment