Tuesday, January 22, 2013

እኔን ኾነኽ





ጌታ ሆይ! ምንኛ ወደድኸኝ! ስለወደድኸኝስ ምንኛ ተዋረድኽልኝ! ይህን ፍቅር ምን አንደበት ሊገልጠው፣ የትኞቹስ ቃላት ሊሥሉት ይችሉ ይኾን! የአንተ ታደርገኝ ዘንድ እኔን ኾንኽልኝ፤ ትፈልገኝ ዘንድ ተገኘኽልኝ፤ በመንግሥትኽ ታሳርፈኝ ዘንድ በድንግል ማኅጸን ኾነኽ ማረፊያ ፍለጋ ከበረት ገባኽልኝ፤ ታነሣኝ ዘንድ ወደቅኽልኝ፡፡ ጌታ ሆይ! በእውነት ሥራኽ ከአእምሮ በላይ ነው! እንደ ቅድስት ድንግል በልብ ይዞ “ዕፁብ ያንተ ሥራ!” እያሉ በምሥጋና ነፍስን በፊትኽ ከማፍሰስ ውጪ ምን መግለጫ ይኖረዋል!

የጣልኹትን እኔነቴን እኔን ኾነኽ ቀደስኸው! ያልቀደስኸው የእኔነቴ ቅንጣት የለም፡፡ ኹለመናዬን ቀደስኸው! ሰው ኾነኽ ሰው መኾንን ቀደስኸው! አቤቱ ስምኽ ይባረክ! የድንግል ማርያም ልጅ ፍጹም አፍቃሪዬ፣ የእነቴ እውነተኛ ወዳጅ ሆይ! ስምኽ ከፍ ከፍ ይበል፡፡ ጌታ ሆይ! በየዕለቱ ይበልጥ አንተን ማወቅን፣ አንተን ማፍቀርንና አንተን መከተልን በልቤ ጨምርልኝና በልቤ በየቀኑ ተወለድ፤ ኑርልኝም፡፡ እንዳረፍኽባት ግርግም ነገሥታቱም፣ እረኞቹም፣ መላእክቱም ወደ እኔ ሲመጡ የሚያገኙት አንተን ብቻ፣ የሚሰሙትም ቃልኽን፣ የሚሰማቸውም ሰላምኽና ፍቅርኽ ብቻ ይኹን፡፡ አባቴ ሆይ! እኔን የሚያገኙኝ ኹሉ አንተን እንጂ እኔን አያግኙ፡፡ በእኔ ውስጥ አንተ ብቻ እንጂ እኔ አይኑር፡፡ መድኃኒት በኾነልኝ ስምኽ! አሜን፡፡



No comments:

Post a Comment